ዓርብ, ኤፕሪል 03, 2015

ባሻ አሸብር በአሜሪካ

 

ደማሙ ብዕረኛ መንግስቱ ለማ

**************************

የዛሬ አስር አመት በታላቅ ሹመት                           
አሜሪካ ልኮኝ ነበረ መንግስት
ዋሽንግተን ገብቼ ዋልኩ አደርኩኝና
ሽር ሽር ስል ሳለ ባንድ አውራ ጎዳና
አላፊ አግዳሚውን ጥቁሩን ነጩን
ሳለ ስመለከተው በኢትዮጵያዊ አይን
የውሀ ጥም ደርሶ ስላረገኝ ቅጥል
ከመንገድ ዳር ካለች ካንድ ትንሽ ሆቴል
ጎራ አልኩና ገና ከወንበር ላርፍ ስል
ተንደርድሮ መጣ የሆቴሉ ጌታ
አማረው ቋመጠ ከጀለው ሊማታ
አብዷል ሰክሯል እንዴ ምንድን መሆኑ ነው
በል ንካኝ በዱላ ግንባርህን ላቡነው
ብዬ ስነጋገር ሰምቶ ባማርኛ
አሳላፊው ሆነ አስታራቂ ዳኛ
ለጥ ብሎ እጅ ነሳና እንደሀገራችን ህግ
አክብሮ ጠየቀኝ ምን እንደምፈልግ
እኔም ጎራ ያልኩንት የሚጠጣ ነገር
ለመሻት መሆኑን ነግሬ ከወንበር
ይቅርታዎን ጌታ አዝናለሁ በጣሙ
ምናምኒት የለም በከንቱ አይድከሙ
አለና እጅ ነሳኝ ሳቁን እየቻለ
“ውሀም የለ?” ብለውማ በሳቅ ገነፈለ
ቤቱን የሞላው ሰው ሁሉም አጨብጭቦ
ብራቮ! ተባለ ብራቮ! ብራቮ!
 በጣም ተገርሜ ደንቆኝ አየሁት
ከዘራዬን ይዤ ሄድኩኝ ወጣሁት
ሃሣብ ገብቶኝ ደጅ ሳሰላስል ቆሜ
ያን ቂዛዛ መስኮት ባስተውለው አግድሜ
አራዳ ግሪኮች እንደሚሸጡት
ያለ በያይነቱ አየሁኝ ብስኩት
ትዝ አለኝ “አራዳ አዲስአባ ሆይ
ሀገርም እንደሰው ይናፍቃል ወይ?”
አስጎመጀኝ በሉ ሳይርበኝ ጠግቤ
አስተውለው ጀመረ መስኮቱን ቀርቤ
የምገዛውንም በልቤ ቆጥሬ
ዳግም ልገባ ስል በስተበሩ ዞሬ
ዞወር ብዬ አያለሁ የሆቴሉ ጌታ
ወገቡን በጁ ይዞ እንደሚል እስክስታ
ተኩሮ ያየኛል ወደኔም ተጠጋ
“ስንት ነው ወዳጄ ያንዱ ብስኩት ዋጋ?”
የያዘው አባዜ ብሎት አላናግር
አይኑ ደም ለበሰ ይጉረጠረጥ ጀመር
አለም ሁሉ ያውቃል መሆኔን ታጋሽ
ትዕግስቴ አሁን አልቋል ጥፋ ብረር ሽሽ
አገጭህን በቦክስ አሁን ሳላፈርሰው
ይህን ጎረጥ አይንህን እዚህ ሳላፈሰው
ከሱቄ መግባትህ አንሶህ አሁንስ
መስኮቴ ስር ደግሞ ልትልከሰከስ
ገበያ አላገኝም ደንበኞቼም
አንተን እዚህ ካዩ ዳግመኛ አይመጡም
ስራ ስራ እኮ ነው አየገባህም እንዴ
ወግድ አትገተር ይቋረጣል ንግዴ
ይህንን እንዳለ ቁጣው ጠና ጋለ
አገጭ እና ጉንጬን በቡጢ ነደለ
በቦክስ አይለኝም መልሶ መልሶ
እስኪሸረፍ ድረስ ጥርሴ በደም ርሶ
ዠለጥ አደረኩት በያዝኩት ከዘራ
ግን አልጠቀመውም ዘበኛ ተጣራ
ፖሊስ ቢሮ ሄድን እርሱ ተለቀቀ
አሸብር ከልካይ ግን ወህኒ ማቀቀ
ማን ሊሰማኝ እዛ ዘሬን ብቆጥር
ብሸልል ባቅራራ ወይም ብፎክር
ደረቴ ላይ ያለው የሀገሬ ባንዲራ
ያምራል ተባለ እንጂ ከብሮም አልተፈራ
የሞጃው ተወላጅ የጠራሁት መንዤ
ሸጎሌ ሻንቅላ ተብዬ መያዜ
የግፍ እንደሆነ የውሸት ሀሰት
አቃተኝ ማንንም ከቶ ማስረዳት
ሲቸግረኝ ጊዜ አንዱን ተጠግቼ
ሻንቆን እንዲህ አልኩት ነገሬን አስልቼ
ሰማኸኝ ወንድሜ አላሳዝንህም?
በሰው ጠብ ገብቼ በከንቱ ስዳከም
አውቃለሁ ከጥንቱ ነጭ እና ሻንቅላ
በቂም እንደኖረ ሲዋጋ ሲጣላ
እኔ ግን ሀበሻው ምን ወገን ልለይ
በማይነካኝ ነገር ለምን ልሰቃይ
እንካ ፀጉሬን እየው ሸጎሌ አይደለሁም::
********************************
ምን ጭ-:http://www.ethiopiaobserver.com/mengistu-lemma-reads-basha-ashebir-be-america/

ማሞ ካቻ (አቶ ማሞ ይንበርብሩ)

  አቶ ማሞ ይንበርብሩ (ማሞ ካቻ) እስቲ እናስታውሳቸው፣ ተቀብሮ እንዳይቀር አኩሪ ታሪካቸው  (ደረጀ መላኩ)   አቶቢሲ ማሞ ካቻ የት ትሄዳለህ? ገብረ ጉራቻ… ታዳጊው ማሞ ይንበርበሩ ገና በጨቅላ እድሜው አባቱ አቶ...