ሐሙስ, ኦክቶበር 15, 2015

አምባሳደር ዘውዴ ረታ ታላቁ የታሪክ ማሕደር ተለየን

                                                                 (ከ1927-2008 ዓ.ም)


ኢትዮጵያ ሰሞኑን ከባድ ሃዘን መትቷታል። ታላላቅ ሰዎቿን በሞት ተነጥቃለች።  ባለፈው ሳምንት ደግሞ ታላቁን የታሪክ ፀሐፊ ጋዜጠኛ እና ዲኘሎማት አምባሣደር ዘውዴ ረታ አጥታለች።  ዘውዴ ረታ ብሪታኒያ (ለንደን) ውስጥ አረፉ።


ከአንድ ወር በፊት ነሀሴ 7 ቀን 2007 ዓም አምባሣደር ዘውዴ ረታ የተወለዱበት የ80 ዓመት የልደት ቀናቸው ነበር። የማስተር ፊልምና ኮሚኒኬሽንስ ባለቤትና ሥራ አስኪያጅ ጋዜጠኛ ቢኒያም ከበደ ለኚህ ታላቅ ሰው የሚመጥን ዝግጅት አድርጐ የዘውዴ ረታን የ80 ዓመት የልደት በአላቸውን ጐፋ ገብርኤል በሚገኘው መኖርያ ቤታቸው በደማቅ ሁኔታ አከበረላቸው። እኔም በዚህ የልደት በአላቸው ቀን ተጋብዤ የዘውዴ ረታን የመጨረሻውን የልደት በአል አከበርኩ። ያቺ ቀን ፈጽሞ አትረሣኝም። ምክንያቱም ዘውዴ ረታ ትልቅ ኢትዮጵያዊ የገዘፈ ስብእና ብሎም በሕይወት ያሉ የዘመን ተራኪ ብእረኛ በመሆናቸው ነው። ከእንዲህ አይነት ሰው ጋር ዳቦና ኬክ ቆርሶ መቋደስ፤ የኋላና የፊት የኢትዮጵያን ታሪክ ማውጋት፤ ከቶስ በምን ይገኛል? ከሁሉም በላይ ደግሞ የመጨረሻውን ቃለ-መጠየቅ ያደረግንላቸው ቀን በመሆኑም ፈፅሞ የማትረሣ ቀን።


በዚያች በነሃሴ 7ቀን 2007 ዓም የዘውዴ ረታን የ80 አመት ልደት በደማቅ ሁኔታ ካከበርን በኋላ አይናችን ግድግዳው ላይ ባሉ አስገራሚ ፎቶዎች ላይ ተሠክቶ ቀረ። ዘውዴ ረታ በዚያ በወርቃማው ዘመናቸው ማለትም ቅድመ 1967 ዓም ከበርካታ የምድራችን ታላላቅ ሰዎች ጋር የተነሷቸው ፎቶዎችን እያየን ስንገረም ቆየን። ዘውዴ ረታም ከኛ ጋር ፎቶዎቹን እያዩ ስለ እያንዳንዱ ፎቶ ትዝታቸውን እና ታሪኩን ያወጉን ጀመር። መሪዎች፤ ንጉሶች፤ የጦር አበጋዞች፤ ዲኘሎማቶች፤ የግዙፍ ስብእና ባለቤቶች ግድግዳው ላይ ሆነው ያለፈውን ዘመን ይተርኩልናል፣ ያሳዩናል፣ ያስታውሱናል። እዚያ ግድግዳ ላይ ሆነው ከሚያወጉን የምድሪቱ ታላላቅ ሰዎች መካከል በሕይወት የቀሩት አምባሣደር ዘውዴ ረታ ብቻ ነበሩ። ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ፤ ፀሀፌ ትእዛዝ አክሊሉ ሀብተወልድ፤ የኢጣሊያ፤ የፈረንሣይ፤ የጀርመን፤ የአሜሪካ፤ የእንግሊዝ ወዘተ ወዘተ መሪዎችና ነገስታት በሙሉ የሉም። ዘውዴ ረታ ብቻ ቀርተው በጋራ የተነሱትን ፎቶዎች ታሪክ ተረኩልን፤ አወጉን። እንዲህ አይነት ሰው በሕይወት ኖሮ ስላለፈው ሁሉ ሲተርክ መስማት በራሱ ያስደስታል። ምክንያቱም ብቸኛው ምስክር ስለሆነ ነው። ፈረንጆቹ እንዲህ አይነት ሰውን ‘A Living Legend’ ይሉታል። በሕይወት ያለው ሕያው ምስክር። ዛሬ ያጣነው ዘውዴ ረታ ይሄ ነው። የታሪክ ምስክሩ አለፈ።


ከሃገራችን ሰው ወርቃማ ምሣሌዎች መካከል “ማን ይናገር የነበረ ማን ያርዳ የቀበረ” የሚለው አንዱ ነው። እናም ዘውዴ ረታ ከአጤ ምኒልክ ዘመን መገባደጃ ጀምሮ ያለውን የኢትዮጵያ ታሪክ ድንቅ በሆኑት ታላላቅ መጽሀፎቻቸው ያስነበቡን በቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዘመን ውስጥ ቁልፍ የታሪክ ቦታ ውስጥ በመስራታቸው ነው። ታሪክን ከውስጥ ሆነው ወደ ውጭ የፃፉ ናቸው። አብዛኛው ታሪክ ከውጭ ወደ ውስጥ ነበር የተፃፈው። በዚህ ምክንያት  ደግሞ የተለያዩ የመረጃ ክፍተቶች ይኖራሉ። ዘውዴ ረታ ግን ውስጥ ሆነው ለዘመናት ያሰባሠቧቸውን የታሪክ ማስረጃዎችን አጠናቅረው በውብ የትረካ ስልታቸው ሦስት ግዙፍ የታሪክ መፃሕፍቶችን ያስነበቡን የወርቃማ ብእር ባለቤት ነበሩ።


ሃምሌ 26 ቀን 2007 ዓ.ም በአዲሰ አበባ ኤግዚቢሽን ማእከል በተካሄደው የንባብ ለሕይወት የመጻሕፍት አውደ-ርእይ ላይ በመጽሐፍቶቻቸው ድንቅ የታሪክ አቀራረብና አፃፃፍ ምክንያት አምባሣደር ዘውዴ ረታ የወርቅ ብእር ተሸላሚ ነበሩ። በዚያ በደማቅ ሥነ ሥርዓት ወቅትም ንግግር አድርገው ነበር። የቀረውን እያዘጋጀሁት ያለው መጽሐፍ ቶሎ እንድጨርሰው ድጋፍ ሆናችሁኝ ብለው ነበር።



እኛም በልደታቸው ቀን በሽልማቱ ወቅት የተነሱትን ፎቶ ግራፍ እቤታቸው በስጦታ አበርከትንላቸው። ቀጥሎም የመጨረሻውን ቃለ መጠየቅ በጋራ አቀረብንላቸው። በወቅቱ እቤታቸው የነበርነው ጋዜጠኛ ቢንያም ከበደ፤ አቶ ሣምሶን አምሃ፤ ገጣሚ አንዱአለም አባተ (የአፀደ ልጅ)፣ አቶ ግርማ ሃብተየስ፤ አቶ ደረጀ ምክሩ /ካሜራ ማን/ እና ውድሰው ዳርዮስ ሞዲ /ኤዲተር/ ነበርን።


በዚህ የልደታቸው ቀን ላይ ብዙ ተጨዋወትን። ስለ መፃሕፍቶቻቸው፤ ስለ ዘመናቸው፤ ስለ እኛ ዘመን፤ ስለ መጪው መጽሐፋቸውም አወጋን። ዘውዴ ረታ በወቅቱ የነበራቸው የጤንነት ሁኔታ ፍጹም ጤነኛ ከመሆናቸውም በላይ ንቁ አእምሮ እና ቀልጣፋ እንቅስቃሴ የሚታይባቸው ነበሩ። የ80 አመት የእድሜ ባለፀጋ አይመስሉም ነበር። እኛም ገና ብዙ የሚቆዩ ናቸው እያልን በውስጣችን አወጋን። ለካ የኛ ግምትና አቆጣጠር አይሰራም። ጉዳዩ ያለው ከላይ ነው። መቼ እንደምንጠራ አናውቀውም።  ስለዚህ እንደ ዘውዴ ረታ  በየትኛውም ዘመን ላይ ስም የሚያስጠራ መልካም ተግባር አከናውኖ መዘጋጀት እንደ ንስሃ ያገለግላል። ንስሃ ግቡ ማለት ጥሩ ስራ ስሩ፤ አትዋሹ፤ አትቅጠፉ፤ ሃጥያት አትስሩ ነው። የዘውዴ ረታ መፃሕፍት ውስጣቸው ያለው ሃቅ ነው። ንስሃ ነው።


የዘውዴ ረታ ብዕር ካፎቱ የተመዘዘው በታሪክ ውዠንብር ውስጥ በወደቅንበት ወቅት ነበር። ለምሣሌ ኤርትራ የኢትዮጵያ ቀኝ ግዛት ነበረች እየተባለ ይወራ ነበር። ኢትዮጵያ ኤርትራን አስገድዳ ጨፍልቃ ነው የገዛችው እየተባለ የሚነገርና የሚደመጥ ሃሣብ ነበር። ዘውዴ ረታ ደግሞ የኤርትራ ጉዳይ ብለው መጽሐፍ አሣተሙ። መጽሐፉ በእውነተኛ መረጃዎች ላይ ተመርኩዞ የተፃፈ ነው በሚል አያሌ አንባቢዎች ወደዱት። እስከ ዛሬም ድረስ በተደጋጋሚ እየታተመ ወዲያው የሚያልቅ መጽሐፍ ነው። መጽሐፉ ሰፊ ተቀባይነትና እውቅና አገኘ።


ተቀባይነትን ያገኘው በኢትዮጵያዊያን ብቻም አልነበረም። ዛሬ ከኢትዮጵያ ተገንጥለው ራሣቸውን መቻላቸውን በሚናገሩ በኤርትራዊያንም ጭምር ነበር። መጽሐፉ ኢትዮጵያ ውስጥ እንደሚነበበው ሁሉ ኤርትራ ውስጥም ተነባቢ ሆነ። በርካታ ኤርትራዊያን መጽሐፉን እንደገዙትም ይነገራል። በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ምን ቢጠቀስ ነው የሁለቱም ሃገር ዜጐች የሚያነቡት የሚል ጥያቄ መነሣቱ አይቀርም


አምባሣደር ዘውዴ ረታ የፃፉት የኤርትራ ጉዳይ መጽሐፍ ትክክለኛ የታሪክ ሰነዶችን በመያዙና እውነተኛ ሃቅ በማንፀባረቁ ነበር የተወደደው። ለምሣሌ ቀደም ባለው ዘመን ኤርትራ በእንግሊዞች የቅኝ አገዛዝ መዳፍ ስር በነበረችበት ወቅት ከዚያ መከራ ወጥታ ከእናት ሃገሯ ከኢትዮጵያ ጋር እንድትቀላቀል ከፍተኛ መስዋእትነት የከፈሉት ኤርትራዊያን ራሣቸው መሆናቸውን ደራሲው ይገልፃሉ። በወቅቱ ኤርትራ እና ኢትዮጵያ ተዋህደው ለመኖር ካለ ጦርነት እና ተጽእኖ በሰላምና በፍፁም ደስታ እንደነበር የጽሁፍ ማስረጃዎችን እየጠቃቀሰ መጽሐፉ ይተነትናል። በነዚህና በሌሎችም የአፃፃፍ ቴክኒኩ መጽሐፉ እስከ አሁን ድረስ በከፍተኛ ደረጃ ከሚታተሙና ከሚሸጡ መፃሕፍት መካከል አንዱ ነው።


የዘውዴ ረታ የመተረክ ችሎታ በስፋት የሚያሣየው ሁለተኛው ግዙፍ መጽሐፋቸው በ1997 ዓም ላይ ብቅ አለ። ርእሱ ተፈሪ መኰንን ረዥሙ የሥልጣን ጉዞ ይሠኛል። ይህ መጽሐፍ 547 ገፆች ያሉትና ከ1884-1922 ዓ.ም የነበረችውን ኢትዮጵያን እና ቤተ-መንግሥታዊ ፖለቲካዋን የሚያስቃኘን በውብ የትረካ ክህሎት የቀረበ ነው።


መጽሐፉ የአፄ ኃይለሥላሴን ውልደት ማለትም ገና ከጋብቻና ከጽንስ ጀምረው እንዴት እንደተወለዱ በመተረክ የአፄ ምኒልክን የመጨረሻ የስልጣን ዘመን ይዞ ልጅ እያሱን፤ ንግስት ዘውዲቱን፤ ተፈሪን እያለ የሚያወጋ የታሪክ ሰነድ ነው። አንድ ታሪክ ፀሐፊ ማስተላለፍ የፈለገውን ታሪክ ለመግለጽ ዋነኛው መሣሪያ ቋንቋ ነው። ዘውዴ ረታ የሰበሰቧቸውን የታሪክ ሃቆች ውብ በሆነ የአማርኛ ቋንቋ ችሎታ አንባቢን የሚመግቡ ፀሐፊ መሆናቸውን ያስመሠከሩበት መጽሐፍ ነው።

የኢትዮጵያ ታሪክ በስርዓት ሲመረመር ብዙ አስገራሚ ጉዳዮች አሉት። ለምሣሌ ዘውዴ ረታ በፃፉት “ተፈሪ መኰንን” በተሠኘው መጽሐፍ ውስጥ አንድ ለየት ያለ ነገር እናገኛለን። ተፈሪ መኰንን /አፄ ኃይለሥላሴ/ በእናታቸው በኩል የሙስሊም ሃይማኖት አለባቸው። የእናታቸው የወ/ሮ ተናኘወርቅ አባት ሺህ አሊ የተባሉ የወረኢሉ ባላባት ናቸው። ከዚህ ቀደም አቶ በሪሁን ከበደ በፃፉት “የአጤ ኃይለሥላሴ ታሪክ” መጽሐፍ ውስጥ ደግሞ የጃንሆይ አባት ራስ መኰንን ከትግሬ ዘር እንዳለባቸው ጽፈዋል። ስለዚህ ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ የብዙ ኢትዮጵያዊ ማንነቶች መገለጫ እንደሆኑ መገንዘብ እንችላለን።


ዘውዴ ረታ የአጤ ኃይለሥላሴን ታሪክ ለመፃፍ ሲነሱ ከየት መጀመር እንዳለባቸው አሰቡ። የአንድ ትልቅ መሪ ታሪክ፤ ከመነሻው ተነስቶ እስከ መጨረሻው ሲዘልቅ እንጂ፤ ከመሃል ተጀምሮ ወደ ፍፃሜዉ ሲያመራ ለአንባቢዎች የተሟላ ሃሣብ ሊሰጥ አይችልም በማለት ወሰኑ። ከዚያም ራስ እምሩ ኃይለሥላሴ የተናገሩት ትዝ አላቸው። ነገር ከመነሻው እንጂ ከመጨረሻው አይጀመርም ያሉትን አስታወሱ።፡ እናም ተፈሪ መኮንን ገና ሲረገዙ ሁሉ ያለውን ታሪክ በጣፋጭ አማርኛ ተረኩት። የተፈሪ እናት እርግዝናቸው አልጠና እያላቸው ሾተላይ እያስቸገራቸው ዘጠኝ ጊዜ አስወርዷቸዋል። ከዚህ ሁሉ ምጥ እና ሾተላይ በኋላ ተፈሪ መኮንን /ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ/ እንዴት እንደተወለዱ ዘውዴ ረታ የተረኩትን በጥቂቱ ላቋድሣችሁ።


“ወ/ሮ የሺእመቤት ከባለቤታቸው ከራስ መኮንን ጋር የነበራቸው ትዳርና ሕይወት ምቾትና ሠላም ያለው በመሆኑ ሲደሰቱ በየአመቱ የሚፀንሱት ልጅ ግን ስለሚሞትባቸው ሃዘንና ሰቀቀን ሣይለያቸው ኖረ። በ1884 ዓ.ም ለዘጠነኛ ጊዜ መፀነሣቸው ሲታወቅ የሸሆቹም ሆኑ የየገዳሙ ትንቢት ተናጋሪዎች “ይህ የተፀነሰው ሕፃን በደህና ወደዚህ አለም ለመምጣት ከጌታ ተፈቅዶለታል። እንደተወለደ ከእናቱ ተነጥሎ ለብቻው በልዩ ጥንቃቄ እንዲያድግ ያስፈልጋል። ከብዙ ሰው አይን ተሠውሮ ካደገ በኋላ ብዙ ፈተናዎችን አሣልፎ አንዱ ቀን ባልተጠበቀ ጊዜ የቅድመ አያቶቹን ዘውድ ለመውረስ ይበቃል”  ብለው ነበር ይባላል።


“ይህ ትንቢት ከልዩ ልዩ ቦታዎች እየተሠራጨ ስለሚነገር የሚባለውን ለመፈፀም ራስ መኮንን እንዲስማሙ ብርቱ ጥረት ተደረገ። በዚያን ጊዜ የራስ መኮንን አስተያየት “የሚሰጥ እሱ፤ ፈጣሪያችን ነው። የሚነሳም እሱ ነው፤ አሁን እኛ በፈጣሪ ሥራ ገብተን እናትና ልጅ የምንለያየው ለምንድን ነው” የሚል ነበር። በመጨረሻም የባሕታዊዎቹ ተከታዮች አሸነፉ።


“ሐምሌ 16 ቀን 1884 ዓ.ም ሌሊት ወይዘሮ የሺእመቤት /ተፈሪ የተባለውን/ ወንድ ልጅ በደህና ሲገላገሉ ወዲያው እናቱ ሳይስሙት /ወይም ሳያዩት/ በሱፍ ጨርቅ ተጠቅልሎ በአገልግል ውስጥ ተደርጐ ለማደጊያ ወደተዘጋጀለት ሥውር ቦታ ተወሠደ። የፃድቁ የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ልዩ አማኝ የሆኑት ወ/ሮ የሺእመቤት ለመጀመሪያ ጊዜ በደህና የተገላገሉትን ሕፃን ልጃቸውን ካላሣያችሁኝ ብለው አላስቸገሩም። “ልጅ በደህና ወልጄ ታቅፌ ለማሣደግ ስፈልግ ብዙ ተሣቅቄ እያለሁ ይኸ ዘጠነኛው ጽንሴ እጅግም አላስቸገረኝም ነበር። ሕይወት እንዲኖረው ከእናቱ መነጠል አለበት ካላችሁ በጤና አድጐ በሰላም እንዳየው እናንተም ፀልዩልኝ” ብለው ዝም አሉ።


“ተፈሪ ከተወለደ ሁለት አመት ሊሞላው ሲቃረብ ወ/ሮ የሺእመቤት እንደገና ፀነሱ። እንደሚባለው ይህ አስረኛው እርግዝና እመይቴን ሰላም አልነሣቸውም ነበር። ከሌሎች ግዜያቶች ይበልጥ ጤንነት ስለተሠማቸው ፆምና ፀሎቱን እጅግ አጥብቀው ሲጠባበቁ መጋቢት 6 ቀን 1886 ዓም የተፀነሰው ለመወለድ መጣሁ አለ። የእርግዝናቸውን ሰዓት ምጡ እጅግ አሰቃያቸው። በዚያን ግዜ በኤጀርሳ ጎሮ ወይዘሮ የሺእመቤት አጠገብ ተገኝተው የዓይን ምስክር የሆኑት በጅሮንድ ተክለ ሃዋርያት በታሪክ ማስታወሻቸው ላይ እንዳሰፈሩት አዋላጆች የሺእመቤትን ሥቃይ ምን ያህል እንዳበዛው ለማስረዳት እጅግ የሚዘገንን መሆኑን ገልፀውታል። አዋላጇ እንደምንም ልጁን መንጥቃ ብታወጣም ሕፃኑ በነፍስ አልቆየም። በቶሎ በድን ሆነ። ወይዘሮ የሺእመቤትም ስቃያቸው ወደ ጣር ተለወጠ። ሰውነታቸው ደከመ። ትንፋሻቸው እያጠረ ሄደ። በዚሁ መጋቢት 6 ቀን 1886 ዓ.ም እኩለ ሌሊት ላይ የወይዘሮ የሺእመቤት የጣር ትንፋሽ ቆሞ፣ ሕይወታቸው አለፈ።”


ዘውዴ ረታ እንዲህ አይነት ልብ የሚነኩ ታሪኮችን በቀላል አማርኛ ግን ውብ በሆነ ትረካ ያስነብቡናል። ታሪክን ከጽንስ ጀምረው እስከ ንግሥና ከዚያም እስከ አለማቀፍ ሰብእና ድረስ የመተረክ ብቃታቸውን ያስመሰከሩበት “ተፈሪ መኰንን ረዥሙ የሥልጣን ጉዞ” የተሰኘው መጽሐፋቸው ዘላለማዊ ስም ያሠጣቸዋል።

ሦስተኛው ግዙፍ መጽሐፋቸው ደግሞ “የቀዳማዊ ኃይለሥላሴ መንግሥት” የሚሰኘው ነው። በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ምንም እንኳ ርዕሱ ከአፄ ኃይለሥላሴ ጋር ቢገናኝም፤ የመጽሐፉ ሰፊ ይዘት ግን ኢትዮጵያ ነች። አብዛኛው ርዕሰ ጉዳይ በንጉሡ ዘመን ስለመበረችው ኢትዮጵያ እና አስተዳደሯ የሚቃኝ ነው። ለምሳሌ ኢትዮጵያ ከፍፁም ፊውዳላዊ ሥርዓት ወደ ሕጋዊ አስተዳደር እንዴት እንደተሸጋገረች ልዩ ልዩ ሠነዶችን በመጠቃቀስ መጽሐፉ ያብራራል።


ከዚህ ሌላም የትምህርትና የስልጣኔ መንገድ በዚያን ዘመን እንዴት እንደነበር ይተርካሉ። በኋላ ደግሞ ይህች ጥንታዊትና ታሪካዊት ሀገር ኢትዮጵያ በፋሽስቶች እጅ የወደቀችበትን እና ዜጐቿ ደግሞ በቅኝ ግዛት መዳፍ ሥር ላለመውደቅ የከፈሉትን መስዋዕትነትም አምባሳደር ዘውዴ ረታ ይተርካሉ። ቀዳማዊ ኃይለሥላሴም በዓለም አቀፍ ደረጃ የሀገራቸውን ጉዳይ ይዘው በመቅረብ በዲፕሎማሲው ረገድ ያበረከቱትን ተግባር በተደራጀ ማስረጃ ዘውዴ ረታ ይተርካሉ። ከኢጣሊያ ወረራ በኋላም እንግሊዝ በኢትዮጵያ ላይ የበላይነቷን ለማሳየት የፈጠረችውን ደባ ንጉሡ እንዴት አድርገው በዘዴ የሀገራቸውን ሉዐላዊነት እንዳረጋገጡ መጽሐፉ ይተርካል። ይሄው 812 ገጾች ያሉት የዘውዴ ረታ መጽሐፍ ኢትዮጵያ ከ1923 ዓ.ም እስከ 1948 ዓ.ም ድረስ ምን እንደነበረች ያሳየናል። ከ1948 እስከ 1966 ዓ.ም ድረስ ያለውን ታሪክ ደግሞ በቅርቡ ያሳትሙታል ተብሎ ይጠበቃል።

እነዚህ ግዙፍ የሆኑ የዘውዴ ረታ መፃሕፍት የቀዳማዊ ኃይለሥላሴን ዘመነ መንግሥት ጠንካራ እና ደካማ ጐኖች በማሳየትና በመተንተን ትልቅ ቦታ የሚሰጣቸው ናቸው። እነዚህንና ሌሎችንም የውድድር ውጤቶች መሠረት በማድረግ ከሀምሌ 23-26 2007 አ.ም በተካሄደው “ንባብ ለሕይወት” በተሰኘው ትልቅ የመፃሕፍት ዐውደ-ርዕይ ላይ መራጭ ኮሚቴው ለአምባሳደር ዘውዴ ረታ ከፍተኛ ድምፅ ሰጥቶ የአመቱ  የወርቅ ብዕር ተሸላሚ አድርጓቸዋል።


በመጽሐፋቸው ውስጥ የሚገኘው ፅሁፍ እንደሚያወሳው፣ ዘውዴ ረታ ነሐሴ 7 ቀን 1927 ዓ.ም እዚሁ አዲስ አበባ ውስጥ መወለዳቸውን ታሪካቸው ያወጋል። ከ1933 ዓ.ም እስከ 1945 ዓ.ም ድረስም ቀድሞ ደጅአዝማች ገብረማርያም ይባል በነበረውና ኋላ “ሊሴ ገብረማርያም” ተብሎ በተሰየመው የፈረንሳይ ት/ቤት የመጀመሪያውንና የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን አከናውነዋል።


ዘውዴ ረታ ገና የ17 አመት ወጣት እያሉ ሶስት ቴያትሮችን ጽፈው ለመድረክ አብቅተዋል። እነዘህም

1-እኔና ክፋቴ

2- ፍቅር ክፉ ችግር

3- የገዛ ስራዬ

የተሰኙ ናቸው። በነዚህ ቴያትሮች ጭብጥና አጻጻፍ የተነሳ ተሰጥኦ ያለው ጸሐፊ መጣ ተብሎ ልዩ እንክብካቤና ድጋፍ ይደረግላቸው ጀመር።

ዘውዴ ረታ፣ ከ1945 ዓ.ም እስከ 1948 ዓ.ም በጋዜጣና ማስታወቂያ መሥሪያ ቤት፣ የቤተ-መንግሥት ዜና ጋዜጠኛና በራዲዮ ዜና አቅራቢነት ሠርተዋል። ከዚያም ከ1948 ዓ.ም እስከ 1952 ዓ.ም ድረስ በፓሪስ “ECOLE SUPERIEURE DE JOURNALISM DE PARIS” የጋዜጠኝነት ትምህርት በማጥናት በዲፕሎማ ተመርቀዋል። ከትምህርታቸው መጠናቀቂያ በኋላ ከ1952 ዓ.ም እስከ 1954 ዓ.ም የኢትዮጵያ ድምጽ ጋዜጣና የመነን መጽሔት ዳይሬክተር ሆነው ሰርተዋል። ቀጥሎም ከ1954 እስከ 1955 ዓ.ም ለአንድ ዓመት የኢትዮጵያ ራዲዮ ብሔራዊ አገልግሎት ዳይሬክተር ሆነው ሰርተዋል። ከ1955 ዓ.ም እስከ 1958 ዓ.ም ደግሞ የኢትዮጵያ ወሬ ምንጭ ዋና ዳይሬክተር ነበሩ። ከ1958 ዓ.ም እስከ 1960 ዓ.ም የማስታወቂያ ሚኒስቴር ረዳት ሚኒስትር ሆነው ሰርተዋል። በኋላም ከ1960 ዓ.ም እስከ 1962 ዓ.ም ድረስ ደግሞ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ድርጅት ዋና ሥራ አስኪያጅ በመሆን አገልግለዋል። ከ1956 ዓ.ም እስከ 1962 ዓ.ም የፓን አፍሪካ ኒውስ ኤጀንሲ ማኅበር ፕሬዝደንት ሆነው ሰርተዋል። ከ1962 ዓ.ም እስከ 1967 ዓ.ም ድረስ ወደ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ተዘዋውረው በሦስት ዘርፎች አገራቸውን አገልግለዋል። እነዚህም የሚከተሉት ናቸው፡


1ኛ. በፓሪስ የኢትዮጵያ ኤምባሲ ሚኒስትር ካውንስለር

2ኛ. የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ም/ሚኒስትር

3ኛ. በሮም እና በቱኒዚያ የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት አምባሳደር ሆነው ሰርተዋል።

አምባሳደር ዘውዴ ረታ፣ በቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዘመነ መንግሥት የሃያ ሁለት ዓመታት አገልግሎት ካበረከቱ በኋላ፣ በደርግ ዘመን ከ1967 ዓ.ም ጀምሮ ስደተኛ ሆነው በአውሮፓ በቆዩበት ዘመን፣ በሮም የኢንተርናሽናል ድርጅት ውስጥ (IFAD) ለአሥራ ሦስት ዓመታት በፕሮቶኮልና በመንግሥታት ግንኙነት ጉዳይ ኃላፊ ሆነው ሠርተዋል።


በ1959 ዓ.ም ከባለቤታቸው ከወ/ሮ ገሊላ ተፈራ ጋር ተጋብተው ሦስት ልጆችንም ማለትም አያልነሽን፣ ቤተልሄምን እና ገብርኤል በጋራ አፍርተው ይኖሩ እንደነበር የሕይወት ታሪካቸው ያወሳል።


አምባሳደር ዘውዴ ረታ፣ ከንጉሠ ነገሥቱ መንግሥት የምኒልክ የመኮንን ደረጃና የኢትዮጵያ የክብር ኮከብ አዛዥ መኮንን ኒሻን ተሸላሚም ነበሩ። ከዚህ ሌላም ከአፍሪካ፣ ከእስያና ከአውሮፓ በድምሩ ከሃያ ሁለት አገሮች የታላቅ መኮንን ደረጃ ኒሻኖችን የተሸለሙ ኢትዮጵያዊ ናቸው።


አምባሳደር ዘውዴ ረታ ገና በወጣትነታቸው ዘመን ማለትም ከ1945 ዓ.ም ላይ ሁሉ ወደ አራት የመድረክ ቴአትሮችን ጽፈው ለሕዝብ ያሳዩ የሥነ-ጽሁፍ እና የዲፕሎማሲ ሰው ናቸው። በፀባያቸውም ትሁት፣ ይህን ሠርቻለሁ ብለው ልታይ፣ ልታይ የማይሉ በተፈጥሯቸው ድብቅ ናቸው።

አምባሳደር ዘውዴ ረታ፣ የአንድ ስርዓተ-መንግሥትን ማለትም የቀዳማዊ ኃይለሥላሴን ዘመን ታሪክ፣ ከውስጥ ሆነው ያዩትን እና የኖሩትን እንዲሁም ደግሞ የተለያዩ ሰነዶችን በማገላበጥ እና ሰዎችን በመጠየቅ ለትውልድ ታሪክ በማስተላለፋቸው የወርቅ ብዕር ተሸላሚ ሆነዋል።
***************
ምንጭ:-- http://www.sendeknewspaper.com/በጥበቡ በለጠ
********************************************************************************

ዘውዴ ረታ – የታሪኩ ቀንድ ስብራት

 

‹… ዘውዴ! ከእኛ ጋር ተመሳሳይ ከሆነው ትውልድ መካከል እንደ አንተ የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴን መንግሥት አመራር በቅርብ የማየትና የመረዳት ዕድል ያገኘ ብዙ ሰው የለም፡፡ ቀጥሎ ደግሞ ያየውንና የተረዳውን፣ ጣዕም ባለው ጽሑፍ አብራርቶ ለመግለጽ ተሰጥኦ ያለው እንደ አንተ የመሰለ ጸሐፊ ብዙ የለም፡፡ ስለዚህ በእኔ አመለካከት ሁለት የተጣመሩ ዕድሎች በአንተ እጅ ተይዘው ይገኛሉ፡፡ እነዚህም ታሪኩን የማወቅና የጽሕፈት ችሎታህ ናቸው፡፡ ስለዚህ እኔ አጥብቄ አደራ የምልህ የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴን መንግሥት ጉዳይ አንተ ዕድል አጋጥሞህ ያየኸውንና ከአዋቂዎች ዘንድ ቀርበህ ያጠናኸውን እውነተኛውን ታሪክ ገልጠህ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ጻፍለት፡፡ ለዚህ ሕዝብ ከአንተ በኩል ከዚህ የበለጠ የምታደርግለት ሊኖር አይችልም፡፡ አንተም አስበህ የጀመርከውን ለመፈጸም እግዚአብሔር ይርዳህ፡፡ … እኛም ወዳጆችህ፣ ዕድሜና ጤና አግኝተን የምትደክምበትን ለማንበብ ያብቃን…››
ከአሥራ ሁለት ዓመታት በፊት ነበር ታዋቂው የታሪክ ምሁር ፕሮፌሰር መርዕድ ወልደ አረጋይ የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ መንግሥት አመራርን በቅርቡ የማወቅ ዕድል ለነበራቸው፣ ከእልፍኝ እስከ አደባባይ ከንጉሠ ነገሥቱ ያልተለዩትን ዘውዴ ረታን እውነተኛው ታሪክ ገልጠህ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ጻፍለት ብለው የተማፀኗቸው፡፡
ይህን የማበረታቻ ምክር መቼም ያልረሱት ዘውዴ ረታ አምና እጅግ ግዙፍ የሆነውን ‹‹የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ መንግሥት›› አንደኛ መጽሐፍ ከነገሡበት 1923 እስከ 1948 ዓ.ም. ድረስ የሚሸፍነውን ታሪክ ለንባብ አደባባይ ያዋሉት፡፡
የአዲሱ መጽሐፋቸውንም የተለየ ፋይዳም እንዲህ አስቀምጠውታል፡፡ ‹‹እንግዲህ ማንም ሰው በቀላሉ እንደሚረዳው ኢትዮጵያ የነፃነት ችግር ያጋጠማት በሁለት ኮሎኒያሊስት በሆኑ አገሮች ነው፡፡ የመጀመሪያው የፋሽስቱ የሙሶሊኒ የግፍ ወረራ ሲሆን፣ ሁለተኛው ደግሞ ነፃ አውጪዎች ነን ብለው በመጡት ወዳጆቻችን በምንላቸው በእንግሊዞች ወታደራዊ የሞግዚት አስተዳደር የተፈጸመብን በደል ነው፡፡ ከእነዚህ ከሁለቱም ኮሎኒያሊስቶች የኢትዮጵያን ነፃነት ለማስመለስ የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ መንግሥት የደረሰበት መከራና ፈተና በቀላሉ የሚገመት አይደለም፡፡ ይህን ሁሉ በተለይ አዲሱ ትውልድ እንዲያውቀው ስለሚያስፈልግ፣ በዚህ መጽሐፍ ውስጥ ታሪኩ በተቻለ መጠን ተዘርዝሮ ቀርቦለታል፡፡››
ጋዜጠኛ፣ ዲፕሎማትና ስመጥር የታሪክ ጸሐፊ (ሦስት ዓይና) የነበሩት አምባሳደር ዘውዴ ረታ በዘመናዊት ኢትዮጵያ ታሪክ ከዳግማዊ አፄ ምኒልክ ዕረፍት በኋላ የነበረውን የልጅ ኢያሱን፣ የንግሥት ዘውዲቱ፣ ብሎም የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዘመን ታሪክ ትክክለኛውን ሒደት የዘመኑም ሆነ መጪው ትውልድ ማወቅ ያስፈልጋል በሚል ነበር የታሪክ መጽሐፋቸውን ‹‹ተፈሪ መኰንን ረዥሙ የሥልጣን ጉዞ›› ለኅትመት ያበቁት፡፡ ‹‹በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት የኤርትራ ጉዳይ 1941-1963›› ሌላው በመረጃና በማስረጃ የተደገፈ ታሪካዊ መጽሐፍንም እነሆ ብለዋል፡፡
የኤርትራን ጉዳይ የተመለከተው መጽሐፋቸው ዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ እንዲገነዘበው በዶ/ር ኃይሉ ሃብቱ አማካይነት “THE ERITREAN QUESTION” በሚል ተተርጉሞ ለሕትመት ዝግጁ መሆኑም ይነገራል፡፡
የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴን ሕገ መንግሥቱ ከተሻሻለበት ከ1948 ዓ.ም. በኋላ የነበረውን በለውጥ የታጀበው ዓቢይ ዘመን የሚያወሳውን መጽሐፍ በማዘጋጀት ላይ ነበሩ አምባሳደር ዘውዴ ረታ፡፡ በተለይ በለንደን (እንግሊዝ)፣ ፓሪስ (ፈረንሣይ) እና ሮም (ኢጣሊያ) ኢትዮጵያን የሚመለከቱ ስለ ዘመነ ኃይለ ሥላሴ የሚያወሱ ሚስጥራዊ ሰነዶች በቅርቡ ክፍት መሆናቸውን ተከትሎ፣ ጥናትና ምርምር ለማድረግ ነበር መስከረም 12 ቀን 2008 ዓ.ም. ወደ ባሕር ማዶ ያቀኑት፡፡ ያለሙት የዘመናት ሕልም እውን ሳያደርጉት ተቀጨ እንጂ፡፡ ሞት ቀደማቸው፡፡ የጥናታቸው ቀዳሚ መነሻ ባደረጉት ለንደን ከተማ መስከረም 26 ቀን 2008 ዓ.ም. በድንገት አርፈዋል፡፡
በኢጣሊያና በቱኒዚያ የኢትዮጵያ አምባሳደር ሆነው ያገለገሉት አቶ ዘውዴ ረት የተወለዱት በአዲስ አበባ ከተማ በ1927 ዓ.ም. ነው፡፡ የመጀመሪያና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን የተከታተሉት በፊት ደጃዝማች ገብረ ማርያም የአርበኞች ትምህርት ቤት በሚባለው፣ ከዚያም ሊሴ ገብረ ማርያም በተባለው ትምህርት ቤት ነበር፡፡ በኢትዮጵያ ሬዲዮ አንባቢነትና በቤተ መንግሥት ዜና አቅራቢነት ተቀጥረው ያገለገሉ ሲሆን፣ በፈረንሣይም በጋዜጠኝነት ተመርቀዋል፡፡ በኢትዮጵያ ድምፅ ዕለታዊ ጋዜጣና ወርኃዊው መነን መጽሔት ዳይሬክተርም ነበሩ፡፡ የኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የፓን አፍሪካን ኒውስ ኤጀንሲ ፕሬዚዳንት፣ የማስታወቂያ ረዳት ሚኒስትር፣ የውጭ ጉዳይ ምክትል ሚኒስትርም ነበሩ፡፡ በዘመነ ደርግ የስደት ዘመናቸውም በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት ውስጥ በዓለም አቀፍ የእርሻ ልማት ፈንድ የመንግሥታት ግንኙነትና የፖለቲካ ኃላፊ ሆነው ለ13 ዓመታት አገልግለዋል፡፡
ሦስት ዓይናው ዘውዴ ረታ በኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት መንግሥት ለሃያ ሁለት ዓመት በላይ ላበረከቱት ውጤታማ ተግባር ከንጉሠ ነገሥቱ መንግሥት የምኒልክ የመኰንን ደረጃና የኢትዮጵያ የክብር ኮከብ አዛዥ መኰንን ኒሻን ተሸልመዋል፡፡ ከተለያዩ አገሮችም ኒሻኖችን የተሸለሙ ሲሆን፣ ከቅርብ ዓመታት ወዲህም በባሕር ማዶና በአገር ውስጥም ልዩ ልዩ ሽልማቶች ተበርክተውላቸዋል፡፡
ከ49 ዓመት በፊት ከወይዘሮ ገሊላ ተፈራ ጋር ጋብቻ መሥርተው ሦስት ልጆች ያፈሩት አምባሳደር ዘውዴ አስከሬን፣ በሳምንቱ መገባደጃ ከእንግሊዝ መጥቶ ሥርዓተ ቀብራቸው በአዲስ አበባ እንደሚፈጸም ከቤተሰቦቻቸው የተገኘው መረጃ ያመለክታል፡፡
****************************************************
ምንጭ:-- ሪፖርተር ተጻፈ በ ሔኖክ ያሬድ

 

ዓርብ, ኤፕሪል 03, 2015

ባሻ አሸብር በአሜሪካ

 

ደማሙ ብዕረኛ መንግስቱ ለማ

**************************

የዛሬ አስር አመት በታላቅ ሹመት                           
አሜሪካ ልኮኝ ነበረ መንግስት
ዋሽንግተን ገብቼ ዋልኩ አደርኩኝና
ሽር ሽር ስል ሳለ ባንድ አውራ ጎዳና
አላፊ አግዳሚውን ጥቁሩን ነጩን
ሳለ ስመለከተው በኢትዮጵያዊ አይን
የውሀ ጥም ደርሶ ስላረገኝ ቅጥል
ከመንገድ ዳር ካለች ካንድ ትንሽ ሆቴል
ጎራ አልኩና ገና ከወንበር ላርፍ ስል
ተንደርድሮ መጣ የሆቴሉ ጌታ
አማረው ቋመጠ ከጀለው ሊማታ
አብዷል ሰክሯል እንዴ ምንድን መሆኑ ነው
በል ንካኝ በዱላ ግንባርህን ላቡነው
ብዬ ስነጋገር ሰምቶ ባማርኛ
አሳላፊው ሆነ አስታራቂ ዳኛ
ለጥ ብሎ እጅ ነሳና እንደሀገራችን ህግ
አክብሮ ጠየቀኝ ምን እንደምፈልግ
እኔም ጎራ ያልኩንት የሚጠጣ ነገር
ለመሻት መሆኑን ነግሬ ከወንበር
ይቅርታዎን ጌታ አዝናለሁ በጣሙ
ምናምኒት የለም በከንቱ አይድከሙ
አለና እጅ ነሳኝ ሳቁን እየቻለ
“ውሀም የለ?” ብለውማ በሳቅ ገነፈለ
ቤቱን የሞላው ሰው ሁሉም አጨብጭቦ
ብራቮ! ተባለ ብራቮ! ብራቮ!
 በጣም ተገርሜ ደንቆኝ አየሁት
ከዘራዬን ይዤ ሄድኩኝ ወጣሁት
ሃሣብ ገብቶኝ ደጅ ሳሰላስል ቆሜ
ያን ቂዛዛ መስኮት ባስተውለው አግድሜ
አራዳ ግሪኮች እንደሚሸጡት
ያለ በያይነቱ አየሁኝ ብስኩት
ትዝ አለኝ “አራዳ አዲስአባ ሆይ
ሀገርም እንደሰው ይናፍቃል ወይ?”
አስጎመጀኝ በሉ ሳይርበኝ ጠግቤ
አስተውለው ጀመረ መስኮቱን ቀርቤ
የምገዛውንም በልቤ ቆጥሬ
ዳግም ልገባ ስል በስተበሩ ዞሬ
ዞወር ብዬ አያለሁ የሆቴሉ ጌታ
ወገቡን በጁ ይዞ እንደሚል እስክስታ
ተኩሮ ያየኛል ወደኔም ተጠጋ
“ስንት ነው ወዳጄ ያንዱ ብስኩት ዋጋ?”
የያዘው አባዜ ብሎት አላናግር
አይኑ ደም ለበሰ ይጉረጠረጥ ጀመር
አለም ሁሉ ያውቃል መሆኔን ታጋሽ
ትዕግስቴ አሁን አልቋል ጥፋ ብረር ሽሽ
አገጭህን በቦክስ አሁን ሳላፈርሰው
ይህን ጎረጥ አይንህን እዚህ ሳላፈሰው
ከሱቄ መግባትህ አንሶህ አሁንስ
መስኮቴ ስር ደግሞ ልትልከሰከስ
ገበያ አላገኝም ደንበኞቼም
አንተን እዚህ ካዩ ዳግመኛ አይመጡም
ስራ ስራ እኮ ነው አየገባህም እንዴ
ወግድ አትገተር ይቋረጣል ንግዴ
ይህንን እንዳለ ቁጣው ጠና ጋለ
አገጭ እና ጉንጬን በቡጢ ነደለ
በቦክስ አይለኝም መልሶ መልሶ
እስኪሸረፍ ድረስ ጥርሴ በደም ርሶ
ዠለጥ አደረኩት በያዝኩት ከዘራ
ግን አልጠቀመውም ዘበኛ ተጣራ
ፖሊስ ቢሮ ሄድን እርሱ ተለቀቀ
አሸብር ከልካይ ግን ወህኒ ማቀቀ
ማን ሊሰማኝ እዛ ዘሬን ብቆጥር
ብሸልል ባቅራራ ወይም ብፎክር
ደረቴ ላይ ያለው የሀገሬ ባንዲራ
ያምራል ተባለ እንጂ ከብሮም አልተፈራ
የሞጃው ተወላጅ የጠራሁት መንዤ
ሸጎሌ ሻንቅላ ተብዬ መያዜ
የግፍ እንደሆነ የውሸት ሀሰት
አቃተኝ ማንንም ከቶ ማስረዳት
ሲቸግረኝ ጊዜ አንዱን ተጠግቼ
ሻንቆን እንዲህ አልኩት ነገሬን አስልቼ
ሰማኸኝ ወንድሜ አላሳዝንህም?
በሰው ጠብ ገብቼ በከንቱ ስዳከም
አውቃለሁ ከጥንቱ ነጭ እና ሻንቅላ
በቂም እንደኖረ ሲዋጋ ሲጣላ
እኔ ግን ሀበሻው ምን ወገን ልለይ
በማይነካኝ ነገር ለምን ልሰቃይ
እንካ ፀጉሬን እየው ሸጎሌ አይደለሁም::
********************************
ምን ጭ-:http://www.ethiopiaobserver.com/mengistu-lemma-reads-basha-ashebir-be-america/

ዓርብ, ማርች 27, 2015

አዛዥ ሐኪም ወርቅነሕ እሸቴ(ዶ/ር ማርቲን)!!

(በኢትዮጵያ የመጀመሪያው ሐኪም)
**************************************

በኢትዮጵያና በእንግሊዝ መካከል በኖረው ታሪክ መቸም ቢሆን በማይዘነጋው የመቅደላው ግብግብ በወራሪው ወታደሮች ሳይቀር በሚገባ የተወደሰው የመይሳውን የክብር አሟሟት ባስገኘልን ልዕልና ፋንታ ከዚሕ አስደናቂ ታሪክ ጀርባ በደንብ ያልተነገሩ ብዙ እውነቶች በመኖራቸው አቅም በፈቀደ ታሪካችንን ከያለበት እያሳደድን ማቅረባችንን ስንቀጥል ክብር ይሰማናል….በዚሕ የአጭር አጭር ወግ ሁልጊዜም ቢሆን በቁጭት ከሚያንገበግበን የልዑል ዓለማየሁ ስደትና ሞት ጋር የሚዛመድ የአንድ ታዋቂ ኢትዮጵያዊ ግለ ታሪክ በወፍ በረር ልንቃኝ እድል ቀናን………..በአጼ ቴዎድሮስ የመጨሻዎቹ የሥልጣን ዓመታት በውስጥ ፖለቲካ ምክንያት በመቅደላ አምባ ለእስር የሚጋዙ በርካቶች ነበሩ….ከእነዚሕም መካከል የዛሬው ባለታሪካችን እናትና አባት ነጋድራስ እሸቴና ወ/ሮ ደስታ ወልደማርያም ይገኙበታል…..በ1857 ዓ/ም በጎንደር ከተማ የተወለዱት ወርቅነሕ ገና የሦስት ዓመት ጨቅላ ሳሉ ከወላጆቻቸው ጋር በመቅደላ አምባ ለእስር መደረጋቸው ምን አልባትም የወደፊቱን እጣ ፈንታቸውን ያደላደለ አጋጣሚ መፍጠሩ አልቀረም……በ1860 ዓ/ም የእንግሊዝ ጦር መቅደላን ሲይዝ በተፈጠረው እረብሻ የሞተው ሞቶ የተቀረው እግሬ አውጪኝ ሲል ከተገኙት ሕጻናት መካከል የአጼ ቴዎድሮስ ልጅ ልዑል ዓለማየሁና ሕጻን ወርቅነሕ በእንግሊዝ ወታደሮች ተማርከው ከወራሪው ጦር ጋር ጉዞ ጀመሩ………ከባሕር ወደብ ሲደርሱ ልኡል ዓለማየሁና ሕጻን ወርቅነሕ ሊለያዩ ግድ ሆነ....... ሮበርት ናፔር ልዑል ዓለማየሁን ይዞ ወደ እንግሊዝ ሲያቀና ሕጻን ወርቅነህ ግን ከኮሌኔል ቻርለስ ቻምበርሊን ጋር በመሆን በወቅቱ በእንግሊዝ ቅኝ ግዛት ስር ወደ ነበረችው ሕንድ ተጉዋዙ………
ሕጻን ወርቅነሕ በሕንድ አገር ለአራት ዓመት እንደተቀመጡ አሰዳጊያቸው ቻርለስ በሞት ስለተለዩ ኮለኔል ማርቲን የተባለው ሰው ተቀብሎ ከአንድ የሚሽን ትምህርት ቤት ገብተው ትምሕርት እንዲቀጥሉ አደረገ…ብሩሕ አእምሮ የነበራቸው ወርቅነሕ የመጀመሪያና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን ፑጃብ በምትባለው ከተማ ተከታትለው ሲጨርሱ ለዩኒቨርሲቲ የሚያበቃ ውጤት ስለበራቸው በፑንጃብ ዩኒቨርሲቲ የሕክምና ትምህርት ለማጥናት ተመዘገቡ…ከዩኒቨርሲቲ ቆይታቸው ጎበዝ ተማሪ እንደነበሩ የሚነገርላቸው እኝህ ሰው የሕክምና ትምህርታቸውን በሚገባ አጠናቀው ከተመረቁ በዛው በህንድ አገር እረዳት የቀዶ ጥገና ሀኪም በመሆን ለሁለት ዓመት አገለገሉ…..በሕንድ የሁለት ዓመት አገልግሎት ከሰጡ በኋላ ከፍተኛ የህክምና ትምህርት ለመከታታል እ.ኤ.አ በ1889 ዓ/ም ወደ እንግሊዝ አቀኑ……በዛም በኤደንብራና በግላስኮው ዩኑኒቨርሲቲ ሕክምና ተምረው በቀዶ ጥገና ሙያ በታላቅ ማዕረግ ተመረቁ…….በዩኒቨርሲ ቆይታቸው ባስመዘገቡት ከፍተኛ ውጤት የሀኪሞች ማሕበር ‘’የበቃ ጥቁር ሀኪም ‘’ የሚል ሽልማት የተበረከተላቸው ሀኪም ወርቅነሕ እ.ኤ.አ በ1891 በሀኪምነት ተመድበው በወቅቱ በሕንድ ግዛት ስር ስትተዳደር ወደነበረችው ወደ በርማ ተላኩ…….በርማ እያሉ ወደ ኢትዮጵያ ለመምጣት የተለያዩ ጥረቶች ሲደርጉ ቆይተው በአጼ ሚኒሊክ በተደረገላቸው ጥሪ መሰረት በ1891 ዓ/ም በልጅነት የተለዪዋት አገራቸውን ለማየት በቁ ከቀሪ ዘመዶቻቸውም ጋር ተዋወቁ…….ለመጀመሪያ ጊዜ ወደ አገራቸው ከተመለሱ በሁዋላ የተለያዩ አገልግሎቶችን ሲሰጡ ቆይተው በ1895 ዓ/ም እንደገና ወደ እንግሊዝ የተመለሱ ሲሆን ከዛን ወዲሕ በተለያዩ ጊዜያት ወደ አገራቸው በመምጣት የተለያዩ በተግባራትን ያከናወኑ ሲሆን ለሁለተኛ ጊዜ በመጡበት ወቅት ከወ/ሮ ቀፀላ ወርቅ ቱሉ ጋር ትዳር የመሠረቱ ሲሆን ትዳራቸው ሰምሮ አምስት ወንዶችና ስምት ሴት ልጆችን አፍርተዋል…….
በሕንድ አገር በሕክምና ሙያቸው አንቱታን ያተረፉት እኝሕ ሰው በተለይ በበርማ ከሕክምና ዳይሬክተርነት አንስቶ እስከ ከፍተኛ የመንግስት ባለስልጣን በደረሱበት አገልግሎት ከፍተኛ ተወዳጅነትን እና ከበሬታን አትርፈዋል…..በሕንድና በበርማ ለ32 ዓመታት አገልግሎት ከሰጡ በሁዋላ በ1919 ዓ/ም ጠቅልለው ወደ ሀገራቸው ተመለሱ…….ሀኪም ወርቅነሕ .ወደ አገራቸው ከተመለሱ በሁዋላ ፋሺስት ኢትዮጵያን እስከወረረበት ድረስ በተለያዩ ሥራዎች ላይ ተሳትፈዋል ከእነዚሕም መካከል በአዲስ አበባ የሚገኘውን የፍልውሀ ድርጅት አቋቁመዋል፣ የተፈሪ መኮንን ትምህርት ቤት ዳይሬክተር ሆነው ሰርተዋል፣ የየካቲት 12 ሆስፒታል(የቀድሞው ቤተሳይዳ)፣ የጅማ መንገድ እና የብርሀንና ሰላም ማተሚያቤት ሲቆሙ የበላይ ተቆጣጣሪ ሆነው ሰርተዋል፣ በ1927 ዓ/ም በአባይ ወንዝ ላይ ለሚገነባው ግድብ እርዳታ ለማሰባሰብ ወደ አሜሪካ የተጉዋዘውን ቡድን መርተዋል ፣ በ1920 ዓ/ም ለቆመው ዘመናዊ ፍርድቤት አዛዥ ተብለው በተሰጣቸው ሹመት በቅንነት አገልግለዋል፣ የጨርጨር አውራጃ ገዢ በመሆን የሰሩ ሲሆን ኢትዮጵያ በነበረባት የተማረ የሰው ኃይል እጥረት የተለያዩ ሙያ ያላቸው 21 ህንዳውያን ወደ ኢትዮጵያ መጥተው እንዲሰሩ ከፍተኛ ሚና ተጫውተዋል…….በ1927 በጄኒቫ የመንግስታቱ ማሕበር የኢትዮጵያ ተጠሪ ሆነው የተላኩት ሀኪም ወርቅነሕ በዛው እያሉ ኢትዮጵያ በፋሺስት እጅ በመውደቋ ወደ እንግሊዝ በማቅናት ከንጉሱ ጋር በመሆን የተለያዩ የዲፐሎማሳዊ ሥራዎችንና በማከናወን በፋሺስት ወረራ ምክንያት ጉዳት የደረሰባት አገራቸውን ለመርዳት የሚያስችሉ ዝግጅቶችን በማደራጃት በወቅቱ ከኢትዮጵያውያንና ከኢትዮጵያ ወዳጆች ከፍተኛ እርዳታ እንዲገኝ ሚና ተጫውተዋል……በዚሕ ድርጊታቸው የተቆጣው ፋሺስት አዲስ አበባ ሲኖሩ የነበሩ የሴፍና ቢንያም የተባሉ ልጆቻቸውን ቢገሉባቸውም በአላማቸው ጸንተው ኢትዮጵያ ከፋሺስት ቀንበር ነጻ እስክትወጣ የተቻላቸውን ሁሉ አደረጉ…..ከነጻነት በሁዋላ በ1934 ዓ/ም በ77 ዓመታቸው ወደ አገራቸው የተመለሱት ሀኪም ወርቅነህ በሽምግልና ዘመናቸው ሳይቀር በሙያቸውና በሌሎች አገልግሎቶች ሁሉ በመሳተፍ የዜግነት ግዴታቸውን ተወጥተዋል……..በመቅደላ አምባ ላይ የተጀመረው የኝህ ሰው አስደናቂ የሕይወት ጉዞ ጥቅምት 11 ቀን 1945 ዓ/ም ሲል በሞት ተደመደመ……አዲስ አበባ በሚገኘው የየካው ሚካኤል ቀብራቸው ሲፈጸም ብዙ ኢትዮጵውያን በቦታው ተገኝተው ሽኝት አረጉላቸው፡፡
*********************************************************************************
 ምንጭ-: This Day in Ethiopian History facebook page

ማሞ ካቻ (አቶ ማሞ ይንበርብሩ)

  አቶ ማሞ ይንበርብሩ (ማሞ ካቻ) እስቲ እናስታውሳቸው፣ ተቀብሮ እንዳይቀር አኩሪ ታሪካቸው  (ደረጀ መላኩ)   አቶቢሲ ማሞ ካቻ የት ትሄዳለህ? ገብረ ጉራቻ… ታዳጊው ማሞ ይንበርበሩ ገና በጨቅላ እድሜው አባቱ አቶ...