ቅዳሜ, ዲሴምበር 22, 2012

ሞክሼ የአማርኛ ፊደላት እና የባለሙያዎች ማብራሪያ

ክፍል አንድ

የፊደል ዘር ይጠበቅ ባህሉም ይከበር
በፊታውራሪ አበበ ሥዩም ደስታ
በፊደሎቻችን ላይ ሦስት ሀ - ሐ - ኀ፣ ሁለት አ - ዐ -፣ ሁለት ሠ - ሰ ሁለት፣ ጸ - ፀ አሉ፡፡ እነዚህ ፊደሎች የራሳቸው የሆነ የስም አጠራርም አላቸው፤ ሀሌታው ሀ፣ ሐመሩ ሐ፣ ብዙኃን ኀ፣ ንጉሡ ሠ፣ እሳቱ ሰ፣ ጸሎት ጸ፣ ፀሐዩ ፀ ይባላሉ፡፡ በጽሑፍ የሚገቡበትን ተገቢ (ተስማሚ) ቦታም አላቸው፡፡ ለምሳሌ በሁለት ፊደሎች መጠቀም ይቻላል፡፡ ሀገር አገር ይህ ትክክለኛ አጻጻፍ ሲሆን፤ ነገር ግን ከዚህ ውጪ ሐገር፣ ኀገር ብሎ መጻፍ ግን ስሕተት ይሆናል፤ የሚከተሉትን ደግሞ እንመልከት፤

ሕገ መንግሥት፣ ሕገ ወጥ፣ ሕዝብ፣ ሕብረት፣ ዓቃቤ ሕግ፣ ወዘተ. የመሳሰሉት አጻጻፋቸው ትክክል ነው፡፡ ከዚህ ልማዳዊ አሠራር ውጪ ህገ መንግሥት፤ ህገወጥ፤ ህዝብ፤ ህብረት፤ አቃቤ ህግ ስሕተታዊ አጻጻፍ ይሆናል፤ ሌላ ማስረጃ ቢፈለግ፤ ኃይለሥላሴ የሚለው ስም ሦስት የተለያዩ ፊደሎች ይዟል፡፡ የመጀመርያው ፊደል ብዙኀን - ኃ - ሲሆን፣ ከንጉሡ -ሥ- ሳድስ፣ ከእሳቱ -ስ- ሃምስን በመጻፍ እንዲካተት ተደርጓል፡፡ ሀይለ ስላሴ ብሎ ቢጻፍ ግን የፊደሎቻችን የአጻጻፍ ሥርዓት ማፋለስ ይሆናል፤ በአቦ ሰጡኝ ፊደሎቻችን አለቦታቸው መግባትም፣ መጻፍም የለባቸውም፡፡

በዓፄ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት በማስታወቂያ ሚኒስቴር ረዳት ሚኒስትር የነበሩት የተከበሩ ብላታ ወልደ ጊዮርጊስ ወልደ ዮሐንስ የቅድሚያ ዓይነተኛ ሥራቸው የፊደሎች ዘሮች አለቦታቸው እንዳይጻፉ መጠበቅ ነበር፤ በዚያን ወቅት ተማሪ ሁኜ አልፎ አልፎ በጋዜጣ እንዲወጣልኝ አንድ አንድ ሐሳብ በማመንጨት እጽፍ ስለነበር ብዙ ጊዜ አርመውኛል፡፡

ከእሳቸው በተማርኩት ትምህርትና ባገኘሁት ልምድ አእምሮዬን አሻሽያለሁ፡፡ በቀድሞው የንጉሠ ነገሥቱ ዘመነ ሥርዓት የክፍል ሹም የመጀመርያ ሹመት ሆኖ ወደ ላይ እንደሚከተለው ይዘልቃል፡፡ ዲሬክተር ዋና ዲሬክተር፤ ረዳት ሚኒስትር ምክትል ሚኒስትር፣ ሚኒስትር ዲ-ኤታ፤ ሚኒስትር፡፡ ከምክትል ሚኒስትር ወደ ላይ ያሉት እስከ ሚኒስትር ማዕረግ የደረሱት ክቡር ይባላሉ፡፡ ከዚህ በታች ያሉትን ግን ክቡር አይባሉም፡፡ በተመሳሳይ ያሉትን ማለት ኮሚሽነሮች፤ ሌ/ጀኔራሎች፣ አምባሳደሮች ክቡር ይባላሉ፡፡ ሚኒስትሮች የነበሩ በዳሬክተርና በሥራ አስኪያጅነት ሥራ ቢመደቡ እንኳን የቀድሞውን የሚኒስትር ማዕረጋቸውና ክብራቸው አይቀነስባቸውም፡፡ ክቡር መባል አለባቸው፡፡ ሥርዓት ነውና፡፡ ይህንኑ መለመድ ይገባዋል፤ በወታደሩ ሹመት አሰጣጥ ግን ያለው ሥርዓት የተጠበቀ ስለሆነ መልካም ነው እላለሁ፡፡ ከዚሁ ሌላ የምለው አለኝ፡፡ ባሁኑ በኢሕአዴግ መንግሥት ዘመን አምባሳደር ነዋሪ የማዕረግ መጠሪያ ስም ሆኖአል፡፡ አንድ አምባሳደር የዲፕሎማሲውን ሥራ አቁሞ ሲዛወር ልክ በሥራው እንዳለ ተቆጥሮ “አምባሳደር” እየተባለ መጠራት የለበትም፡፡

ለምሳሌ በዓፄ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት አምባሳደርነት ተሹመው የነበሩት ክቡር አቶ ጋሻው ዘለቀ፣ ክቡር አቶ ዘነበ ኃይለ፣ ክቡር ልጅ መንበረ ያየህ ይራድ፤ ክቡር ፊታውራሪ መሐመድ ሲራጅ ብዙ ዘመን በአምባሳደርነት ሲሠሩ ቆይተው ተልእኮዋቸውን ፈጽመው ወደ አገራቸው ሲመለሱ አምባሳደር የሚል ቀርቶ በቀድሞ ስማቸው አቶ ተብለው ነበር የሚጠሩት፤ ይህንኑ ጠይቆ ለማረጋገጥ ይቻላል፡፡ ፊታውራሪ የነበሩትም፤ ፊታውራሪ ተብለው ይጠራሉ፡፡ ዘላቂ ሆኖ ከሰው ጋር ቅጽል የማዕረግ ስም ሆኖ የሚያገለግል ነው፡፡ በራሴ ምሳሌ ልውሰድ፤ ከግርማዊ ጃንሆይ በአዋጅ የተሰጠኝ የማዕረግ ስም ፊታውራሪ ነው፤ በዚህ ምድራዊው ዓለም እስካለሁ ድረስ የምጠራበት ሲሆን፣ ከሞትኩም በኋላ እጠራበታለሁ፡፡ እንዲሁም በንጉሠ ነገሥቱ መልካም ፈቃድ የሚሰጠው የሥልጣንና ማዕረግ ተዋረድ ባላምባራስ፣ ግራዝማች፣ ቀኛዝማች ፊታውራሪ፣ ደጀዝማች፣ ቢትወደድ፣ ራስ ቢትወደድ፣ ልዑል ራስ፣ አልጋ ወራሽ፣ ንጉሥ ንጉሠ ነገሥት ሲሆን፣ በሌላ በኩል ደግሞ ብላታ፣ ብላቴን ጌታ፣ ፀሐፊ ትዕዛዝ፣ ሊቀ መኳስ በሕይወት ሳሉ ይጠሩበታል፡፡ ከሞቱም በኋላ ስማቸውና ታሪካቸው በተነሣ ቁጥር ከመቃብር በላይ ሆኖ በማዕረጉ ስም ይጠሩበታል፡፡


አምባሳደር ግን የማዕረግ ስም መጠሪያ ስላልሆነ የዲፕሎማሲ ሥራቸውን ሲያቋርጡ አምባሳደር ተብለው ሊጠሩበት አይገባም፡፡ በሌላ መንግሥት የማይሠራበት ሲሆን የኢትዮጵያ መንግሥት ለብቻው በዚህ ስም አጠራር ሕጋዊ ማድረጉ ተገቢ አይመስለኝም፡፡ እንደ ማዕረግ በዘላቂነት ይጠሩበት ከተባለ እኔ ከማሳሰብ በቀር እምጎዳበት የለም፡፡ ከዚህ ጋር የማያይዘው ሌላም አለ፤ ከላይ በዝርዝር እንደገለጽኩት ባሁኑ ሰዓት ዲሬክተር ጄኔራል እየተባሉ አንዳንድ ሹማምንት ይጠሩበታል፡፡ በእኔ አስተያየት ዲሬክተር ጄኔራል ከማለት ይልቅ ዋና ዲሬክተር ቢባሉ ወይም ለስም አጠራሩ የሚቀል ስለሆነ ረዳት ሚኒስትር እየተባሉ ቢጠሩ መልካም ነው፡፡ በዚህ ቢታረም ያማረ ይሆናል፡፡

በማጠቃለያ የማቀርበው ሐሳብ በየዕለቱ እና በየሳምንቱ በሚታተሙ ጋዜጦች መጽሔቶች፣ መጻሕፍት የፊደሎቻችን ዘሮችና ልማዳዊ የአጻጻፍ ሥርዓቶች ይጠብቁ (ይከበሩ) በማለት ሐሳቤን እቋጫለሁ፡፡ እንዲሁም የኮምፒውተር ፀሐፊዎች ይህንኑ የአጻጻፍ ስልት (ፈለግ) ተከትለው ይጠቀሙበት በማለት መልእክቴን አስተላልፋለሁ፡፡ በተጨማሪም ደራስያን፣ አስተማሪዎች፣ ማተሚያ ቤቶች፣ ከያኒያን ይህንኑ እንዲተገብሩ ማድረግ የግል ኃላፊነት ስላለባቸው ትኩረት ይስጡበት እላለሁ፡፡

ሌላው መታረም የሚገባው፣ “ስፖርት” እየተባለ የሚጻፈው ነው፡፡ ምክንያቱም የአውሮፓ ፊደል ኤስ (S) የእ ፊደል ድምፅ ስላለው፣ Sport ቢጻፍ ትክክል ነው፤ የእኛው ፊደል (ስ) ግን ድምፁ የተዋጠ ስለሆነ እ ፊደል ተጨምሮበት “እስፖርት” ቢባል የተሻለ ነው፤ እንዲሁም ለርምጃ እርምጃ ቢባል፣ በኔ በኩል ጥሩ ስለሆነ ታስቦበት ቢታረም መልካም ይመስለኛል፡፡
***********************
ምንጭ:-- ሪፖርተር ጋዜጣ

 

እሑድ, ዲሴምበር 09, 2012

ተፅዕኖ ፈጣሪው ቀኝ ጌታ ዮፍታሄ ንጉሴ

“ሰውን ሰው ቢወደው አይሆንም እንደራስ ታመህ ሳልጠይቅህ መቅረቴን አትውቀስ ባውቀው ነው የመጣሁ እንደማልመለስ ይማርህ መሀሪው እስመጣ ድረስ”
/ዮፍታሄ ንጉሴ በቅድመ ፋሺስትና 
በድህረ ወረራ በርካታ ስራዎቻቸውን 
አበርክተው ላለፉት ብላቴን ጌታ ህሩይ ወ/ስላሴ 
ህልፈት የጻፉት የሀዘን እንጉርጉሮ ነበር፡፡/

“ጎነዛዚቴ ሆይ ወይ ቆነጃጅቴ
ምንኛ ነደደ ተቃጠለ አንዠቴ
እንመለሳለን ባዲሱ ጉልበቴ
እናንተም ተምርኮ እኔም ተስደቴ”
***************************************************************************
የአማርኛን ስነ ጽሁፍ ካሳደጉት ታላላቅ ኢትዮጵያዊያን መካከል ባለቅኔው ዮፍታሄ ንጉሴ ይጠቀሳሉ፡፡ ዮፍታሄ ንጉሴ የተወለዱት በጎጃም ክፍለ ሀገር በደብረ ኤልያስ በ1885 ዓ.ም ሲሆን በደብረ ኤልያስ ደብር የጥንቱን የኢትዮጵያ ቤተክርስትያን ትምህርት በሚገባ ተምረዋል፡፡ ዮፍታሄ በልጅነታቸው የዜማ ትምህርት ያስተማሯቸው መሪጌታ አደላ ንጉሴ ሲሆኑ የቅኔን ትምህርት ያስተማሯቸው የኔታ ገብረስላሴ ነበሩ፡፡ የኔታ ገብረስላሴ በደብረ ኤልያስ ደብር ታዋቂ የቅኔ መምህር ሲሆኑ ሁለተኛው ኢትዮጵያዊ ፓትርያርክ አቡነ ቴዎፍሎስን ቅኔ እንዳስተማሯቸው በታሪክ ይታወቃል፡፡ ደብረ ኤልያስ ደብር የ”ፍቅር እስከ መቃብር” ደራሲ ሃዲስ አለማየው የተማሩበት ደብር ነው፡፡
አቶ ሙሉጌታ ስዩም በ1964 ዓ.ም በቀዳማዊ ኃይለ ስላሴ ዩኒቨርስቲ በመመረቂያ ጽሁፉ ላይ እንደገለፀው፤ በደብረ ኤልያስ ደብር የነበሩ መምህራን “ማህበረ ኤልያስ” በሚል ስም እግረ ኤልያስ ብለው ደቀመዛሙርት ተማሪዎቻቸውን ይጠራሉ፡፡ በዮፍታሄ የዜማና የቅኔ ችሎታ መምህራኖቹ ከመደነቃቸው የተነሳ ለአምስት ተከታታይ ዓመታት እግረ ኤልያስ የሚለውን ምርጥ ስም ሰጥተውታል፡፡ ለዮፍታሔ ገና በልጅነቱ የአባቶችን ማእረግ ቀኝ ጌታ ሾመውታል፡፡
ቀኝ ጌታ ዮፍታሄ በ1911 ዓ.ም አዲስ አበባ እንደመጡ፣ ወዲያውኑ በአቦ ደብር በአጋፋሪነት፤ በመቀጠልም በደብረ አለቅነት ተሹመዋል፡፡ ከቤተክርስቲያን አገልጋይነት ቀጥለው በሊጋባ ወዳጆ ጽ/ቤት የጽሕፈት ስራ እየሰሩ ለተወሰነ አመት ቆዩ፡፡
በኋላም ዶክተር አምሳሉ አክሊሉ ባልታተመ ጥናታቸው እንደገለፁት፤ ቀኝ ጌታ ዮፍታሄ በዳግማዊ ሚኒሊክ ትምህርት ቤት በአስተማሪነት ተቀጥረው ልዩ ልዩ መዝሙሮችን እየደረሱ ማስተማር ጀመሩ፡፡ በቀድሞ ጊዜ ዳግማዊ ምኒሊክ ትምህርት ቤት ያስተምሩ የነበሩ መምህራን በየጊዜው በትምህርት ቤቱ ቅጥር ጊቢ ልዩ ልዩ ትያትሮች እየደረሱ ለተማሪዎች ያሳዩ ነበር፡፡ ይህም ሁኔታ የመዝሙር መምህሩን ዮፍታሄን ከቲያትር ጋር አስተዋወቃቸው፡፡ ዮፍታሄም አዳዲስ ትያትሮችን በተለየ አቅጣጫ መድረስ ጀመሩ፡፡
ቀኝ ጌታ ዮፍታሄ ንጉሴ ከደረሷቸው በርከት ያሉ ትያትሮች መካከል “አፋጀሽኝ”፣ “የሆድ አምላኩ ቅጣት”፣ “የደንቆሮዎች ትያትር”፣ “እርበተ ፀሐይ” እና “ጎበዝ አየን” ይጠቀሳሉ፡፡
የትያትር መምህሩና ተዋናዩ ተስፋዬ ገሰሰ በጥናታዊ ጽሁፋቸው እንደገለፁት፤ ዮፍታሄ ንጉሴ በድርሰት ችሎታቸው ብዙ የተመሰገኑ እና ከግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ስላሴ ብዙ ሽልማቶችን ያገኙ ነበር፡፡
ከጦርነቱ በፊት በመናገሻ ቅጥር ጊቢ ውስጥ የጊዮርጊስ ትምህርት ቤት ሲባል ከነበረው ቀበና ከሚገኘው ሊሴ ኃይለ ስላሴ ትምህርት ቤት፣ ከተፈሪ መኮንንና ከዳግማዊ ምኒሊክ ትምህርት ቤቶች ተማሪዎች ተመርጠው ልዩ ልዩ ትያትሮችን እያዘጋጁ ያበረክቱ ነበር፡፡ አቶ ሙሉጌታ ስዩም በጥናቱ እንደጠቆመው፣ አንድ ጊዜ ጃንሆይ ዮፍታሄን ትያትር በመመልከት ላይ እያሉ በጣም ከመደሰታቸው የተነሳ ከልዑል አልጋ ወራሽ አንገት ወርቅ አውልቀው፤ ለዮፍታሄ አድርገውላቸዋል፡፡
ቀኝ ጌታ ዮፍታሄ በርካታ የመድረክ ድርሰቶች አዘጋጅተው አሳይተዋል፡፡ ነገር ግን ድርሰቶቹ ባለመታተማቸው የተገኙት በጣም ጥቂቶች ናቸው፡፡ “ጎበዝ አየን” የሚባለው ድርሰታቸው የህትመት ብርሀን አይቷል፡፡
ለመድረክ ከቀረቡት ውስጥ የተመልካችን አድናቆት ያተረፈው “አፋጀሽኝ” የተባለው ድርሰታቸው ነው፡፡ ይሄን ድርሰት ዮፍታሄ የጀመሩት ከጣሊያን ወረራ በፊት ሲሆን ድርሰቱን የፈፀሙት ከወረራው በኋላ ነው፡፡
“አፋጀሽኝ” ድርሰት ምሳሌያዊ ሲሆን በወቅቱ የነበረውን የአለም ፖለቲካዊ አዝማሚያ የሚጠቁም ከመሆኑም በላይ በድርሰቱ ውስጥ የተመሰለችው እናት ሀገር ኢትዮጵያ በሚከጅሏት ዘንድ የነበራትን የፖለቲካ ሁኔታ የሚያሳይ ነው፡፡ “አፋጀሽኝ” ዋና ጭብጡ በጣሊያንና በኢትዮጵያ የነበረውን ጦርነት የሚያመለክት ነው፡፡ ይሄም የጊዜው አንገብጋቢ ፖለቲካዊ መልእክት ነበር፡፡ ድርሰቱ የዮፍታሄን ኪናዊ ችሎታ በቅጡ የሚያንፀባርቅ እንደሆነ ይነገርለታል፡፡
በኢትዮጵያ የድራማ ታሪክ የመድረክ ተውኔቶችን ካቀጣጠሉት ፈር ቀዳጆች መካከል በቅድሚያ የሚጠቀሱት በጅሮንድ ተክለሀዋርያትና እና ቀኝ ጌታ ዮፍታሄ ንጉሴ ናቸው፡፡
ዮፍታሄ የድራማ ሰው የነበሩትን ማቲዎስ በቀለን አስተምረዋል፡፡ “ሙናዬ ሙናዬ” የተሰኘው ዘፈን የዮፍታሄ ግጥም ሲሆን ዜማው በአገር ፍቅር ማህበር ይገኛል፡፡
ቀኝ ጌታ ዮፍታሄ ከተውኔት ድርሰታቸው በተጨማሪ መዝሙሮችንና ግጥሞችን ደርሰዋል፡፡ የኢትዮጵያ አንድነትና የህብረት መዝሙር የሚገልጽልንን የኢትዮጵያ ህዝብ መዝሙር (ተፈሪ ማርሽ)፣ ወላድ ኢትዮጵያ፣ አጥንቱን ልልቀመው፣ ድንግል አገሬ ሆይ የሚባሉ መዝሙሮችን ደርሰዋል፡፡ አጥንቱን ልልቀመው የሚለው ግጥም አርበኞቹን የዶጋሊውን አሉላ አባ ነጋ እና ራስ ጎበናን በማነፃፀር የገጠሙት ግጥም ሲሆን ድንግል ሀገሬ ሆይ የተሰኘውን ድርሰት የፃፉት በስደት ኢሊባቡር ሆነው በ1929 ዓ.ም ነበር፡፡ ይህ መዝሙር ከመጀመሪያ ረድፍ ከሚጠቀሱት ስራዎቻቸው ቀዳሚው ነው፡፡
ድንግል ሀገሩ ሆይ ጥንተ ተደንግሎ
ጥንተ ተደንግሎ ጥንተ ተደንግሎ
ህፃናቱ ታርደው ያንቺም ልብ ቆስሎ
ልጅሽ ተሰደደ አንቺን ተከትሎ
የህፃናቱ ደም አዘክሪ ኩሎ፡፡
አዝማች፤ አስጨነቀኝ ስደትሽ
እመቤቴ ተመለሺ እመቤቴ ተመለሺ
ይሄ ግጥም ዮፍታሄ ንጉሴ ህዝቡ በፋሺስት ወረራ የደረሰበትን ስደት የገለፁበት ስንኝ ነው፡፡ ቅድስት ድንግል ማርያም ከእስራኤል ወደ ግብጽ ያደረገችውን ስደት እና በኤሮድስ ህፃናት መቀላታቸውን ከኢትዮጵያ ስደት ጋር ያነፃፀሩበት ግጥምም ነው፡፡
የቀኝ ጌታ ዮፍታሄ ግጥሞች ትንቢታዊ ሲሆኑ በአንድ ስንኝ የሚጽፉት ግጥም ተሰጦአቸው የላቀ መሆኑን ያሳየናል፡
የሰማይ አሞራ ልጠይቅሽ ወሬ፣
ተቃጥሏል መሰለኝ ሸተተኝ አገሬ፡፡
በጣሊያን ወረራ ወቅት ለፋሺስት ያገለገሉ ባንዳዎችን በማስመልከት የገጠሙት ምፀታዊ ግጥም እንዲህ ይላል፡-
ለጌሾ ወቀጣ ማንም ሰው አልመጣ
ለመጠጡ ጊዜ ከየጐሬው ወጣ፡፡
ቀኝ ጌታ ዮፍታሄ በተለይ የግእዙን ቅኔ መንገድ ለአማርኛ ለማውረስና የግእዙን ኪነታዊ ጠባይ አማርኛ እንዲኖረው ለማድረግ ታላቅ አስተዋጽኦ እንዳደረጉ ከግጥሞቻቸው እንረዳለን፡፡ ዶክተር አምሳሉ አክሊሉ በጥናታቸው እንደፃፉት፤ ይህም በግእዝ ቋንቋ ያላቸውን እውቀትና ብስለት የሚያረጋግጥ ነው፡፡ ከሳቸው በፊት እንዲህ ያለ ሙከራ ያደረገ ሰው መኖሩም ያጠራጥራል፡፡ የተፃፈም ነገር አላጋጠመንም፡፡ ግን ኋላ ላይ ይህን መንገድ ብዙዎቹ ባለቅኔዎች ተከትለው ሰርተውበታል፡፡
ቆሞ የስኳር ጠጅ
ውስተ ደብረ ማሕው ልብነ ሀገሩ ስቃይ ወተድላ፤
ወደይነ በበተራሆሙ አረቄ ወጠላ፤
በውስተ በርሜል ልብነ ምስትግቡአ በቀለ አተላ፤
እሳተ አራዳ ኮኛክ እሷው ተቃጥላ፤
አወያይታ ለባቢሎን ገላ፡፡
ግማሽ አማርኛ ግማሽ ግእዝ አድርገው የሚያዘጋጇቸው ማህሌተ ገንቦ የተባሉት መዝሙሮቻቸው አድማጭ የሚስቡ ነበሩ፡፡ በተጨማሪም በቀኝ ጌታ ዮፍታሄ ንጉሴ ድርሰት ላይ ጐልቶ እንደታየው የዮፍታሄ አፃፃፍ ከቀበሌኛ ወይም ከአገራቸው ከጐጃም አማርኛ የነፃ ነው፡፡ ለማንም አማርኛ ተናጋሪ ሳይቸግር ይገባል፡፡ የግእዝ ብስለታቸው ለዚህ አፃፃፍ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አድርጓል፡፡
ማሽላና ስንዴ በአንድ አብረን ስንቆላ፤
እያረረ ሳቀ የባህር ማሽላ፡፡
ከሰል የሚሆኑ ብዙ እንጨቶች ሳሉ፤
ዝግባ ለምን ይሆን ይቆረጥ የሚሉ፡፡
የቀኝ ጌታ ዮፍታሄ አፃፃፍ ለተከታዮቹ ደራሲያን ምሳሌ ስለነበር አንጋፋነታቸው ታላቅ ዋጋ የሚሰጠው ነው፡፡ ዮፍታሄ በግእዝ ቅኔ የበሰሉ ስለነበሩ አማርኛ የስነ ጽሑፍ ቋንቋ እንዲሆንና እንዲያድግ የላቀ አስተዋፅኦ አበርክተዋል፡፡
የአማርኛ ስነ ጽሑፍን ለማሳደግ በተውኔት፣ በግጥም፣ በዘፈን እና በመዝሙር ባደረጉት ጥረት በኢትዮጵያ ስነ ጽሑፍ ታሪክ ውስጥ ከፍተኛ የክብር ቦታ አላቸው፡፡ ባለ ቅኔው ዮፍታሄ ከጣሊያን ወረራ በኋላ እስከ 1941 ዓ.ም የህግ መወሰኛ ምክር ቤት ምክትል ፕሬዝዳንት ሆነው ሲሰሩ ቆይተው በ1942 ዓ.ም አርፈዋል፡፡ የባለ ቅኔው ዮፍታሄ ስራዎች ግን ተጽእኖ ፈጥረው ከትውልድ ወደ ትውልድ ይሸጋገራሉ፡፡

*********************************************************************************
ምንጭ:--http://www.addisadmassnews.com
            --http://www.ethiosalon.com
            --http://ethioliteraturepaltalk.blogspot.com

ሰኞ, ዲሴምበር 03, 2012

የሸገር ሬዲዮ መዓዛ

 ክፍል --፪
**************

እዚህ አዲስ አበባ ውስጥ የሬዲዮ መቀበያችንን መስመር በኤፍ ኤም በኩል ከአንዱ ጫፍ ወደ ሌላው ጫፍ ብንዘውረው ሰባት ያህል የሬዲዮ ጣቢያዎችን ማግኘት እንችላለን፡፡
ሬዲዮ ጣቢያዎቹ የተለያዩ ቢሆኑም አብዛኞቹ የሚያቀርቡት ተመሳሳይ “ዝግጅት” ነው፡፡
አንዱን ጣቢያ ከሌላው ለመለየት የሚያስችል የራሳቸው የሆነ መለያ ቀለም ስለሌላቸው፤ የአንዱ ሬዲዮ ፕሮግራም በሰባት የሬዲዮ መስመሮች ውስጥ ተከፋፍሎ የሚሰማ እስኪመስል ድረስ ምንም ዓይነት ልዩነት አይታይባቸውም፡፡ የሚያቀርቧቸው ፕሮግራሞች በክሊሼ የታጀሉና ኦና ከመሆናቸው የተነሳ አድማጭን ያንገፈግፋሉ፡፡ መስፍን ሀብተማርያም በአንድ የወጐች መድበሉ ላይ እንዳለው፤ ለአንዳንዶቹ ሬዲዮኖች ሲባል “ምነው ጆሮም እንደ ዓይን ቆብ በኖረው” ያሰኛል፡፡
ለመሆኑ ጥሩ የሬዲዮ ፕሮግራም እንዴት ያለ ነው? ጥሩ የሬዲዮ ፕሮግራም፤ ባለሙያ መጥናና ቀምማ ባሰናዳችው መልካም ወጥ ሊመሰል ይችላል ይባላል፡፡
 
የባለሙያዋን ቅመም ዓይነትና መጠን እንዲሁም የአበሳሰል ዘዴ ባናውቀውም፣ በማድመጥ ግን ጥሩው የቱ እንደሆነ እናውቀዋለን፡፡ ለምሳሌ ለእኔ መልካም የሬዲዮ ፕሮግራም ማለት እንደ ቢቢሲ፣ እንደ ዶቼ ቬሌ፣ እንደ ቪኦኤ ወይም እንደ ሸገር ሬዲዮ ፕሮግራም ያለ ነው፡፡
የሬዲዮ ፕሮግራም ዝግጅት የማያቋርጥ መሰናዶ እንደሚሻ የዘርፉ ባለሙያዎች ይጠቁማሉ፡፡ በተጨማሪም ሙያው ከማንኛውም የጋዜጠኝነት ዘርፍ ያላነሰ ምርምር፣ ሐቀኛ መረጃ እና እንደ ጥበብ ደግሞ የፈጠራ ሥራ ያስፈልገዋል፡፡ በዚህ ላይ ተመስርቶ ቀላል፣ የተመጣጠነ ሆኖም አዝናኝ ወይም አስተማሪ የሆነ ፕሮግራም ከሙዚቃ ጋር ተዋህዶ ለዛ ባልተለየው ዘዴ ሲቀርብ የአድማጩን የዕውቀት አድማስ ያሰፋል ወይም ያዝናናል፡፡ በዚህ ረገድ በሀገራችን የተሻለ ሥራ በማከናወን የአድማጩን ስሜት ለማርካት የቻለው ሸገር 102.1 ኤፍ ኤም ሬዲዮ ነው፡፡
 
ይህ ሬዲዮ በተመሠረተ በአጭር ጊዜ ውስጥ ያሳየው ብቃት በአገራችን የሬዲዮ ሥርጭት ታሪክ ውስጥ ጉልህ ሥፍራን እንዲያገኝ አድርጐታል፡፡ የጣቢያው ብቃትና ችሎታም ምንጭ የአዘጋጆቹ የዓመታት የሬዲዮና የጥበብ ሥራ ቅምር ውጤት ነው፡፡ ሸገር ሬዲዮ የተፀነሰው፤ አንጋፋው የኢትዮጵያ ሬዲዮ በመሠረተውና የአገሪቱ የመጀመሪያው የኤፍኤም ሬዲዮ በሆነው በኤፍ ኤም አዲስ 97.1 ስቱዲዮ ውስጥ ከአስራ ሶስት ዓመታት በፊት በ1992 ዓ.ም ነበር፡፡

በአንድ ወቅት የሸገር ሬዲዮ አስኳል የሆነው የ“ጨዋታ” ፕሮግራምን ጅማሮ አስመልክተው የፕሮግራሙ ፕሮድዩሰር አቶ አበበ ባልቻ ሲገልጹ፤ የኤፍኤም አዲስ 97.1 ሥራ አስኪያጅ የነበሩ ሰው፤ ሬዲዮ ጣቢያቸው ለተባባሪ አዘጋጆች የአየር ሰዓቱን ክፍት ሊያደርግ እንዳሰበ እንዳጫወቷቸው አስታውሰው፤ “ስለዚህም በሬዲዮ ላይ የመሥራት ልምድም ሆነ ፍላጐትም ከነበራቸው ከወይዘሮ መዓዛ ብሩ እና ከአቶ ተፈሪ ዓለሙ ጋር በመሆን ቅዳሜ ከቀትር በኋላ ባለው ጊዜ የሚቀርብ ዝግጅት ለማቅረብ መሰናዶ ጀመርን” ብለው ነበር፡፡
 
በዚህም መሠረት ወይዘሮ መዓዛ ብሩ ቀደም ብለው ያቋቋሙት “አደይ ፕሮሞሽን” እና የአቶ ተፈሪ ዓለሙ “ትንሣኤ ኪነጥበባት” ተጣምረው “ጨዋታ” ሲሉ የሰየሙትን ዝግጅት ከኤፍ ኤም አዲስ 97.1 ጋር በመተባበር፣ ቅዳሜ ሐምሌ 1 ቀን 1992 ዓ.ም በአየር ላይ በማዋል ፕሮግራማቸውን በይፋ ጀመሩ፡፡ የጨዋታ ፕሮግራም ዘወትር ቅዳሜ ከሰባት ሰዓት ተኩል እስከ ምሽቱ ሁለት ሰዓት ተኩል ለ420 ደቂቃዎች ያህል የቃለመጠይቅ፣ የድራማና የግጥም፣ የስፖርትና የሙዚቃ ዝግጅቶችን ያቀርብ ጀመር፡፡ ፕሮግራሙ የአዘጋጆቹ ልምድ፣ ችሎታ፣ ጥረትና ለዛ የታከለበት በመሆኑ በአጭር ጊዜ ውስጥ በኤፍ ኤም አዲስ 97.1 ከሚቀርቡ ዝግጅቶች በተወዳጅነት ቀዳሚው ለመሆን በቃ፡፡
 
በዚህ ጊዜ በተለይ የማይዘነጋውና በጨዋታ ፕሮግራም ከሚቀርቡት ዝግጅቶች ሁሉ ተወዳጁ መጀመሪያ በደረጄ ኃይሌ፣ በኋላ በመዓዛ ብሩ ይቀርብ የነበረው “የጨዋታ እንግዳ” የተሰኘው የቃለመጠይቅ ፕሮግራም ነበር፡፡ በዚህ ፕሮግራም በርካታ የአገር ባለውለታ የሆኑ እንግዶች ቀርበው የሥራ እና የሕይወት ትውስታቸውን አካፍለው አድማጩን አስደስተውታል፡፡
በተጨማሪም አንደ ፍቃዱ ተክለማርያም ያሉ ስም ያላቸው ታዋቂ የጥበብ ባለሙያዎች የሚያቀርቧቸው ትረካዎችና የሬዲዮ ድራማዎች ለጨዋታ ፕሮግራም ውበት የሰጡ ፈርጦች ሆነውለት ነበር፡፡ የቅዳሜ ጨዋታ ተቀባይነት እየጨመረ ወደ ሸገር ሬዲዮ እስከተዘዋወረ ድረስ ቀጥሏል፡፡
 
ለመሆኑ ሸገር ሬዲዮ እንዴት ተመሠረተ? ባለቤቱስ ማን ነው የሚለው ጥያቄ የሬዲዮው ወዳጆችና አድናቂዎች ሁሉ ይመስለኛል፡፡ የዚህ ሬዲዮ መስራች፣ ባለቤትና ሥራ አስኪያጅ ወይዘሮ መዓዛ ብሩ ትባላለች፡፡

መዓዛ የተወለደችው እዚህ አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ሲሆን ዘመኑም 1951 ዓ.ም ነበር፡፡ ከአንደኛ እስከ ሶስተኛ ክፍል በሐረርጌ ክፍለ ሀገር በሒርና ከተማ ተምራ፣ ከአራተኛ እስከ 12ኛ ክፍል ያለውን ትምህርቷን ደግሞ በቅድስት ማርያም ትምህርት ቤት (Saint Mary School) ተከታትላ ፈጽማለች፡፡ መዓዛ በትምህርት ቤቷ በክፍል ውስጥ አጫጭር ታሪኮችን ለተማሪዎች በማንበብ ከመታወቋም ሌላ ከፍ ያለ የሥነ - ጽሑፍ ዝንባሌ እንደነበራት የሚያስታውሱት መምህራኗ “አንድ ቀን ታላቅ የጥበብ ሰው እንደሚወጣት እናውቅ ነበር” ይላሉ፡፡
 
መዓዛ በ1971 ዓ.ም በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሥነ - ቋንቋ ጥናት ተቋም ውስጥ በሥነ -ልሣን (Linguistics) ትምህርት ክፍል ተመደበች፡፡ ሥነ - ልሣን መዓዛ የምትፈልገው ጥናት ባለመሆኑ በምደባው ቅር ብትሰኝም፤ በንዑስ ትምህርት ደረጃ (minor study) የምትወስደው የውጭ ቋንቋና ሥነ - ጽሑፍ በመሆኑ ለነበራት ቅሬታ እንደማካካሻ ሆኖላታል፡፡ በዚህ ዩኒቨርሲቲ የሶስተኛ ዓመት ተማሪ ሳለች የተፈጠረ አንድ አጋጣሚ ደግሞ መዓዛንና ሬዲዮንን የሚያስተሳስር ይሆናል፡፡ ይኸውም የኢትዮጵያ ሬዲዮ የፕሮግራሞች ኃላፊ የነበረው አቶ ታደሰ ሙሉነህ ለሚያዘጋጀው የእሁድ የሬዲዮ ፕሮግራም ድራማ የሚጫወቱ ሸጋ ድምጽ ያላቸው ወጣቶችን ሲያፈላልግ ከመዓዛ ጋር ይተዋወቃል፡፡ ድራማው አስታጥቃቸው ይሁን ያሰናዳው ሲሆን የመዓዛ ድምጽ ለሙከራ በስቱዲዮ ተቀርጾ ሲሰማው፣ ታደሰ ሙሉነህ የሚፈልገውና የሚወደው ድምጽ ሆኖ ስላገኘው ይደሰታል፡፡ ከዚህ በኋላም ለእሁድ ፕሮግራም የሚሆኑ ጽሑፎችን በየሳምንቱ እንድታነብለት ያግባባትና የመዓዛና የሬዲዮ ፍቅር በኢትዮጵያ ሬዲዮ ይወለዳል፡፡ ከዚህ ጊዜ ጀምሮ የመዓዛ ድምጽ በእሁድ የሬዲዮ ፕሮግራም አድማጮች ዘንድ የተለመደና የተወደደ ሆነ፡፡ መዓዛም የሌሎችን ጽሑፎች በማንበብ ብቻ ሳትወሰን የራሷን ጽሁፎች እያዘጋጀች የምታቀርብ ንቁ ተሳታፊ በመሆን ከሬዲዮ ፕሮግራሙ ቤተሰቦች እንደ አንዱ ሆነች፡፡ በ1974 ዓ.ም ከዩኒቨርሲቲ ተመርቃ ትምህርቷ ፍጻሜውን እስካገኘ ድረስም መዓዛ ሬዲዮና ትምህርትን ጎን ለጎን ስታስኬድ ቆይታለች፡፡
የመዓዛ የሥራ ዓለም የተጀመረው ግን በምትወደውና በምትፈልገው በኢትዮጵያ ሬዲዮ ውስጥ ሳይሆን መንግስት በመደባት በባህል ሚኒስቴር መስሪያ ቤት ውስጥ ነበር፡፡ ስራዋም ባህልና ስፖርት የተባለው የመስሪያ ቤቱ መምሪያ በሚያሳትመው “መርሐ ስፖርት” የተሰኘ ወርሃዊ የስፖርት መጽሔት (በኋላ ጋዜጣ) ላይ ሆነ፡፡ ምንም እንኳ አዲሱ ስራዋ ከራዲዮ የሚያርቃት ቢሆንም መዓዛ ግን ሳትሸነፍ ሬዲዮን በትርፍ ጊዜ ሥራነት ተያያዘችው፡፡ ሬዲዮ ጣቢያው የሚሠጣትን አነስተኛ ክፍያ እየተቀበለችም ልዩ ልዩ ጭውውቶችን እና መጣጥፎችን በግልና በጋራ በማቅረብ ተወዳጅ ሥራዎቿን ለሕዝብ አበርክታለች፡፡
 
መዓዛ በእሁድ የሬዲዮ ፕሮግራም ታቀርባቸው የነበሩት ሥራዎች ይዘት ማህበራዊ ሕይወት እንዲሠምር በመጣር ላይ ያተኮሩ ሆነው ግልጽ፣ ቀላልና ለዛ ያልተለያቸው ስለነበሩ ከሶስት አሥርት ዓመታት በኋላም ትውስታቸው ከአድማጭ ህሊና አልጠፉም፡፡ በዚሁ ፕሮግራም ላይ መዓዛ ካበረከተቻቸው የፈጠራ ሥራዎቿ ውስጥ ጎልቶ የሚታወሰው “የአዲሱ ቤተሰብ” የተሰኘ ባለ ሰማንያ ስድስት ክፍል ድራማ ሲሆን በዘመኑ ከሊቅ እስከ ደቂቅ ሁሉም የሚያደምጠው ተወዳጅ የቤተሰብ ድራማ ነበር፡፡
መዓዛ በ “መርሀ ስፖርት” እና በሬዲዮ መካከል ሆና ከአራት ዓመት በላይ ከቆየች በኋላ በ1979 ዓ.ም የባህል ሚኒስቴርን ለቅቃ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ተቀጠረች፡፡
 
አዲሱን መስሪያ ቤቷን ከተቀላቀለችበት ከዚህ ጊዜ ጀምሮ ከሬዲዮ እየራቀች መጣች፡፡ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ውስጥ የቆየችው ለሶስት ዓመታት ያህል ሲሆን ከዚያ በኋላ የግሏን የማስታወቂያ ሥራ ድርጅት መሥርታ የራስዋ ተቀጣሪ ሆናለች፡፡ ከ1979 ዓ.ም ጀምሮ እስከ 1992 ዓ.ም ባሉት የአስራ ሶስት ዓመታት ጊዜ ግን መዓዛና ሬዲዮ ተራራቁ፡፡
መዓዛና ሬዲዮ ዳግም የተዋደዱት ከላይ እንደተገለጸው በ1992 ዓ.ም ሳምንታዊውን የ “ጨዋታ” ፕሮግራም በኤፍ ኤም 97.1 ከተፈሪ ዓለሙ ጋር በጋራ ማቅረብ ሲጀምሩ ነበር፡፡ የ “ጨዋታ” ፕሮግራም እስከ 1999 ዓ.ም ድረስ በአድማጮቹ እንደተወደደ በኤፍ ኤም አዲስ 97.1 ላይ ሲቀርብ ቆይቷል፡፡ መንግሥት ለመጀመሪያ ጊዜ ሁለት የኤፍ ኤም ሬዲዮ ፈቃዶችን ለግሉ ዘርፍ ለመስጠት ሲዘጋጅ፣ ዝርዝር የሥራ እቅድ አቅርባ ባመለከተችው መሠረት፤ ከረጅም ጊዜ ቆይታ በኋላ ከአስር አመልካቾች መካከል አንዷ ሆና የመጀመሪያ የግል የኤፍ ኤም ሬዲዮ ባለቤት ያደረጋትን ፈቃድ ተቀበለች፡፡
መዓዛ የሬዲዮ ማሰራጫ መሳሪያዎችን ውድነት፣ የማሰራጫ ቦታ እና የባለሙያ እጦትን ተቋቁማ ሸገር 102.1 ኤፍ ኤም ሬዲዮን በታህሳስ 2009 ዓ.ም አበረከተችልን፡፡

ባለትዳርና የሶስት ልጆች እናት የሆነችው መዓዛ እንደ ባለቤት፣ ሥራ አስኪያጅና ጋዜጠኛ በመሆን በኢትዮጵያ ተወዳጁንና የመጀመሪያውን የግል የኤፍ ኤም ሬዲዮ ጣቢያ ትመራለች፡፡ በመዓዛ ህይወትና ሥራዎችዋ ላይ የመመረቂያ ጥናቱን ለሠራው ለኤርምያስ ወሌ በሚያዝያ ወር 2002 ዓ.ም በሰጠችው ቃለምልልስ “የማይክራፎን ፍቅር አይለቀኝም፤ እስካሁን ድረስ ከሬዲዮ ባለመለየቴም እጅግ ደስተኛ ነኝ” በማለት ስለ ስራዋ ያላትን ስሜት ተናግራለች፡፡
 
ሸገር በዚህ ዓመት የተመሠረተበትን የአምስተኛ ዓመት የልደት በዓሉን ያከብራል፡፡ ሸገር ደካማውን ጎኑን አጠንክሮ፣ ጠንካራውን እያጎለበተ ገና ብዙ ሻማዎች እንደሚለኩስ የአድማጮቹ ተስፋ ነው፡፡ በዚህ አጋጣሚ ወይዘሮ መዓዛ ብሩን፣ አቶ ተፈሪ ዓለሙን እና መላውን የሸገር ሬዲዮ ጣቢያ ሠራተኞችና ጋዜጠኞች እንኳን ለሸገር ሬዲዮ የአምስተኛ ዓመት የልደት በዓል አደረሳችሁ እላለሁ፡፡
“ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!!!”

ጠያቂዋ መዓዛ ብሩ ስትጠየቅ /መዓዛ ብሩ ስለጨዋታ ፕሮግራም ምን ትላለች ?



ቀኝ ጌታ ዮፍታሄ ንጉሴ

ማሽላና ስንዴ በአንድ አብረን ስንቆላ፤
እያረረ ሳቀ የባህር ማሽላ፡፡

ከሰል የሚሆኑ ብዙ እንጨቶች ሳሉ፤
ዝግባ ለምን ይሆን ይቆረጥ የሚሉ፡፡


         የሰማይ አሞራ ልጠይቅሽ ወሬ፣
         ተቃጥሏል መሰለኝ ሸተተኝ አገሬ፡፡

       
         ለጌሾ ወቀጣ ማንም ሰው አልመጣ
         ለመጠጡ ጊዜ ከየጐሬው ወጣ፡፡

         ቀኝ ጌታ ዮፍታሄ ከተውኔት ድርሰታቸው በተጨማሪ መዝሙሮችንና ግጥሞችን ደርሰዋል፡፡ የኢትዮጵያ አንድነትና የህብረት መዝሙር የሚገልጽልንን የኢትዮጵያ ህዝብ መዝሙር (ተፈሪ ማርሽ)፣ ወላድ ኢትዮጵያ፣ አጥንቱን ልልቀመው፣ ድንግል አገሬ ሆይ የሚባሉ መዝሙሮችን ደርሰዋል፡፡ አጥንቱን ልልቀመው የሚለው ግጥም አርበኞቹን የዶጋሊውን አሉላ አባ ነጋ እና ራስ ጎበናን በማነፃፀር የገጠሙት ግጥም ሲሆን ድንግል ሀገሬ ሆይ የተሰኘውን ድርሰት የፃፉት በስደት ኢሊባቡር ሆነው በ1929 ዓ.ም ነበር፡፡ ይህ መዝሙር ከመጀመሪያ ረድፍ ከሚጠቀሱት ስራዎቻቸው ቀዳሚው ነው፡፡

             ድንግል ሀገሩ ሆይ ጥንተ ተደንግሎ
             ጥንተ ተደንግሎ ጥንተ ተደንግሎ
             ህፃናቱ ታርደው ያንቺም ልብ ቆስሎ
             ልጅሽ ተሰደደ አንቺን ተከትሎ
             የህፃናቱ ደም አዘክሪ ኩሎ፡፡
             አዝማች፤ አስጨነቀኝ ስደትሽ
             እመቤቴ ተመለሺ እመቤቴ ተመለሺ


ይሄ ግጥም ዮፍታሄ ንጉሴ ህዝቡ በፋሺስት ወረራ የደረሰበትን ስደት የገለፁበት ስንኝ ነው፡፡ ቅድስት ድንግል ማርያም ከእስራኤል ወደ ግብጽ ያደረገችውን ስደት እና በኤሮድስ ህፃናት መቀላታቸውን ከኢትዮጵያ ስደት ጋር ያነፃፀሩበት ግጥምም ነው፡፡ የቀኝ ጌታ ዮፍታሄ ግጥሞች ትንቢታዊ ሲሆኑ በአንድ ስንኝ የሚጽፉት ግጥም ተሰጦአቸው የላቀ መሆኑን ያሳየናል፡
የቀኝ ጌታ ዮፍታሄ አፃፃፍ ለተከታዮቹ ደራሲያን ምሳሌ ስለነበር አንጋፋነታቸው ታላቅ ዋጋ የሚሰጠው ነው፡፡ ዮፍታሄ በግእዝ ቅኔ የበሰሉ ስለነበሩ አማርኛ የስነ ጽሑፍ ቋንቋ እንዲሆንና እንዲያድግ የላቀ አስተዋፅኦ አበርክተዋል፡፡

     የአማርኛ ስነ ጽሑፍን ለማሳደግ በተውኔት፣ በግጥም፣ በዘፈን እና በመዝሙር ባደረጉት ጥረት በኢትዮጵያ ስነ ጽሑፍ ታሪክ ውስጥ ከፍተኛ የክብር ቦታ አላቸው፡፡ ባለ ቅኔው ዮፍታሄ ከጣሊያን ወረራ በኋላ እስከ 1941 ዓ.ም የህግ መወሰኛ ምክር ቤት ምክትል ፕሬዝዳንት ሆነው ሲሰሩ ቆይተው በ1942 ዓ.ም አርፈዋል፡፡ የባለ ቅኔው ዮፍታሄ ስራዎች ግን ተጽእኖ ፈጥረው ከትውልድ ወደ ትውልድ ይሸጋገራሉ፡፡

ቀኝ ጌታ ዮፍታሄ ንጉሴ  ሥራዎች:--

1. እኔ አይኔን ሰው አማረው (ግጥምና ቅኔ)
2. ዐጥንቱን ልልቀመው፥ መቃብር ቆፍሬ (ግጥምና ቅኔ)
3. ወላድ ኢትዮጵያ ለልጆቿ ብላ (ግጥምና ቅኔ)
4. ጎበዛዝቴ ሆይ ወይ ቆነጃጅቴ (ግጥምና ቅኔ)
5. ሰውን ሰው ቢወደው አይኾንም እንደራስ (ግጥምና ቅኔ)
6. አወይ ጥርሴ ሞኙ ዘወትር ይሥቃል (ግጥምና ቅኔ)
7. ሙናዬ (ግጥምና ቅኔ)
8. የኛማ ሙሽራ (ግጥምና ቅኔ)
9. አንተ ባለጐዛ (ግጥምና ቅኔ)
10. ድንግል አገሬ ሆይ ጥንተ ተደንግሎ (ግጥምና ቅኔ)
11. የእኛማ ሀገር (ግጥምና ቅኔ)
12. ሰለኢትዮጵያ (ግጥምና ቅኔ)
13. ትንሽ ዐማርኛ (ግጥምና ቅኔ)
14. የሥነ- በዓል መዝሙር...እንደመፋቂያ (ግጥምና ቅኔ)
15. ጉሰማዬ (ግጥምና ቅኔ)
16. ተነሱ ታጠቁ (ግጥምና ቅኔ)
17. አብሪ ብርሃንሽን (ግጥምና ቅኔ)
18. የባሕር ዳር ጨፌ (ግጥምና ቅኔ)
19. ባገር ገዳይ፥ቋጥኝ ድንጋይ... (ግጥምና ቅኔ)
20. በለስ ለመለመች (ግጥምና ቅኔ)
21. እስክትመጣ ድረስ... (ግጥምና ቅኔ)
22. ጎሐ ጽባሕ (ግጥምና ቅኔ)
23. አገሬ ኢትዮጵያ...ሞኝ ነሽ ተላላ... (ግጥምና ቅኔ)
24. የኢትዮጵያ ሕዝብ መዝሙር (ግጥምና ቅኔ)
25. የሰንደቅ ዓላማ መዝሙር ደሙን:ያፈሰሰ፥ተጣማጅ: አርበኛ (ግጥምና ቅኔ)
26. አፋጀሽኝ (ተውኔት)
27. እያዩ ማዘን (ተውኔት)
28. ስለአያ ከምሱና ስለአያ እነባንት ይቀጡ (ተውኔት)
29. እለቄጥሩ /ጎበዝ አየን /  (ተውኔት)
30. ጥቅም ያለበት ጨዋታ (ተውኔት)
31. የሕዝብ ፀፀት፥የእመት በልዩ ጉዳት (ተውኔት)
32. የሆድ አምላኩ ቅጣት (ተውኔት)
33. ዕርበተ ፀሐይ (ተውኔት)
34. ምስክር (ተውኔት)
35. ያማረ ምላሽ (ተውኔት)
36. ዳዲቱራ (ተውኔት)
37. ሞሽሪት ሙሽራ (ተውኔት)
38. መሸ በከንቱ፥ ሥራ ለፈቱ (ተውኔት)
39. ጠረፍ ይጠበቅ (ተውኔት)
40. ዓለም አታላይ (ተውኔት)
41. የደንቆሮዎች ትያትር (ተውኔት)
42. ንጉሡና ዘውድ (ተውኔት)




        ምንጭ:-- http://mekilit.blogspot.com/2014/02/1885.html





አኮቴት ስለሚገባት እንስት ጋዜጠኛ

ክፍል- ፩
 *****
ሀተታ ሀ…
የዚህ ፅሁፍ መነሻ እውነት ነው…. እውነት እንደመነሻ እንጂ ያላግባብ ምስጋና ለማቅረብ ታስቦ አይደለም፡፡ ለመተዋወቅና ዝምድና ለመፍጠርም አይደለም፡፡
ጉርሻ ቢጤ ነገር ለማግኘት ማሞካሸት የሚል እሳቤም አልያዘም፡፡ የብልጠት ምስጋና እንዲሆን ታስቦ የተደረገም አይደለም፡፡ በፍፁም፡፡ በእውነት እውቀት እንጂ በብልጣብልጥነት የኖረ… የሚቀጥል ሀገር አለ ብሎ ጸሐፊው አያምንም፡፡ በመሆኑም የብልጠት መወድስ አይደለም፡፡ እውነት ግን ምክንያት ነበር፡፡ የሰራ ስው ሊወደስ እና ሊመሰገን ይገባል፡፡ የሚል እውነት ነው፡፡ ቤቴ ከባልንጀሮቼ ጋር ቁጭ ብዬ የማወራው… የሚያስወራ ርዕሰ ጉዳይ ከብዙ ጊዜ በኋላ በማግኘቴ የልቤን የእውነት ምስጋና ለማቀበል ያህል ነው፡፡
ሀተታ ሁ…
ጠጠር በምታክል የህይወት ተሞክሮዬ ውስጥ የማይረሱ እና ሊዘነጉ የማይችሉ የሬዲዮ ፕሮግራሞችን መጥቀስ እችላለሁ፡፡ የእውነትም ነበሩ፡፡ታዲያ ለኔ ቀድሞ የሚመጣው ዶ/ር እጓለ ገ/ዮሀንስ “የከፍተኛ ትምህርት ዘይቤ” ብለው በሬዲዮ ያደረጉት ንግግር ነው፡፡ በሬዲዮ ሲተላለፍ ባላዳምጠውም በመፅሀፍ መልክ በመታተሙ ለማንበብ እድል አግኝቻለሁ፡፡ ንግግሩ የተደረገበት ዋና መንስኤም አፄ ሀይለስላሴ ገነተ ልዑል ቤተመንግስትን ለዩኒቨርስቲ መገልገያ እንዲውል በማድረጋቸው ነበር፡፡ ንግግር ተባለ እንጂ ታስቦ የተፃፈ የሊቅ መፅሀፍ ነው ለኔ፡፡ ሀገሬ እንዴት ያለች የሊቅ ሀገር እንደሆነች ከሚያስረግጡ የሬዲዮ ንግግሮች መካከል እንዱ ነው ማለት ይቻላል፡፡
መፅሀፉን ያላነበባችሁት ብታነቡት መልካም ፍሬን ታገኙበታላችሁ በማለት ወደ ሚቀጥለው ሀሳቤ ልሻገር፡፡
ከሰማኋቸው እና እውቀት እውቀት ከሚሸቱ የሬዲዮ ፕሮግራሞች መካከል ከዛሬ 13 ዓመት በፊት ገደማ በኢትዮጵያ ሬዲዮ ይቀርቡ የነበሩት የ “እሁድ ጥዋት” እና “ቅዳሜ ወጣቶች” ፕሮግራም የማይዘነጉኝ ናቸው፡፡ በአንዲት ትንሽ የገጠር መንደር…በሰፈሩ ብቸኛ በሆነችው… በመቀጥቀጥ ብዛት የቢራ ጠርሙስ በመሳሰሉ ባትሪዎች በምትንቀሳቀሰው ያላምሬ ሬዲዮ የሱማሌ፣ የትግራይ እና የደቡብ ወንድሜን የሕይወት ልምድ፣ ተሞክሮ ያሳውቀኝ እና እሩቅ ሀገር ስላለው ኢትዮጵያዊ ወንድሜ መንፈሳዊ ቅናት ይፈጥርብኝ የነበረው የቅዳሜ የወጣቶች ፕሮግራም ድንቅ ነበር፡፡ ፕሮግራሞቹ ኢትዮጵያዊነትን የሚሰብኩ፣ ወጣትነትን በእጅጉ የሚገልፁ እና የሚያንፁም ነበሩ፡፡ ወይ ጉድ! … እኔም በዚች እድሜዬ ነበሩ ካልኩ የሆነ ቦታ የተቋረጠ እና የተረሳ ነገር አለ ማለት ነው፡፡ ችግር አለ እንደማለትም ያስኬዳል፡፡
ትምህርት ቤት ሰኞ ጠዋት በእረፍት ጊዜ ለ15 ደቂቃ የምንወያይበትን ዕርሰ ጉዳይ የሚሰጠን ሌላው የሬዲዮ ፕሮግራም “ከመጻህፍት ዓለም” ነበር፡፡ በሚጢጢ አንጎላችን ስለገፀባህሪ አሳሳል፣ ስለሰው ምንነት የተከራከረንበትን ጊዜ አልረሳውም፡፡ ቃል የተባል መጸሕፍ ሲተረክ ጥጉ ይልማ ከጸሀይ ይበልጣል ብዬ በመከራከሬ የቀመስኩት ቦክስ ምልክቱ ዛሬም አለ፡፡ በአጠቃላይ ግን ለዛ ያላቸው እና ማንነትን የሚቀርጹ ፕሮግራሞች ነበሩ፡፡ ነበሩ… ነበሩ… ብቻ፡፡
ሀተታ…..
“ከትላንት ዛሬ ይሻላል ነው ይበልጣል” የሚለውን ሀረግ ከየት እንዳነበብኩት አላስታውሰውም፡፡ ዛሬ… በኔ ጊዜ ግን አብዛኞዎቹ በሬዲዮ የሚቀርቡ ፕሮግራሞች ልደትን ለማክበር የተሰናዱ ይመስላሉ፡፡ በኔ ጊዜ ያሉ የሬዲዮ ጣቢያዎች በአራዳ ቋንቋ ብገልፀው … ለ‘ኢንጆይ’ የተቋቋሙ ይመስለኛል፡፡ ድረ ገፅ ላይ የተፃፈ እንግሊዘኛን ወደ አማርኛ ገልብጦ ማንበቢያ ጣቢያም ይመስሉኛል፡፡ ያልተጣራ መረጃ እና መረጃን ብቻ ለማስተላለፍ የተቋቋሙም ይመስሉኛል፡፡ ለምሳሌ አንድ የክልል ከተማ ላይ የተቋቋመ የሬዲዮ ጣቢያ ስለ አንድ የውጭ ሀገር ዜጋ ሙሉ ጊዜውን ሰጥቶ መለፍለፍ ፋይዳው ለኔ አይገባኝም፡፡ እንዲገባኝም አልገደድም፡፡ ይልቁኑስ የአካባቢውን እውነታ፣ ውበት ማንነት እና በራስ የመኩራት ባህል፣ በአጠቃላይ ደግሞ ኢትዮጵያዊ ማንነት ተኮር ስለሆነ ነገር በሬዲዮ ማውራት ግን ለብዙ አርቆ
አሳቢዎች ይገባቸዋል፡፡
እንደ እውነቱ ከሆነ ‘ግሎባላይዜሽን’ ከሚያመጣው ጣጣ አንዱ መዋዋጥ ነው፡፡ የሀገሬ የሬዲዮ ፕሮግራሞችም መነሻ አላማ መሆን የነበረበት ከዚህ መዋዋጥ የምንወጣበትን መንገድ በማመልከት፤ ጥርት ባለ ኢትዮጵያዊነት መኩራት ምን ማለት ነው የሚል ሀገራዊ አንድምታ ያለውን ሀሳብ ይዞ መቅረብ ነው፡ ነገር ግን ፕሮግራማቸው ቀድሞ ከተዋጠ ወጤቱ አስፈሪ ነው የሚሆነው፡፡ በተለይ የሚዲያ ተፅዕኖ ክብደትን ሳስብ መጭው ጊዜ ያስፈራኛል፡፡ የወገኛ ነገር ሆኖብኝ እንጂ የጽሁፌ አላማ ስለጣቢያዎች የፕሮግራም ይዘት ማውራት አልነበረም፡፡ ግን ደግሞ በሰከነ አእምሮ እንዲያስቡ ጠቁሞ ማለፍ ክፋቱ አይታየኝም፡፡
ሀተታ አ…
ቀደም ብዬ ለማስገንዘብ እንደሞከርኩት የጽሑፌ መነሻ አላማ ስለ አንድ ብርቱ እንስት የሬድዮ ጋዜጠኛ አኮቴት ማቅረብ ነው፡፡ ብርቱ እንስት የሬዲዮ ጋዜጠኛ ብዬ መፃፍ ስጀምር፣ መዓዛ ብሩ የምትባል የሸገር በተለይ ደግሞ “የጨዋታ እንግዳ” አስተናጋጅ ጋዜጠኛ በአንባቢያን አእምሮ እንደምትከሰት እገምታለሁ፡፡ በኔ ጊዜ እየቀረቡ ካሉት የሬዲዮ ፕሮግራሞች በተለየ መልኩ ብርሀን ለመፈንጠቅ የምትታትር ጋዜጠኛ ነች፤ መዓዛ ብሩ፡፡ እውነት ነው፤ እኛ ወጣት ኢትዮጵያዊያን የሆነ ብርሀን በማጣት እና የባዕድ ሀገር ተብለጭላጭ ብርሃን መሳይን ነገር በመሻት ውቅያኖስ ላይ እንደተጣለ ኩበት እየዋለልን እንደሆንን እኔን እንደማስረጃ ማቅረብ ወይም የጎረቤቴን ልጅ መጥቀስ በቂ ነው፡፡ ዛሬ ከአድዋ ጀግኖች ይልቅ ቬትናም ላይ ጦርነት ያወጁ የአሜሪካ ‘ጀግኖች’ በልጠውብን በጣም በታመምንበት ሰዓት፣ “የጨዋታ እንግዳ” የተሰኘ የሬዲዮ ፕሮግራም መኖሩ እውነትም ይህች ሀገር ብዙ ተቆርቋሪ ዜጋ እንዳሏት የሚያመላክት ነው፡፡
አኮቴቴ የጨበጣ እንዳይሆን ግን ምክንያቶቼን ለመጥቀስ ልሞክር፡፡ የአዋቂ እይታ ስም ከማውጣት ይነሳልና ከስሙ ልጀምር፤ “የጨዋታ እንግዳ” ጨዋታ ለአብዛኛዎቻችን እንግዳ ቃል አይደለም፡፡ ከህፃን እስከ አዋቂ፣ ከሊቅ እስከ ደቂቅ ያለ የህይወት ምግብ ነው፡፡ ልብ ካላችሁ ደግሞ ቤተሰቦቻችን “ልጆች ጨዋታ ላይ ነን” ካሉ ቁም ነገር እየሰሩ ነው፡፡ እከሌ እኮ ጨዋታ አዋቂ ነውም ይባላል፡፡ በትያትረኛ ስንመለከተው ደግሞ በቅድመ-ቅኝ ግዛት በአፍሪካ ለትያትር መኖር ወይም መፈጠር ጨዋታ አዋቂዎች እንደመነሻ ምክንያት ይታያሉ፡፡ ጨዋታ የሚለው ቃል አስደንቆን ሳንጨርስ እንግዳ ይከተላል፡፡ እኔን፣ አንተን፣ አንችን፣ እኛን ሊገልፅ የሚችል ቃል ነው፡፡ በኢትዮጵያዊታችን ከምንኮራባቸው እና የጋራ መገለጫዎቻችን ከሆኑት አንዱ እንግዳ ተቀብለን ማክበራችን ነው፡፡ እንደ “ጨዋታ እንግዳ” አይነቱ ቀላል እና ሳቢ አገላለፅ የስነጥበብ አንዱ መገለጫ እንደሆነም ብዙዎች አስረግጠው ይናገራሉ፡፡ ከዚህ ይበልጥ ደግሞ አብረሀም በእንግዳ ተቀባይነቱ ሶስቱ ስላሴዎችን እንዳስተናገደ ሁሉ፤ በጨዋታ እንግዳ የቀረቡ ብዙ አዋቂ፣ መርማሪ፣ አርቆ አሳቢ እና ሀገርኛ የሆኑ ዘመዶቼ መሆናቸውን ሳስብ እውነትም ስምን መልዓክ ያወጣዋል እንድል ይስገድደኛል፡፡ ከስያሜው ወጣ ብዬ መዓዛ ብሩን በአደባባይ እንዳመሰግናት ስላደረጉኝ ብዙ ነገሮች ለማውራት ትህትና የበዛው ድፍረት በቂ ይመስለኛል፡፡ መዓዛ ብሩ አብዝታ የጋዜጠኛ ስነምግባርን የተላበሰች፣ ለበቃ የጋዜጠኝነት ሙያ የተፈጠረች ብቁ ጋዜጠኛ ነች፡፡ እንዴት?
ስለጋዜጠኝነት ስነምግባር ሲወራ ቀድሞ የሚመጣው ጋዜጠኛ እውነትን የመሻቱ ጉዳይ ነው፡፡ መዓዛ እንግዶቿን ስታጨዋውት የተረዳሁት ነገር ቢኖር ይሄ እና ይሄ ብቻ ነው፡፡ ሀቁን በራሷ እይታ ለመተንተን አትደፍርም፡፡ አንድ ጥያቄ ጠይቀው መልሱን እራሳቸው እንደሚመልሱት እና በእንግዳቸው ላይ ተፅኖ ለመፍጠር እንደሚታገሉ ጋዜጠኞች አይነት አይደለችም፡፡ ሀቁ እንዲወጣ ግን የበሰለ የቤት ስራዋን ሰርታ ትመጣለች፡፡ አንዳንዴ “እንግዶቿ ከየት ያገኘችው መረጃ ነው?” እስኪሉ ድረስ ጥናቷ እጅግ በጣም ጥልቀት አለው፡፡ እንደአብዛኛዎቹ ልደትህ መቼ ነው የሚከበረው? የምግብ የመጠጥ፣ እና የልብስ ምርጫህ ምን ይመስላል? ድመት አትወድም አሉ? ጀምስ ቦንድ የተባለው ፈረንጅ አብሮህ እንዲሰራ ጠይቆህ ነበር? የሚሉ አይነት ጥያቄዎች ከመዓዛ አንደበት አልሰማሁም፡፡ ይልቁንም እውነት… በተለይ ደግሞ ኢትዮጵያዊ ማንነትን ሊገነባ የሚችል ሀቅ እንዲወጣ እሳቷን ትለኩሳለች፡፡ ለኔ መረጃ እውቀት የሚሆነው በዚሁ ረገድ ነው ብዬ እተማመናለሁ፡፡
መዓዛ ለምታነሳው ርዕሠ ጉዳይ እራሷን ከምንጩ ትነጥላለች፡፡ ከስሜታዊነት የፀዱ ጥያቄዎችን በማሰናዳትም ከሙያው የሚጠበቀውን ስነምግባር ትጠብቃለች፡፡ በመዓዛ “የጨዋታ እንግዳ” የምናውቀው አንድ እና አንድ ነገር መዓዛ ብሩ የምትባል ጋዜጠኛ እንግዳ ስትጠይቅ ብቻ፡፡ ጥያቄዎቿም ከራስ ስሜት የፀዱ ናቸው፡፡
ለአድማጭ ፍላጎት እና ስሜት ቅድሚያ የምትሰጥ ጋዜጠኛ ናት፡፡ ይህ አይነቱ ስነምግባር አፍሪካ ውስጥ ለሚገኙ ጋዜጠኞች ፈታኝ እና የማይታሰብ ነው፡፡ መዓዛ ጥቁር እንግዳ ብላ ከጋበዘች፤ እንትና የሚባል ግለስብ፣ እነእንትና የሚባሉ ሰዎች ወይንም እንትን የሚባል መደብ ይከፋዋል የሚል የደካማ ምክንያት ተብትቦ ሲይዛት እስካሁን አልታዘብኩም፡፡ ጥያቄዎቿ የማንም ተፅዕኖ ሲያደበዝዘው አይታይም፡፡ የሀቁ ጠቀሜታ ለአድማጯ እስካመዘነ ድረስ ከመጠየቅ ወደ ኋላ አትልም፡፡
የመዓዛ ብሩ ሂስ እና የመቻቻል መድረክ
ይህ እንድፅፍ ካስገደደኝ ሁነኛ የመዓዛ ጥንካሬ መገለጫዎች የመጀመሪያውን ደረጃ ይዞ ይገኛል፡፡ የምንጠያየቅበትን፣ የምንተቻችበትን እና ካለፈው ተምረን የወደፊቱን የምንተነብይበትን መድረክ በማዘጋጀት መዓዛ ትልቅ ድርሻ እየተወጣች ትገኛለች፡፡ የታሪክ ክፍተቶች በበጎ እንዲሞሉ ትተጋለች፡፡ የትውልድ ቀጣይነት እንዲኖር መመኘት ብቻ ሳይሆን እውን እንዲሆን ትሮጣለች፡፡ በተለይ ደግሞ በ “ጨዋታ እንግዳ” የቀረቡ እንግዶች የዘነጋናቸው ወይንም በተዳፈነ አስተሳሰብ ከሆነ መደብ ጋር መድበን ቂም የያዘንባቸው፤ ሀቁ ሲወጣ ግን በየቤታችን ይቅር ይበሉን ያልናቸው ሊቃውንት ናቸው፡፡ እናም እንደ ሲኤንኤኑ ላሪ ኪንግ እና የሀርድ ቶኩ ስቴቨን ጆን ሳካር፣ መዓዛም ምርቱ ከገለባው የሚለይበት፣ ምክንያታዊ ዳኝነት ገዥ ሀሳብ የሚሆንብት መድረክ ነው የ “ጨዋታ እንግዳ”ዋ ፡፡አቦ መዓዛ ይመችሽ!
ከዚህ በላይ ስለመዓዛ ብቁ የጋዜጠኝነት ተሰጥኦ ለመተንተን ሰፊ እና ጥልቅ የጋዜጠኝነት እውቀት ይፈልጋል፡ለማድነቅ ግን ክፍት አእምሮ፣ ተራማጅ አስተሳሰብ እና ስሜት በቂ ነው ባይ ነኝ፡፡ነገ ብዙ መዓዛዎች እንዲመጡ እና ሌላ መዓዛ እንድናሸት ሁሌም በርችልን፡፡ በስተመጨረሻ መዓዛ “የጨዋታ እንግዳ” ብላ ሰዎችን መጋበዟ አንድምታው ምን ይሆን?.... ሙያው ውስጥ ላሉ ባልንጀሮቿ ብዙ ብዙ ነው መልዕክቱ፡፡ መቸም ለብልህ ሁለቴ አይነግሩትም፡፡
ለኛ… በየትኛውም ቦታ ተሰማርተን ቀና ደፋ ለምንል ወጣቶች ደግሞ ቃሉ ሰፊ ነው፡፡ በ “ጨዋታ እንግዳ” ከቀረቡ ልሂቃን መካከል የአንዱን ሊቅ ንግግር ልውሰድና እኔ እንደሚመቸኝ አድርጌ ላቅርበው፡፡ ለሁሉም ኢትዮጵያዊ የመጀመሪያ፣ የማትቀየር እና ምርጫ የሌላት እጮኛው ኢትዮጵያ ናት፡፡
የዚችን ድንቅ እጮኛ ሁኔታ እና ያልተፈታ እውነት ለማወቅ መጠየቅ፣ ጠይቆም ደጉን ከክፉ መለየት፡፡ ምክንያቱም እጅን አጣጥፎ ከመቀመጥ መጠየቅ ይበልጣል፡፡ ከመጠየቅም ደግሞ እጅግ በጣም መጠየቅ ያዋጣል፡፡ እንደ ሀገርም እንደራስም ለመኖር ሳናስተውል “አብቅቶላቸዋል… ያዛውንት ቃል ምንተዳዬ” ብለን የዘነጋናቸውን ፣ በአካባቢያችን ያሉ አዛውንትን እየጠየቅን መቅረፅ፣ መሠነድ ክፍተታችንን ለመሙላት አማራጭ የሌለው ማለፊያ መንገድ ነው፡፡
******************************************************
ምንጭ:---http://www.addisadmassnews.com

ማሞ ካቻ (አቶ ማሞ ይንበርብሩ)

  አቶ ማሞ ይንበርብሩ (ማሞ ካቻ) እስቲ እናስታውሳቸው፣ ተቀብሮ እንዳይቀር አኩሪ ታሪካቸው  (ደረጀ መላኩ)   አቶቢሲ ማሞ ካቻ የት ትሄዳለህ? ገብረ ጉራቻ… ታዳጊው ማሞ ይንበርበሩ ገና በጨቅላ እድሜው አባቱ አቶ...