ሐሙስ, ዲሴምበር 22, 2016

አማተር ክበባትና ማህበራት የት ደረሱ?

ዳዊት ንጉሡ ረታ


መነሻዬ
ሰሞኑን የጥበብ ባለሙያው አብርሃም ወልዴ የአይዶል ሾው የልዑካን ቡድን በደሴና በባህር ዳር ውድድር ሲያካሂድ በቴሌቪዥን መስኮት ተከታትያለሁ። መቼም ወሎና ጎጃም ሲነሱ የቀድሞዎቹን የወሎ ኪነትና የጎጃሙን ጊሽ ዓባይ የሙዚቃ ቡድኖች በማስታወስ “በዚህ የአይዶል ውድድር ምን ዓይነት ጥበብ እናያለን?” የሚል ጉጉት መፈጠሩ አይቀርም፡፡
እነማን ናቸው እነ ይሁኔ በላይንና ሰማኸኝ በለውን የሚተኩት?... እነማንስ ናቸው እነ ዜኒት ሙሃባንና ማሪቱ ለገሰን የሚያስታውሱን?  እነኚህ የጥበብ መፍለቂያ ቦታዎች ዛሬም የጥበብ ልጆችን ማፍለቃቸው እንዳልቀረባቸው የሚያረጋግጡልንስ እነማን ይሆኑ?....በሚል ውድድሩን ለመከታተል ትዕግስት አጥቶ እንደኔው የሚቁነጠነጥም አይጠፋም፡፡
ሆኖም ግን ውድድሩ ሲቀርብ ነገሩ የተገላቢጦሽ ሆኖ ተገኝቶአል፡፡ ራሳቸው የአይዶል ዳኞቹን ጨምሮ እኔንና መሰል ተመልካቾችን ባስገረመን መልኩ ይሄ ነው የሚባል/የምትባል ድምፃዊም ሆነ የውዝዋዜ ተሰጥዖ ያለው ተወዳዳሪ ባለመመልከታችን “ምነዋ ወሎ? ምነዋ ጎጃም?” ማለታችን አልቀረም፡፡….ይሄን ጊዜ ጥያቄ ይነሳል፡፡………ባንድ ወቅት በአገሪቱ እንደ አሸን ፈልተው በተለያዩ ጊዜያትና ቦታዎች ልዩ-ልዩ የጥበብ በረከቶችን ለጥበብ አፍቃሪው ህብረተሰብ ሲያቀርቡ የነበሩት እነዚያ የአማተር ወጣቶች ክበባትና ማህበራት የት ደረሱብን?...የሚል፡፡ 
1980ዎቹ
እነዚህ ጊዜያት ዛሬ ዛሬ በኪነ-ጥበቡ ዓለም ጎልተው የወጡና አይናችን በስስት የሚመለከታቸው፤ ጆሮአችን በጉጉት የሚያደምጣቸው ከያኒያን የተፈጠሩበት ጊዜ ነው፡፡ በወቅቱ በአማተር የቴአትር፣ የሙዚቃ፣ የጋዜጠኝነትና የስነፅሁፍ ክበባት ሁሉም እንደየ-ችሎታው ተደራጅቶ፣ ከባህልና ማስታወቂያ ቢሮ ህጋዊ ፈቃድ በማግኘት የሚንቀሳቀስበት ወርቃማ ዘመን!
አርቲስት ተስፋዬ ሲማ
አማተር ከያኒያንን በመመልመልና በተለያዩ ዙሮች በማሰልጠ፣ በጥበቡ ታሪክ ስሙ እንዳይረሳ የሆነው ተስፋዬ ሲማ የተባለ አርቲስት ነው፡፡ ይህ ሰው በእርግጥ በአሁኑ ጊዜ መኖሪያውን በአሜሪካ ቢያደርግም ለብዙዎቹ የአዲስ አበባ አማተር ከያኒያን መፈጠርና ለአማተር ክበባቱም መደራጀት ታላቅ ባለውለታ ነው፡፡ 
በወቅቱ (በ1980ዎቹ ዓ.ም) ይህ የጥበብ ባለሙያ በአንድ ዙር እስከ 60 የሚደርሱ ወጣቶችን በመመዝገብና የማወዳደሪያ ፈተና በማውጣት አምስት ኪሎ አካባቢ በሚገኘው በወቅቱ የስፖርት ኮሚሽን ፅ/ቤት ቅጥር ጊቢ ውስጥ በሚገኘው አዳራሽ ልክ እንደ መደበኛ ትምህርት የቴአትር ጥበባት ኮርስ ይሰጥ እንደነበረ አስታውሳለሁ። ትምህርቱ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲው የቴአትር ጥበባት ኮርስ ጋር በእጅጉ የሚመሳሰል ሲሆን ልዩነቱ የጊዜ ብቻ ነው፡፡ ተስፋዬ ሲማ ያንን ስልጠና የሚሰጠው ለ3 ወራት ብቻ ነበር፡፡
የዚህ ስልጠና ፀበል ፃዲቅ ደርሶአቸው ዛሬ ታላቅ ደረጃ ከደረሱ ከያኒያን መካከል ኮሜዲያን አስረስ በቀለ፤ አለልኝ መኳንንት ፅጌ፣ ጥላሁን ዘውገ፣ ተፈራ ወርቁ ወዘተ ይገኙበታል፡፡ ከዚያ በኋላ ስልጠናውን ያጠናቀቁ አብዛኞቹ ከያኒያን ከዚያ በመውጣት የየራሳቸውን የአማተር ከያኒያን ክበባት በመመስረት ለዓመታት ዘልቀዋል፡፡
አርቲስት ተስፋዬ አበበ (ፋዘር) 
ቀደምት ናቸው፡፡ ከታላላቆቹ እነአርቲስት ፍቃዱ ተ/ማርያም ጀምሮ እስከ አሁኖቹ ወጣት ተዋናይ ዳንኤል ተገኝ ድረስ ሳይታክቱ የጥበብ ልጆችን ፈጥረዋል፡፡ በርሳቸው ቤተ-ጥበብ ያላለፈ፤ ልምዳቸውን ያልተጋራ፤ ምክራቸውን ያላደመጠ፤ የጥበብ አብርክቶአቸውን የማያውቅ አማተር ከያኒ አለ ቢባል ይጋነናል፡፡ ከልፋታቸውና ከድካማቸው የተነሳ ገና አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አስቦ የክብር ዶክትሬት ሳይሰጣቸው የጥበብ ልጆቻቸው “ፋዘር” የሚል ከልብ የማይጠፋ ስም ሰይመዋቸዋል፡፡
እኚህ የጥበብ ሰው አማተር ከያኒያኑን በመፍጠር ያበረከቱት አስተዋፅኦ በመጀመሪያው ረድፍ የሚቀመጥ ነው፡፡ ዛሬ ብዙዎች ከእሳቸው የጥበብ ትሩፋት ተgድሰው እንጀራ ወጥቶላቸዋል፡፡ ዛሬ የአገሪቱን የፊልምና የቴአትር ጥበብ እየመሩትም ይገኛሉ፡፡ ተፈላጊነታቸውም አይሎአል፡፡ 
አማተር ክበባትና ማህበራቱ
በወቅቱ (በ1980ዎቹ ዓ.ም) ከቴአትር ቤቶች ባልተናነሰ መልኩ የጥበብ ስራዎቻቸውን የሚያቀርቡ በርካታ አማተር ክበባቶች ነበሩ፡፡ ከእነዚህም ውስጥ በታላላቆቹ የመድረክ ሰዎች ወጋየሁ ንጋቱ፣ ሱራፌል ጋሻው፤ ገድሉ አሰግደው፤ ወዘተ ስም አማተር ክበባት ተመስርተው እንደነበረ አስታውሳለሁ፡፡ እነዚህ የቴአትር ቡድኖች በቴአትር ቤቶች መድረክ እየተከራዩ፣ የመድረክ ቴአትሮችን ገንዘብ በማስከፈል እስከማሳየት ደርሰው ነበር፡፡ በዚህን ጊዜ በአዲስ አበባ ከተማ ብቻ ተመዝግበው በህጋዊነት ይንቀሳቀሱ የነበሩት ቡድኖች ከ500 በላይ ነበሩ፡፡
በወቅቱ እነዚህ አማተር ከያኒያን የሚሰሩዋቸው የጥበብ ስራዎች በሙሉ በወቅቱ ክበባቱን እንዲመዘግብና እንዲቆጣጠር ስልጣኑ በተሰጠው የባህልና ማስታወቂያ ቢሮ ባለሙያዎች የሚገመገሙ ሲሆን ሚዛን የደፉት ወደ ህዝብ እንዲቀርቡ የድጋፍ ደብዳቤ ሲፃፍላቸው፤ ደከም ላሉት ደግሞ ቢሮው ባለሙያ ጭምር በመመደብ ያግዛቸውም እንደነበር ትዝታው አለኝ፡፡
ሽመልስ አበራ ጆሮ፣ ዳዊት ፍሬው ኃይሉና፣ 
ዳዊት ንጉሡ ረታ
የታሪክ አጋጣሚ ሆኖ የሶስታችንም አባቶች (አርቲስት አበራ ደስታ-ጆሮ፣ ፍሬው ኃይሉና ንጉሡ ረታ) ከዚህ ዓለም በሞት የተለዩት ባንድ ወቅት ነበር፡፡ (1986-87 አካባቢ) በዚህም የተነሳ ሶስታችንም አማተር ክበባት በአባቶቻችን ስም መስርተን ነበረ፡፡ በነገራችን ላይ የእኔ አባት አርቲስት ንጉሡ ረታ በአዲስ አበባ ማዘጋጃ ቤት የቴአትርና ባህል አዳራሽ ውስጥ የባህል ሙዚቃ ክፍል ሃላፊ በመሆን ሲያገለግል የነበረ ሲሆን በአብዛኛው ሰው ዘንድ የሚታወቀው ለፋንቱ ማንዶዬ በሰጣቸው ግጥምና ዜማዎች (እሁድ የዕቁብ ጠላ ስለጋ ስለጋና ምን ጠጅ አለ! በሚሉት ስራዎቹ ሲሆን በተጨማሪም ማን ይፈራል ሞት…ማን ይፈራል!...ለእናት ሃገር ሲባል… በሚለው ህዝባዊ መዝሙሩም) ነው፡፡
እናም ሶስታችን የመሰረትናቸው ክበባት ብዙ እንቅስቃሴዎችን ሲያደርጉ ከቆዩ በኋላ ሽመልስ አበራ ጆሮ ራስ ቴአትር በተዋናይነት ሲቀጠር፤ ዳዊት ፍሬው ኃይሉ ደግሞ በብሄራዊ ቴአትር ስራ ሲጀምር ሁለቱ ክበባት ፈረሱ፡፡ እኔ ግን በወቅቱ ተማሪ ስለነበርኩ ክበቤ ስራውን በመቀጠል እነ ድምፃዊት አበባ ደሳለኝን፤ ጥበቡ ወርቅዬን፣ ተወዛዋዥ አቢዮት (ካሳነሽ) ደመቀንና የካስት ኤጀንቱን ሰለሞን ታፈሰን የመሳሰሉትን የጥበብ ልጆች ለማፍራት ችሎአል፡፡
አፍለኛውና ዩኒቲ 
ስለ አማተር ክበባት እያወሩ በአፍለኛውና ዩኒቲ ክበባት ታቅፈው ስለነበሩ ከያኒያን አለማውራት አይቻልም፡፡ አፍለኛው የተመሰረተው በቤተሰብ መምሪያ አማካኝነት ሲሆን ደራሲና ተዋናይ ሰለሞን ዓለሙ፣ የማስታወቂያ ባለሙያው ሰራዊት ፍቅሬ፣ ደራሲና ተርጓሚ እንደዚሁም ተዋናይት አዜብ ወርቁ፣ ተዋናይት ድርብ ወርቅ ሰይፉ፣ ፍሬህይወት መለሰና የመሳሰሉት በወቅቱ አፍለኛው ካፈራቸው  የጥበብ ልጆች ውስጥ በግንባር ቀደምትነት ይጠቀሳሉ፡፡ 
የአፍለኛው ልጆች በአዲስ አበባ ቴአትርና ባህል አዳራሽ መድረክ ተከራይተው፣ “ከዳንኪራው በስተጀርባና” “ፍራሽ ሜዳ” የተሰኙ ቴአትሮችን ለመድረክ ዕይታ አብቅተዋል፡፡ እንደዚሁም በኢትዮጵያ ሬዲዮ ቀርቦ ከፍተኛ ተወዳጅነትን ያተረፈውን “አብዬ ዘርጋው” የተሰኘውን ረዥምና ተከታታይ የሬዲዮ ድራማ በማቅረብ ከፍተኛ አድናቆትን አትርፈዋል፡፡
በዩኒቲ ኮሌጅ አማካኝነት የተመሰረተው የዩኒቲ የቴአትር ክበብም የጥበቡን ልጆች በማፍራት ያደረገው አስተዋፅኦ ቀላል የሚባል አይደለም፡፡ የመድረክ ድራማ ደራሲና ተዋናይ ቴዎድሮስ ለገሰ፤ አዘጋጅና ተዋናይ ተሻለ ወርቁ፣ ተዋናይ ደምሴ በየነ ወዘተ ግኝታቸው ከዚሁ ከዩኒቲ የቴአትር ክበብ ነው፡፡
የዩኒቲ ልጆች ደግሞ በሃገር ፍቅር ቴአትር “የልብ እሳት” የተሰኘ ተወዳጅ ቴአትራቸውን ለረጅም ዓመታት ሲያቀርቡ እንደነበረ ከዚያም በተለያዩ ክልሎች ድረስ በመሄድ፣ ለክልል ተመልካቾች አቅርበው ከፍተኛ አድናቆት ተችሮአቸው እንደነበረ ትውስታዬ ነው፡፡ የዩኒቲ ልጆች ዛሬም በተለያዩ ቴአትር ቤቶች ተቀጥረው፣ ጥበባዊ አበርክቶት እየቸሩን ሲሆን ቴዎድሮስ ለገሰ ደግሞ ኑሮውን በአሜሪካ አድርጎአል፡፡ (ቴዎድሮስ) (በቅርቡ “ዲያስፖራ” የሚል የመድረክ ድራማ ከአሜሪካ ይዞ መጥቶ እንደነበር ይታወሳል)
የቢኒያም ወርቁ ልጆች
መቼም ሰለሞን ቦጋለን፤ ሳምሶን ታደሰ ቤቢን፤ ፍቃዱ ከበደን የማያውቅ የቴአትርና የፊልም ተመልካች አለ ለማለት ያስቸግራል፡፡ እነዚህ በቴአትርና በፊልም ስራቸው ደምቀው የወጡት ከያኒያን በተለምዶ የቢኒያም ወርቁ ልጆች ይባላሉ። መሰረታቸውን ጨርቆስ አካባቢ አድርገው በመጀመር ዛሬ በእያንዳንዳችን ቤት በቪሲዲ ፊልሞችና በቴሌቪቭዥን ተከታታይ ድራማዎች ሰተት ብለው መምጣታቸውን ቀጥለዋል፡፡ ቢኒያም ወርቁም ትርጉም ባላቸው ድርሰቶቹ እነዚህን ተዋናዮች በማሰራት ከህዝብ እንዲተዋወቁና ብሎም የጥበቡን ሰልፍ ከፊት በመሆን እንዲመሩት አብቅቶአቸዋል።  
የቢኒያም ወርቁ ልጆች በዘርፋቸው ውድድር ሲካሄድ ሽልማቱን ጠራርገው እየወሰዱት ነው፡፡ ለፊልም ስራ እሽግ ብሮችን እየተቀበሉ ይገኛሉ፡፡ ይህ ስኬት መነሻው ግን ጨርቆስ ነው፡፡
አማተር የጋዜጠኝነት ክበባት
የአማተር ክበባቱ በቴአትር ብቻ የተወሰኑም አልነበሩም፡፡ በእነ ጋሽ ጳውሎስ ኞኞ ስም የተሰየሙ፣ ትፍላሜ የተሰኘ፣ ሰናይ የሚባል ወዘተ አማተር የጋዜጠኝነት ክበባት እንደነበሩና ለበርካታ ጋዜጠኞች መፈጠርም በር እንደከፈቱ አስታውሳለሁ፡፡ ከእነዚህ ውስጥ በኢትዮጵያ ሬዲዮ የወጣቶች ፕሮግራምና የቅዳሜ መዝናኛ አዘጋጅ የነበረው መሳይ ከበደ እንደዚሁም በዚሁ ጣቢያ ዜና አንባቢና ሪፖርተር ሆኖ የሚሰራው ከተማ ኃ/ማርያም ከብዙዎቹ ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ በዚህ ወቅት በተለይም በደሴ ከተማ የነበረ ታዋቂ የአማተር ጋዜጠኞች ማህበር እንደነበረም ትዝ ይለኛል፡፡ 
እነዚህ ክበባት የንባብ ባህል እንዲዳብር፤ ስነ-ፅሁፍን የሚሞካክሩ ታዳጊ ፀሃፍት እንዲበረታቱ፤ ህብረተሰቡ ስለ ስነ-ፅሁፍ ያለው ግንዛቤ እንዲዳብር ወዘተ ያደረጉት አስተዋፅዖ እንዲህ ባጭር ገፅና ጊዜ ተዘርዝሮ የሚያልቅ አይደለም፡፡ 
ወደ ቀደመው ነገሬ ልመለስ
እኔ ባጭሩ ብፅፈውም ይህን የመሳሰሉ ቀላል የማይባል ታሪክ ያላቸው የጥበቡ ባለውለታዎችን ያፈሩት እነዚያ ተወዳጅ የአማተር ክበባትና ማህበራት የት ደረሱ?....ምነዋ እነ ወሎና ጎጃም የጥበብ ልጆች አምራችነታቸውን ቀነሱ? ምነዋ ስለእነዚያ ደማቅ ክበባት ተቆርቋሪ ሰዎች አጣን?...በመጪው ጊዜስ አዲሶቹ ትውልድ ጥበብን ወደ የት ይሆን የሚተዋወቋት?....
ጥያቄው ብዙ ነው፡፡ መልሱም የዚያኑ ያህል ብዙ ሊሆን ይችላል፡፡ እንደቀልድ ከሰፈራችን፤ ከቀበሌያችን፤ ከከተማችን እየደበዘዙ የጠፉት እነዚያ ወሳኝ ክበባት ዛሬ ዋጋ ሊያስከፍሉን ነው። ካሜራ ያለው ሁሉ ፊልም ልስራ አለና እንጨት እንጨት የሚሉ ፊልሞች በድፍረት እየመጡ ነው፡፡ ለዛ የሌላቸው ድምፃዊያንን፤ በቡድን ያልተቀናጁና ውበት የሌላቸው ተወዛዋዦችን እያየን ነው። አይዶል ባዶ ሲሆንብን ይሰማናል፡፡ ራሳቸው ያልሰለጠኑ ነገር ግን “የመድረክና የፊልም ተዋናዮችን እናሰለጥናለን!” የሚሉ ደፋር ተቋማት እየተፈጠሩ ነው፡፡ የክልሉ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ነገሩን በቸልታ ያለፈው ይመስላል፤ እንቅስቃሴው ደካማ ነው፡፡ 
እናስ?........ የሚመለከታችሁ ሁሉ የመሰላችሁን አክሉበት፡፡
መልካም ቅዳሜ!

***********************************
ምንጭ:-- http://www.addisadmassnews.com/

ማሞ ካቻ (አቶ ማሞ ይንበርብሩ)

  አቶ ማሞ ይንበርብሩ (ማሞ ካቻ) እስቲ እናስታውሳቸው፣ ተቀብሮ እንዳይቀር አኩሪ ታሪካቸው  (ደረጀ መላኩ)   አቶቢሲ ማሞ ካቻ የት ትሄዳለህ? ገብረ ጉራቻ… ታዳጊው ማሞ ይንበርበሩ ገና በጨቅላ እድሜው አባቱ አቶ...