ማክሰኞ, ዲሴምበር 17, 2013

ከፊልም መንደር


“የኢትዮጵያን ፊልም እንደ ዥዋዥዌ ነው የማየው”

  • Written by  አበባየሁ ገበያው 
  • ***********************
“አሪፍ ሃያሲ ፊት ለፊት እየሄደ መንገድን ያሳያል፣ ቀሽም ሃያሲ ኋላ ኋላ እየተከተለ ይገፋል”  አርቲስት ግሩም ኤርሚያስ
አብዛኞቹ የፊልም አድናቂዎች ከ‹‹ሄርሜላ›› ፊልም ጀምሮ ያውቁታል፡፡ በፊልም ትወና ሙያ ለ11 ዓመታት የሰራው አርቲስት ግሩም ኤርሚያስ፤ በየጊዜው በርካታ የፊልም ፅሁፎች ቢቀርቡለትም እስካሁን በዓመት ከአንድ በላይ ፊልም አልሰራም፡፡ መስራት ሳይፈልግ ቀርቶ አይደለም፡፡ የሚመጥነው እያጣ መሆኑን አርቲስቱ ይናገራል። ባለፈው ሳምንት በኢትዮጵያ ኢንተርናሽናል ፊልም ፌስቲቫል ‹‹የዓመቱ ምርጥ የወንድ የፊልም ተዋናይ›› በሚል የተሸለመው አርቲስቱ፤ የዛሬ ሶስት ዓመትም በተመሳሳይ ዘርፍ ተሸላሚ ነበር፡፡ የ‹‹ሜተድ አክቲንግ›› የትወና ዘይቤ ገፀ ባህርይው መስሎ ሳይሆን ሆኖ መጫወት እንደሚፈልግ ያስረዳል፡፡ ለዚህ ነው የሚተውነውን ገፀ ባህሪ ለማጥናት ሰፊ ጊዜ የሚወስደው፡፡ ዘንድሮ በተሸለመበት በ‹‹400 ፍቅር›› ፊልም ላይ ቦክሰኛውን ሆኖ ለመጫዎት ለስምንት ወር የቦክስ ስልጠና እንደወሰደ ይናገራል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አበባየሁ ገበያው ከግሩም ኤርሚያስ ጋር ባደረገችው ቆይቶ ስለ ህይወቱና ስለ ሙያው፣ ስለ ኢትዮጵያ የፊልም ኢንዱስትሪና ተያያዥ ጉዳዮች አነጋግራዋለች፡፡


በቅርቡ ሁለተኛ ልጅ አግኝተሃል፡፡ ባለፈው ሳምንት ደግሞ የኢትዮጵያ ኢንተርናሽናል ፊልም ፌስቲቫል “የዓመቱ ምርጥ የፊልም ተዋናይ” በሚል ተመርጠሃል፡፡ ሽልማት በሽልማት ሆነሃል ልበል…
አዎ.. ሁለቱም ሽልማቶች ናቸው፡፡ የመጀመሪያ ልጄ ወንድ ነው..አምስት አመቱ ነው፡፡ ሁለተኛ ልጄ ደግሞ ሴት ናት፡፡ ይህ የእግዚአብሄር ሽልማት ነው። አዲስዋ ልጄ ከተወለደች ሃምሳ አምስተኛ ቀንዋ ነው። ሌላው በ”የኢትዮጵያ ኢንተርናሽና ፊልም ፌስቲቫል” ሁለት ጊዜ ማለትም በአምስተኛውና በስምንተኛው ዙር ውድድር “ምርጥ የወንድ ፊልም ተዋናይ” ሆኜ ተመርጫለሁ፡፡ ይሔኛው ሽልማት ደግም ሰዎች ለሰራሁት ስራ እውቅና ሰጥተው አክብሮታቸውን ያሳዩበት ነው፡፡ ሁለቱም ለእኔ ብርቅ ናቸው፡፡
እስቲ አሸናፊ ስለሆንክባቸው ስራዎችህ ንገረኝ?
በአምስተኛው ዙር ‹‹ትዝታ›› እና ‹‹ይሉኝታ›› በተሰኙት ፊልሞች በእጩነት ቀርቤ ነው  በአንዱ የተሸለምኩት፡፡ ባለፈው ሳምንት በስምንተኛው ዙር ውድድር ደግሞ ‹‹400 ፍቅር›› በተባለው ፊልም “ምርጥ የዓመቱ የወንድ ፊልም ተዋናይ” ሆኜ ተሸልሜአለሁ፡፡
‹‹ትዝታ›› እና ‹‹ይሉኝታ›› ፊልሞች..ጭብጣቸው ምን ነበር?
ሁለቱም በተለያየ ዘውግ የተፃፉ የተለያየ ባህሪ ያላቸው ፊልሞች ናቸው፡፡ ‹‹ይሉኝታ››ን ካየነው ዳርክ ኮሜዲ ከሚባለው የፊልም ዘውግ የሚመደብ ነው፡፡ ‹‹ትዝታ›› ደግሞ ሙሉ በሙሉ ድራማ ነው። ሁለቱ ውስጥ የተለያዩና ፅንፍ ለፅንፍ ያሉ ገፀ ባህሪያት ናቸው ያሉት፡፡ ‹‹ይሉኝታ›› ላይ ያለው ዋና ገፀ ባህሪ ጥግ ድረስ ሄዶ ሰዎችን የመረዳት ባህሪ ያለው..ለእኔ ጂኒየስ የምለው ዓይነት ሰው ነው፡፡ በቅርብ የማውቀውን ሰው ነው አክት ያደረግሁት። ለእኔ እንደዚህ ዓይነት ሰዎች ለፍፁምነት እጅግ የቀረቡ ናቸው፡፡ በምድር ላይ ብዙ አይደሉም። ክርስቶስ እንዳደረገው፤ ሁሉነገራቸውን ለሰው የሰጡ ዓይነት ናቸው፡፡ ከውጭ ስናያቸው ሞኝ፣ የዋህ ሊመስሉ ይችላሉ፡፡ እንደዚህ ዓይነት ሰዎች በርከት ቢሉ አለማችን ትቀየራች ብዬ አስባለሁ፡፡
‹‹ትዝታ›› ፊልም እውነተኛ ታሪክ ነው፡፡ ዳሬክተሩ ሃብታሙ አሰፋ፤ የአባቱን እውነተኛ ታሪክ ነው የጻፈው፡፡ ያልኖርኩበትን የ60ዎቹን ወጣትነትና በእርጅና ውስጥ ያለ ህይወት ነው የዳሰስኩበት፡፡ የሚገርመው ሁለቱንም አልኖርኩበትም፡፡ ሁለቱም ጽንፍ ያላቸው ግን ወድጃቸው የተጫወትኳቸው ናቸው፡፡ ዘንድሮ በስምንተኛው ዙር ያሸለመኝ ደግሞ ‹‹400 ፍቅር›› ፊልም ነው፡፡ የሁለት መንታዎች ታሪክ ነው፡፡ በመጀመሪያ ‹‹ምን ዓይነት መንታዎች አሉ?›› የሚል ሰፊ ጥናት አደረግሁ፡፡ ብዙ ዓይነት የመንታ ዓይነቶች አሉ፡፡ በፊልሙ ላይ ያሉት ግን ‹‹ሚረር ኢሜጅ አይዴንቲካል ትዊንስ›› የሚባሉ የመንታ ዓይነቶች ናቸው፡፡ እንደዚህ ዓይነት መንታዎች ከሌሎች መንታዎች የሚለዩት፣ ራሳችንን በመስታወት በምናይ ጊዜ መስታወት ውስጥ ላለው ምስል ሁሉ ነገራችን ተቃራኒ ነው። ቀኛችን ግራ ነው፣ ግራችን ቀኝ ነው፡፡ እንደዚህ ዓይነት መንታዎችም መልካቸው አንድ ዓይነት ይሆናል እንጂ ሁሉ ነገራቸው የተለያየ ነው፡፡ ለምሳሌ አንደኛው ግራኝ ከሆነ፣ አንደኛው ቀኝ ይሆናል፡፡ ፍፁም የተለያዩ ናቸው፡፡ አንደኛው ቦክሰኛ ነው፣ አንደኛው ደግሞ ዲዛይነር ነው፡፡
በዚህ ፊልም ውስጥ ቦክሰኛውን ሆነህ ለመጫወት ቦክስ ተለማምደሃል?
ያውም ስምንት ወር ነዋ  የፈጋሁት! ከቦክሰኞች ጋር በመዋል..ሙሉ በሙሉ የቦክስ ልምምዱን ወስጄ ነው የወጣሁት፡፡ ቦክሱን ያስተማሩኝን አሰልጣኝ ከድር ከማልን እና ካሳዬ ከፋን በጣም አመሰግናለሁ። በስምንት ወር ውስጥ ፕሮፌሽናል ቦክሰኛ ነው ያደረጉኝ፡፡
አሁን መዘረር ነው በለኛ...
/ሳቅ/ የሚገጥመኝ ካለ ዝግጁ ነኝ። እና በፊልሙ ላይ የመንትዮችን ባህሪ ሳጠና፣ ከእናትና ከአባታቸው የወረሱት ጂን ምንድን ነው? ለምሳሌ አንደኛው ከእናቱ የድፍረትን ጂን ወስዷል። አንደኛው ደግሞ አባታቸው ፈሪ ስለነበረ የአባታቸውን ጂን ወስዷል። የዚህን ያህል ነው የካራክተሮችን ባህሪ ያጠናሁት። የዚህ ልፋት ዋጋ ነው በሰዎች ዘንድ ዋጋ አሰጥቶኝ ያሸለመኝ፡፡
ወደ ሙያው ከገባህ ጀምሮ ስንት ፊልሞች ሰራህ?
አስራ አንድ ፊልሞች ነው የሰራሁት፡፡ “መስዋዕት”፣ “ሄርሜላ”፣ “ልዕልት”፣ “ስርየት”፣ “የሞረያም ምድር”፣ “862”፣ “ትዝታ”፣ “ይሉኝታ”፣ “አማላዩ” እና “400 ፍቅር” ናቸው፤ ባለፉት አስራ አንድ ዓመታት የሰራኋቸው፡፡ ይሄ እንግዲህ በዓመት አንድ ፊልም ማለት ነው፡፡
ፊልሞች በበዙበት ወቅት እንዴት በዓመት አንድ ብቻ በመስራት ተወሰንክ?
ሁሉጊዜ የሚስበኝ የምሰራበት ፊልም ያለው ታሪክ ምንድን ነው የሚለው ነው፡፡ ለማህበረሰቡ በተወሰነ መልኩ መልዕክት ማስተላለፍ የሚችል ታሪክ ሲሆን ደስ ይለኛል፡፡ በሁለተኛ ደረጃ፣ የምጫወተው ካራክተር (ገፀባህሪ) ነው የሚመስጠኝ፡፡ የእኔ መስፈርት፣ እስከዛሬ ከተጫወትኳቸው ካራክተሮች በጭራሽ የማይመሳሰል መሆን አለበት የሚል ነው፡፡ ለምሳሌ ሰዎች ‹‹አማላዩ››ን ፊልም አይተው ‹‹አማላዩ›› ላይ ያለውን አይነት ካራክተር..ይዘቱም ቅርፁም ተመሳሳይ የሆነ የፊልም ታሪክ ይዘውልኝ ይመጣሉ.. ግን አልቀበልም፡፡ ምክንያቱም ያ በቃ ሞተ፤ ለእኔ ያ ሰው እንደተቀበረ ሰው ማለት ነው። አንድ ካራክተር ከሰራሁት በኋላ እንሰነባበታለን፡፡ ከዛ ደግሞ ያልሰራሁት፣ ያልዳሰስኩት፣ ያልነካሁት ገፀ ባህሪ መጫወት እፈልጋሁ፡፡ የተወሰነ ጊዜ እጠብቃለሁ፤ አሪፍ አሪፍ ነገር እስኪመጣልኝ፡፡ ለዛ መሰለኝ..
ለአምስት ዓመት በማረሚያ ቤት ታስረህ ነበር፡፡ እንዴት ነው ያሳለፍከው?
ብዙ መፃህፍትን “ቁርጥም አድርጌ የበላኋቸው” የዛን ጊዜ ነው፡፡ ልቦለድ፣ ፍልስፍና፣ ስለላ.. ብዙ ታሪኮችን አንብቤያለሁ፡፡ የማንዴላን “Long walk to Freedom”፣ “ፍቅር እስከ መቃብር” ወዘተ.. ትምህርቴን አቋርጬ ስለነበር፣ እንደ አዲስ ከዘጠነኛ ክፍል ጀምሬ እዚያው ተማርኩ፡፡ የቋንቋ ችሎታዬን በተወሰነ መልኩ ለማዳበርም ሞክሬያለሁ፡፡ ማረሚያ ቤት ለእኔ ዩኒቨርስቲ ነበር፣ ህይወትን “ግራጅዌት” አድርጌ እንደወጣሁ ነው የምቆጥረው፡፡ ራስን የመፈለግ ጉዞ ነበር የሆነልኝ፡፡
የሁለተኛ ደረጃ ትምህርትን በማረምያ ቤት ጨረስክ፡፡ ከዚያ በኋላስ አልቀጠልክም?
ከሆሊላንድ አርት አካዳሚ በትያትሪካል አርት ተመርቄአለሁ፤ ሁለት ዓመት ተምሬ፡፡
አንዳንድ ባለሙያዎች ‹‹ሜተድ አክቲንግ” እንደምትከል ይናገራሉ፡፡ እስቲ ስለእሱ አብራራልኝ…
እንደ ስታይል የሜተድ አክቲንግ ስታይል ተከታይ ነኝ፡፡ የሩሲያዊውን አክተርና ዳይሬክተር የስታኒላቭስኪን የሜተድ አክቲንግ መፅሃፍ አግኝቼ አንብቤዋለሁ፡፡ እሱን ከአነበብኩ በኋላ ነው የሜተድ አክቲንጉ ተከታይ መሆን የጀመርኩት፡፡ በዚህ ስታይል መሰረት፤ የምትጫወችውን ካራክተር መምሰል ሳይሆን መሆን አለብሽ፡፡ አንቺ ወደ ካራክተሩ እንድትሄጂ እንጂ ካራክተሩ ወደ አንቺ እንዲመጣ አይጠበቅም፡፡ ወደ አንቺ የሚመጣ ከሆነ “ታይፕ አክተር” ነው የምትሆኝው፡፡ ያ ከሆነ ደግሞ የምሰራቸው ፊልሞች ተመሳሳይ ይሆናሉ ማለት ነው፡፡ ካራክተሩ ወደ አንቺ እንዲመጣ በጋበዝሽው ቁጥር  ሌሎች ሰዎችን ነው የምትሆኝው፡፡ ሜተድ አክቲንግ የሚጠቅመው ካራክተሮችን እንዳትደግሚ በማድረግ ነው፡፡ እኔ ደግሞ የዚህ ውጤት ነኝ፡፡
የተለያዩ ባህሪያትን እያጠኑ ሆኖ መጫወት ትክክለኛው የራስህ ባህሪ ላይ ተጽዕኖ አያሳድርም?
እውነት ነው፤ በጣም ተፅዕኖ (ኢንፍሉዌንስ) አለው፡፡ አንዳንድ ጊዜ ዲፕሬሽን (መደበት) ሊያጋጥምሽ ይችላል፡፡ የተጫወትኩት ባህሪ ከደሜ ውስጥ ሙልጭ ብሎ እስኪወጣ ድረስ ይዞኝ ይጠፋል፡፡ ይሁነኝ ብለሽ አይደለም የሚመጣብሽ። በሰብኮንሸስ ማይንድ (ንቁ ባልሆነው የአዕምሮአችን ክፍል) ነው የሚሰራው። ብዙዎቻችን የምንኖረውም በሰብኮንሼስ ማይንዳችን ነው፡፡ ሰብኮንሸስ ማይንድ በነገርሽው መጠን፣ ያንን ነገር ቅርጽ አስይዞ ያስቀምጥና ይመነዝረዋል፡፡ ከዚያም አሳልፎ ለኮንሸስ ማይንድ (ለንቁው የአዕምሮአችን ክፍል) ይሰጣል፡፡ ‹‹400 ፍቅር››ን ስሰራ አነበብኩ፤ ሪሰርች አደረግሁ፡፡ ቦክስ ተማርኩ…ከቦክሰኞች ጋር ተገኘሁ..ራሴን ‹‹ቦክሰኛ ነኝ›› ብዬ አሳመንኩ፡፡ ቦክስ ቦክስ ስል ሳላውቀው…ሰውነቴም ሪአክት ማድረግ ጀመረ… ክብደት ጨመርኩ..ጡንቻዬ ይሳሳብ ጀመር፡፡ አሁን ደግሞ የሃሺሽ ሱስኛ (ድራግ አዲክትድ) የሆነ ገፀ ባህሪ ያለበትን የፍጹም አስፋውን ፊልም ለመስራት ጥናት ላይ ነኝ፡፡ ሪሰርች ጀምሬያለሁ፤ ሰውነቴ ሲከሳ ይታወቀኛል፡፡
እንዴት ነው በሱስ የተያዘ ሰው ባህሪን የምታጠናው?
/ሳቅ/…ድራግ አዲክትድ ወይም የሀሺሽ ሱስኛ ሰውን ባህሪ ነው የማጠናው፡፡ በተደጋጋሚ ጳውሎስ ሆስፒታል “ሪሃብሊቴሽን ሴንተር” እየተመላለስኩ ነው፡፡ የድራግ ሰብስታንሶች ያሉባቸው ሰዎች ከሱሳቸው የሚነፁበትን መንገድ ለምሳሌ ከመጠጥ፣ ሲጋራ፣ አልኮልና፣ አደንዛዥ ዕፅ... ለማጥናት ሰሞኑን ያለሁት ጳውሎስ ነው..ብዙ የተሰሩ ጥናቶችን ከኢንተርኔት እያወጣሁ አነባለሁ፡፡ በሽተኞች፣ ዶክተሮች፣ ሳይካትሪስቶች…አግኝቻለሁ፡፡ እነሱን ሳገኝ ሳላውቀው ምን እንደሆንኩ ታውቂያለሽ? በየቀኑ የማዘወትረው ስፖርት አስጠላኝ፡፡ ብታምኝም ባታምኝም የምግብ ፍላጐቴ ሁሉ እየተዘጋ መጣ፡፡ ኪሎዬም እየቀነሰ ነው፡፡ ለምን መሰለሽ? ከህመምተኞች ጋር ሳወራ፤ የምግብ ፍላጎት እንደሚያጡና ክብደታቸው እንደሚቀንስ ሰማሁ፤ አሁን ሰውነቴ በዛ ነገር ውስጥ እየገባ ነው ያለው፡፡
ከአምስት ወር በፊት ወታደር ገፀባህሪ ያለው ፊልም ለመስራት ለሶስት ወር የወታደር ካምፕ ውስጥ ልትገባ በዝግጅት ላይ እንደነበርክ ነግረኸኛል፡፡ ምን ደረሰ?
ገና ነው፤ በሆነ ምክንያት እንዲቆይ ተደርጓል። ነገር ግን ከአምስት ወር በፊት እንዳልሽው ወታደር ወታደር ሸትቼ ነበር፡፡ በዛን ወቅት የማያቸው ፊልሞች በጠቅላላ የጦርነት “ዋር ሙቪ” ነበሩ። ማንበብ የምፈልገው መፃህፍት ሁሉ ከውትድርና ጋር የተገናኙ ነበረ፡፡ ማየት የምፈልገው ወታደር ነው፡፡ ከሚሊተሪ ነክ ሰዎች ጋር መዋል ጀምሬ ነበር። እነሱን መስማት ማድመጥ ነበር ስራዬ፡፡ ለሶስት ወር ስልጠና ልንገባ ወደ አዋሽ አካባቢ ካምፕ ሁሉ ተዘጋጅቶልን ነበር፡፡ ይህን ማድረጌ ካራክተሩን በቀላሉ ማግኘት እንድችል ይረዳኛል፡፡ ጊዜው ሲደርስ እሱንም እሰራዋለሁ ብዬ አምናለሁ፡፡
ስታንቶች የሚያስፈለጉት ታዲያ መቼ ነው?
ለምሳሌ እኔ ሞተር ሳይክል መንዳት ባልችል ወይም መኪና ከኋላ የሚከተለው የ”ካር ቼዚንግ” ካራክተር ያለው ፊልም ልስራ ብል..ስታንቶች ያኔ ይመጣሉ፡፡ ስታንቶች ለአክተሩ በጣም ከባድ የሆኑ ልዩ ክህሎት የሚጠይቅበት ቦታ ላይ ነው የሚያስፈልጉት፡፡ ካልሆነ ራስሽ ብትሰሪው ይመረጣል፡፡ እኔ ራሴ ብሰራው እመርጣለሁ፡፡ ደስ የሚለውን…እስከ አሁን በስታንት የተሰራ የለም..ራሴ ስታንት ሆኜ ነው የምሰራው /ሳቅ/
እስከ አሁን ከሰራኋቸው ፊልሞች ምርጥ “ማስተርፒስ” የምትለው ፊልም የትኛው ነው?
ሁሉም በቂ ዝግጅትና ጊዜ ተወስዶባቸው..ወድጃቸው..በጥናትና በፍቅር.. ተለፈቶባቸው፣ በተለያየ መንፈስና ከአካባቢ የተሰሩ ናቸው፡፡
ፊልም የሙሉ ጊዜ ስራህ ይመስለኛል..
አዎ፡፡ ፊልም ብቻ ነው የምሰራው /ሳቅ/
የምትጠይቀው ክፍያ አይቀመስም ይባላል፡፡ ለአንድ ፊልም ስንት ትላለህ?
ክፍያ ላይ ደህና ነኝ፡፡ ከመቶ ሺ በላይ ነው። የዓመት ቀለብ ናት፤ እሷን እየቆረጠምኩ.. ሌላ የሚመጥነኝ ፊልም እስኪመጣ እጠብቃለሁ፡፡
ለፊልም ብለህ በምትለማመዳቸው አንዳንድ ነገሮች ለምሳሌ መጠጥ፣ ሲጋራ ሱስ ተይዘህ ለመላቀቅ የተቸገርክበት ሁኔታ የለም?
/ሳቅ/ ከጫቱም፣ ከሲጋራውም፣ ከድራጉም.. ባጠቃላይ ከየትኛውም ሱስ የለሁበትም፤ እግዚአብሄር ይመስገን፡፡ ሱስ ካልሽው ግን የስፖርት ሱስ አለብኝ..ስራ ከሌለኝ አብዛኛውን ጊዜዬን ጂም ነው የማሳልፈው፡፡ ምክንያቱም ትወና ለእኔ የማይንድ ስቴትና (አዕምሮአችን) የፊዚካል ባዲያችን (አካላችን) ሃርመናይዤሽን ነው ብዬ ነው የማስበው። የሁለቱም ጥምረት ነው፡፡ ሁለትም እኩል መገንባት (መታነፅ) አለባቸው፡፡ ሁለትን ቢውልድ አፕ የሚያደርግ ተዋናይ አሪፍ ተዋናይ ይሆናል ይባላል፡፡ በትርፍ ጊዜዬ መፅሃፍ አነባለሁ። ድሮ ፊክሽን ነበር፤ አሁን የህይወት ታሪኮች (ባዮግራፊ) ፍልስፍና፣ (ሳይኮሎጂ) መፃህፍትን አነባለሁ፡፡ የግጥም መፃሃፍትም እሞካክራለሁ፡፡
መፃፍ ላይስ እንዴት ነው?
አጫጭር ልቦለዶችን እፅፋለሁ.. እሞክራለሁ፡፡ በፍቅር ነው የምወደው፡፡
ወደፊት በመፅሃፍ መልክ ይወጣሉ?
አዎ አስባለሁ፡፡ የተወሰኑ አሉኝ.. በቅርቡ ይታተማል፡፡
የፊልም ስክሪፕት መፃፍና ዳይሬክት ማድረግስ?
“የፕሬዚደንቱ ምስጢሮች” የሚለውን አጭር ታሪክ ዳይሬክት አድርጊያለሁ፡፡ በ2000 ዓ.ም. አካባቢ የአጭር ልቦለዶችን የአረትኦት ስራ ሰርቻለሁ፡፡ ሁለት ፊልሞችን ፅፌያለሁ.. ‹‹ልዕልት” እና “የሞሪያም ምድር›› የእኔ ድርሰቶች ናቸው። አሁን ግን ሙሉ በሙሉ በትወና ስራ ውስጥ ተመሰጥኩ፡፡
በተለይ በእኛ አገር በፊልም ውስጥ ለመተወን የሚያስቸግሩ አንዳንድ ነገሮች አሉ፡፡ ለምሳሌ ከንፈር ለከንፈር መሳሳም አንተ ይሄን ትደፍራለህ?
እንደነዚህ አይነት ነገሮች በርግጥ ትንሽ ከባድ ናቸው፡፡ ከባህላችን ጋር አይሄዱም፡፡ እንደዚህ ዓይነት ነገሮችን አልሞክርም፡፡ ብዙ ነገር በካሜራ ይሸወዳል እንጂ ይከብዳል፡፡ የቆምኩበት መሬት ወይም ባህላዊ መሰረት (ግራውንድ) ማን ነው ብዬ ነው የማስበው። የቆምኩበት ግራውንድ አሜሪካኖች ናቸው… ኢትዮጵያውያኖች? የምሰራው በኢትዮጵያውያን ግራውንድ ነው፡፡ አበሾች ነን። እኔም የዚህ ማህበረሰብ ውጤት ነኝ፡፡ ያደግሁት ሁሉ ነገር ሽፍንፍን ባለበት ማህበረሰብ ውስጥ ነው። እንደ አርት ግን ትክክል ነው፤ መሰራት አለበት፡፡
ፖለቲካ ላይ እንዴት ነህ? ብዙ አርቲስቶች “ፖለቲካና ኤሌክትሪክ በሩቁ” የሚሉ ይመስላል፡፡ አንተስ?
ፖለቲካ ከባድ ነገር ነው ብዬ አስባለሁ፡፡ እኛ እንደምናስበው ዓይነት ጨዋታ ላይሆን ይችላል፡፡ ሁሉም ለሆነ ነገር ይፈጠራል፡፡ አርቲስት፣ እግር ኳስ ተጫዋች.. አንዳንዱ ደግሞ ለፖለቲካ ይፈጠራል። ለዛ የተፈጠሩ ሰዎችን አከብራለሁ፤ አደንቃለሁ። እንደሌላው ሞያ ማለት ነው፡፡ ብዙ ጊዜ እኛ አድናቆት የሚኖረን ለአርት ለተፈጠረ ሰው ሊሆን ይችላል፡፡ ለምንድን ነው ለፖለቲካ የተፈጠረን ሰው የማናደንቀው? አንዳንድ ሰዎች ለፖለቲካ ተፈጥረዋል ብዬ አስባለሁ፡፡ እንደዚህ ዓይነት ሰዎችን ከልቤ አደንቃለሁ፡፡
በአኗኗርህ ምን አይነት የህይወት ስታይል ትከተላለህ?
ቀለል ያሉ አለባበሶች ይማርኩኛል፡፡ ህይወቴ በራሱ ሲምፕሊ ሲቲ የተከተለ ነው፡፡ በግል ህይወቴ የተወሳሰበ ነገር የለኝም፡፡ በኑሮዬም.. በብዙ ነገር… ስለብስም ቀለል ማለት ይመቸኛል፡፡ ግን ራሴን ሳጠናው ደግሞ አንድ ካራክተር አግኝቼ በልምምድ ላይ ከሆንኩ የዛ ካራክተር ስታይል ሲንፀባረቅብኝ አስተውላለሁ፡፡ እስከ አሁን በዲዛይነር የመልበስ ባህላችን ገና ነው፤ የሚያለብሰኝ ካገኘሁ ግን አልጠላም፡፡
አንተ አሪፍ የምትላቸው አሉ? እንደተመልካች ባለሙያ ማለቴ ነው…
ተይ! ከጓደኞቼ ጋር ታጣይኛለሽ፡፡ ግን ካስገደድሽኝ ከአስር አይበልጡም፤ እስከ አሁን ከአየሁዋችው፡፡
የኢትዮጵያ ፊልሞች የእድገት ደረጃ እንዴት ታየዋለህ?
የኢትዮጵያን ፊልም ኢንዱስትሪ እንደዥዋዥዌ ነው የማየው፡፡ በጣም ወደፊት የተራመደ ፊልም ታያለሽ፡፡ በተራመደበት ፍጥነት ተመልሶ ደግሞ ወደ ኋላ ይሄዳል፡፡ ብዙ ጊዜ ከጓደኞቼ ጋር ሳወራ ይህንኑ ነው የምለው፡፡ የሆኑ ፊልሞች ይዘውት ይወጣሉ፤ የሆኑ ፊልሞች ወደላይ ይዘውት ይወርዳሉ፡፡
ፕሮፌሽናል የፊልም ሃያስያን አለመኖራቸው ለዚህ አስተዋፅኦ አድርጓል ትላለህ?
በጣም ቆንጆ ጥያቄ ጠየቅሽኝ፡፡ በርካታ ሃያሲያንን እንፈልጋለን፡፡ በነገራችን ላይ ሃያሲው  ከፊልም ባለሞያዎቹ የተሸለ እውቀት ያለው መሆን አለበት፡፡ እንጂ ዘለፋ ሂስ ሊሆን አይችልም፡፡ በዘለፋ ምንም ማስተማር አትችይም፡፡ ፖዘቲቭና ኔጌቲቭ ጎኑን የሚነግረን፣ ሞያዊ አስተያየት የሚሰጠን ነው የእውቀት ሰው፡፡ እንደዚህ አይነት ሃያሲያን ቢኖሩን ጥሩ ነበር፡፡ ማርክ ትዌይን ስለሃያሲ ያለው አንድ አባባል አለ፡- “ከፊት ከፊት እየሄደ ለደራሲው መንገድ የሚያሳይ ትክክለኛ ሃያሲ ነው” ይላል፡፡ ቀሽም ሃያሲ ከኋላ ከኋላ እየተከተለ ባለሙያውን የሚገፋው ነው። ለእኛ የሚያስፈልገን ከፊት ለፊት እየሄደ መንገዱን የሚጠርግልን ሃያሲ ነው እንጂ የሚገፋ ምን ያደርጋል። የፊልም ኢንዱስትሪው እንዲያድግ እንደዚህ ዓይነት ሰዎች የግድ ያስፈልጋሉ፡፡ ራሱ ሂስ ‹‹ሞያዊ አስተያየት›› ስለሆነ ማለት ነው፡፡
ምን አዲስ ስራዎች እንጠብቅ?
ሁለት ስራዎች አሉ፡፡ ከቶም ፊልም ፕሮዳክሽን ጋር የሰራሁት አንድ ፊልም አለ፡፡ ታሪኩ ስለ አንድ ሃብታም ወጣት ነው፡፡ የተለየ አይነት ባህሪ ያለው ነው.. ትወድታላችሁ፡፡ ሁለተኛው እኔና ሰለሞን ቦጋለ የሰራነው ‹‹የፀሃይ መውጫ ልጆች›› የተሰኘ ፊልም ሲሆን የቢንያም ወርቁ ድርሰት ነው፡፡ በዓይነቱም በይዘቱም ለየት ያለ ነው፡፡ ..ለመስራት በጥናት ላይ ነኝ ያልኩሽ የድራግ አዲክትድ ካራክተር ደግሞ የፍፁም አስፋው ፊልም ነው፡፡ ለጊዜው እነዚህ ናቸው፡፡
ሃሳብ የለህም?
በማውቀው ቋንቋና በለመድኩት ባህል ላይ ስሰራ ደስ ይለኛል፡፡ በትምህርት በኩል ግን በተለይ ከትወና ጋር በተገናኘ ስኮላርሽፖችን ለማግኘት ሁልጊዜ ራሴን ማሳደግ እፈልጋለሁ፡፡ ለራሴ ብቻ ሳይሆን በአገሬም የትወና ፍላጎትና ጥማት ያላቸውን ሰዎች ማስተማር እፈልጋለሁ፡፡ ለዚህ ነው ከዚህ በፊት ተዋናይ ለመሆን ለሚፈልጉ ሰዎች መፅሃፍ ተርጉሜ ያሳተምኩት፡፡
የመፅሃፉ ርዕስ ምንድን ነው?
‹‹መሰረታዊ የትወና መማሪያ›› የሚል መፅሃፍ ነው፡፡ ወደ ትወና በስፋት እየገባሁ በመጣሁ ጊዜ ሙያው ባህር እየሆነና ብዙ ልፋት የሚጠይቅ እየሆነ መጣብኝ.. ያኔ በመሃይም ዕውቀቴ ትወና የጀመርኩ አካባቢ ያወቅሁ መስሎኝ ነበር፡፡ እየሰራሁ በመጣሁ ቁጥር እየሰፋብኝ ነው የመጣው፡፡ ስፋቱን ለማጥበብ መማር አለብኝ፡፡ እድሉን ባገኝ ደስ ይለኛል፤ እስከዚያው በአጠገቤ ያሉትን መፅሃፍት እያነበብኩ እቆያለሁ፡፡
የውጭ ፊልሞችን ትመለከታለህ? የትኞቹን ዘውጐች ትመርጣለህ? የትኞቹን የሆሊውድ አክተሮችስ ታደንቃለህ?
የውጪ ፊልሞች በጣም አያለሁ፡፡ አንድ መፅሀፍ ላይ እንዳነበብኩት አንድ ሰው ፊልም ሰሪ ለመሆን ከፈለገ ፊልም ማየት ነው የሚያስፈልገው። የፊልም ሜከር ትምህርት ቤቱ ራሱ ፊልም ማየት ነው፡፡ የአሜሪካ ፊልሞች እጅግ ይመስጡኛል። የድራማ ዘውግ ፊልሞች አድናቂ ነኝ፡፡ ድራማ የሚያነጣጥረው ሪያሊስቲክ በሆኑ ነገሮች ላይ ነው፡፡ ንፅፅሩም በሁለት መሃል ያሉ እውነቶችን እንድትመርጪ ነው የሚያደርገው፡፡ ድራማ ለተዋናዩም፣ ለአዘጋጁም፣ ለፀሃፊውም ከባድ ነው ይባላል፡፡ ከሆሊውድ አክተሮች የማደንቀው… ከወጣቶቹ ኩባ ጉዲንግ፣ ኤድዋን አልበርተን፣ ማትዴመንን ሲሆን ከፊልም “ሮሚዬዝ ብሊዲንግ” አደንቃለሁ፡፡ ጋሪአልድ ማን የተጫወተበት… ከአውሮፓ ፊልሞች “ሲኒማ ፓራዲዞ” የተባለውን የጣሊያኖች ፊልም አደንቃለሁ። በነገራችን ላይ የአውሮፓ ፊልምም አያለሁ፡፡ ብዙዎቹ የእንግሊዝኛ ሰብታይትል ስላላቸው ቋንቋ ላይ ችግር የለም። የኢራን ፊልሞች በጣም ነው የምወዳቸው። የሚገራርሙ ናቸው፡፡ የአውሮፓ ፊልሞች ለጥበብ አዳኞች ነው የሚሰራው፡፡ ለእኔ አንደኛ ፊልሜ ግን “ሲኒማ ፓራዲዞ” ነው፡፡ በዚህ አጋጣሚ ለአንባቢያን ይህንን ፊልም እጋብዛለሁ፡፡ የፊልም ትምህርት በጣም እየተሰጠ ያለው በአሜሪካ ነው። አውሮፓዎችም አላቸው፡፡ ግን ብማር ብዬ የማስበው አውሮፓ እንግሊዝ አገር ነው፡፡ የእነሱ ፊልሞች በጣም ጠንካራ ናቸው፡፡ ለጥበብ አዳኞች የሚሰራ ነው፡፡ ስኬፒስት ኦዴንሶች አይደለም የሚበዙት፡፡ የሚሰሩት ፊልሞች “ጥበብ ..ለጥበብ ደንታ” የሚባሉ አይነት ናቸው። እነሱ ሲያሾፉ ምን ይላሉ? “ኮሜርሺያል የሆነ የአውሮፓ ፊልም ሆሊውድ ውስጥ ቢሄድ የጥበብ ፊልም ይሆናል” ይላሉ፡፡ እንደዚህ ነው አውሮፓውያን አሜሪካኖቹን የሚንቋቸው፡፡ የሆሊውድ ዳይሬክተሮች ራሳቸው ፊልም የአውሮፓውያንን ፊልም ነው የማያዩት፡፡
ትያትር ላይ ስትተውን አተታይም፡፡ ለምንድነው?
መድረክ ላይ ሰርቼ አላውቅም፡፡ ትያትር የማከብረው ሞያ ነው፤ ዘልዬ መግባት አልፈልግም። ምናልባት ወደ ትያትር ብመጣ እንኳን ስለቲያትር የተወሰኑ ነገሮች በደንብ አውቄ መሆን አለበት፡፡ ምክንያቱም የፊልም አክቲንግ እና የመድረክ አክቲንግ የተወሰነ ልዩነት አላቸው፡፡ ልዩነቱን አጥብቤ ነው ወደ ቲያትር መግባት የምፈልገው፡፡ ለአንድ የፊልም አክተር ከዘጠና ፐርሰንት በላይ ያለው የስሜት ጨዋታ አይን ውስጥ ነው፡፡ ወደ ትያትር ስትመጪ ግን ሰፊ ነው፡፡ ብዙ ሰው ነው ያለው፡፡ ለዛ ሁሉ ሰው ስሜትሽ እንዲጋባበት የምታደርጊው በአይንሽ አይደለም፤ የእጅ እንቅስቃሴዎችን፣ የፊት ገፅታዎችን ትጠቀሚያለሽ …የፊልም ትወና በካሜራ ክሎዝ አፕ እየታየ ነው ጨዋታው፡፡
ፊልም አክት አይደረግም ኑሮ ነው የሚኖረው። “ኖ ፌስ አክቲንግ” ይባላል፡፡ ፊትሽ ላይ አክት አያስፈልግም፡፡ አይን ውስጥ ነው ብዙ ስሜቶች የሚያልቁት፡፡ በጥቅሉ ግን እኔ ቅኝቴም፣ የተጠመቅሁበትም ፊልም ነው፡፡
 ***********************************************************************
ምንጭ:--http://www.addisadmassnews.com

የኢትዮጵያ ኮከብ

በ- አብነት ስሜ

የመጽሐፉ ዋና መከራከሪያ ዘመን በየሁለት ሺህ ዓመቱ ይለወጣል፤ በሦስተኛው ሚሌኒየም የአኳሪየስ ዘመን ገብቷል፤ የኢትዮጵያ ኮከብ አኳሪየስ ነው፤ የአኳሪየስ ዘመን አኳሪየስ ለሆነችው ኢትዮጵያ ከጉዳቱ ይልቅ ጥቅሙ ያመዝናል፤ የሚል ነው፡፡ ትንታኔው የተካሔደው በአስትሮሎጂ ማዕቀፍ ውስጥ ነው።
መጽሐፉ በአምስት ክፍልና በአስራ ሰባት ምዕራፎች ተደራጅቶ ቀርቧል። ለትንታኔው ዳራ ለመስጠት ሲባል የአስትሮሎጂ ታሪካዊ አመጣጥና አሠራር በክፍል አንድ ተመጥኖ ቀርቧል። በዚህ ክፍል ስለዋና ኮከብና ስለ ልደት ሰንጠረዥም አጭር ማብራሪያ አለ። በዚህ ክፍል ባለው የመጨረሻ ምዕራፍም የዘመናት ኮከብ ምጥን ገለፃ ይገኛል። የክፍል ሁለት ዋና ትኩረት 8ኛው ሺህ ስለሚባለው ስለ አኳሪየስ ዘመን ነው። በዚህ ክፍል የአኳሪየስ ዘመን ባህሪ ከአኳሪየስ ኮከብ ፀባይ ተፅእኖ እና ከሊዮ ኮከብ ንኡስ ተፅእኖ አንፃር ተብራርቷል። ክፍል ሦስት ወደ ኋላ መለስ ይልና የአስትሮሎጂን ጥቅሞች እና ምክሮች ያቀርባል። ምክሮቹ በተለይ በጤናና በሙያ ዝንባሌ ላይ ያተኩራሉ።
ክፍል አራት በሀገራት ኮከብ መጠነኛ ገለፃ ይንደረደርና የኢትዮጵያ ኮከብ ላይ ሙሉ ትኩረቱን ያደርጋል። ክፍል ሁለትና ክፍል አራት የመጽሐፉ ማእከላዊ ይዘቶች ናቸው። በክፍል አምስት ሦስት አባሪዎች ተካተዋል። አባሪ 1 ስለ ጉዱ ካሳ ኮከብ በ2001 የተፃፈ ብእሮግ ነው፡፡ አባሪ 2፣ በ1999 ስለ ኢትዮጵያ ኮከብ የጻፍኩት አጭር ብእሮግ ነው። አባሪ 3፣ የውጭ አገርና የኢትዮጵያውያን ስመጥር ግለሰቦችን ኮከብ አጭር ዝርዝር ይዟል። በዚህ አባሪ፣ የሀገራትና የገፀባህርያት ኮከቦች ዝርዝርም ይገኛል።
**************************************
ምንጭ:--http://semnaworeq.blogspot.com/

ረቡዕ, ሜይ 22, 2013

መንትያ ጥበባት፤ ግጥምና ሙዚቃ!

መንትያ ጥበባት፤ ግጥምና ሙዚቃ!
ሰሎሞን ተሠማ ጂ.
****************** 
“የአንድን አገር የሥልጣኔ ደረጃ ለማወቅ ብትሻ፤ ሙዚቃውን አድምጥ፣ ሥነ-ጽሑፉን አንብ!” ብሎ ነበር - ዲዜሬል፡፡ ፕ/ር አሸናፊ ከበደም፣ “የአንዲት አገር ሥልጣኔ አቋም በሳይንስ፣ በፖለቲካ፣ በኤኮኖሚ፣ በቴክኖለጂና በሚሊታሪ ኃይሉ ብቻ ሳይሆን በሙዚቃ፣ ሥነ-ጽሑፍና በሌሎችም የኪነ-ጥበባት ዘርፎች የተደላደለ እንዲሆን ያስፈልጋል፡፡ በተለይም ሙዚቃና ሥነ-ጽሑፍ ረቂቅ አስተሳሰብና ዲሲፕሊንን ስለሚፈጥሩ ሥልጣኔው ተስፋፍቶ መገኘት አለበት፡፡ የቴክኖሎጂና የኤኮኖሚ እድገት ሊኖር የሚችለው የረቂቁ አስተሳሰብ ችሎታ ያላቸው ሰዎች ሲኖሩ ነው” ይሉ ነበር (መነን መጽሔት፣ ሰኔ 1957 ዓ.ም፤ ገጽ 22)፡፡ በማስከተልም፣ “በአዕምሮና በልብ ምንነቱ ሳይታወቅ የሚታሰብ ነገር በሙዚቃ አካል ይኖረዋል በሥነ-ጽሑፍም ግዝፎ ይወጣል፡፡ ታላቅ የተባሉት ሁሉ ዘጠና-ዘጠኝ ከመቶ የሚሆኑት የጥበባዊ (ካላሲክ) ሙዚቃ ተጨዋች የሥነ-ጽሑፍም አፍቃሪዎች ነበሩ፤” ብለዋል (አዲስ ዘመን ጋዜጣ፣ የካቲት 8 ቀን 1960 ዓ.ም፤ ገጽ 5)፡፡  አይንስታይንም ሆነ ዶክተር ኒኮላ ቴስላ በጥበባዊ ሙዚቃና ሥነ-ጽሑፍ አፍቃሪነታቸው የታወቁ ነበሩ፡፡

በሃገራችንም ቢሆን ጥልቁና ረቂቁ ፍልስፍና የገባውና የኖረው በዜማና በቅኔ አማካኝነት ነው፡፡ በሙዚቃ የተራቀቁት ሊቃውንት - በዜማ ቤት፣ በቅኔ ቤትና መጽሐፍት ቤት ውስጥ ሚስጢራትን አቀላጥፈው የሚያውቁ ምሁራን ስለነበሩ ምናባቸው ሰፊ፣ ሥነ-ሥርዓታቸውም ሥልጡንና የተገራ ነበር (ኃይለ ገብርኤል ዳኜ፤ 1970፣ ገጽ 89-90)፡፡ የዜማ ቤት በአራት ይከፈላል፡፡ የመጀመሪያው ድጓ ቤት ነው፡፡ ዓመቱን ሙሉ በቅዳሴና በሰዐታት ጊዜ የሚዘመሩትን ዜማዎች ያጠናሉ፡፡ በመቀጠልም፣ ከቅዳሴ በኋላ በደባትሮች በህብር የሚዘመረውን “ዝማሬ” እና በቀብር ስነ-ሥርዓት እንዲሁም በዝክር ጊዜ የሚዘመረውን “መዋሲት” ያካትታል፡፡ በሦስተኛ ደረጃም መምህራንና የዜማ ሊቃውንት መሆን የሚፈልጉ “ቅዳሴና ሰዐታትን” የተመሰገነ አስተማሪ ዘንድ ሄደው ያጠናሉ፡፡ 

ድጓ ቤት፣ ዝማሬና መዋሲት፣ እንዲሁም ቅዳሴና ሰዐታት የዜማ ተማሪው በተናጠል የሚያዜማቸው ናቸው፡፡ አራተኛውና የመጨረሻው ደግሞ፣ “አቋቋም” ይባላል፡፡ አቋቋም፣ በዜማ ቤት ውስጥ የወረብ፣ ዝማሜና ማሕሌት መማሪያ ነው፡፡ ሃይማኖታዊ ስልት ያለው ውዝዋዜ (ዳንስ) ነው፡፡ ይህ ክፍል በህብረት ጽናጽልና መቋሚያ ተይዞ ንፋስ ከንበል-ቀና እንደሚያደርገው ሰንበሌጥ በስልት ይወዛወዛሉ (ኃይለ ገብርኤል ዳኜ፤ 1970፣ ገጽ 91)፡፡ የነዚህ የዜማ ቤት ሊቃውንት የቀለምና የሙዚቃ ዕውቀታቸውን በሃይማኖታዊውም ሆነ በዓለማዊው ምግባራቸው ሲገለጥ ኖሯል፡፡ 
 
ከዜማ ቤት ቀጠሎም በቅኔ ቤት ቆይታቸው ዘጠኝ ዓይነት አቀኛኘቶችን ያጠናሉ፤ ይለማመዳሉም፡፡ ከባለሁለት ስንኝ (ጉባኤ ቃና) ጀምረው ባለሦስት፣ አራት እስከ ዕጣነ-ሞገር ወይም መወድስ ድረስ (ባለሰባት ወይም ስምንት ስንኝ ያላቸው ሰምና ወርቅ ግጥሞችን) መግጠም ያጠናሉ፡፡ ይጽፋሉም፡፡ የቅኔን አዝመራ የቆረጠመ ምናቡና ምርምሩ የላቀ መሆኑ አይጠረጠርም፡፡ የቅኔ ቤትን ያጠናቀቀ ሙያተኛ አርዕስታዊ የሆነ ርዕሰ-ጉዳይ ላይ እንደልቡ ሃሳቡን በቃላት አማካኝነት ትርጉም መስጠት አያቅተውም፡፡ እርግጡን ለመናገር፣ የምርምርን ክህሎት ብቻ ሳይሆን የፈጠራ ችሎታንም ያዳብል፡፡ ቅኔን ያወቀና ያጠናቀቀ ኩረጃን (Hates an imitation of an imitation) ይጠየፋል::   

በተመሳሳይ ሁኔታም፣ ለምዕራባውያንም ሙዚቃ ማለት ግጥም ነው፡፡ ግጥምና ሙዚቃ ትርጓሜያቸው አንድ ነው፡፡ በሌላ አነገገር፣ ሙዚቃ ሥነ-ጸሑፍ ነው፡፡ ዕውቀት ነው፡፡ ምናብ ነው፡፡ ፈጠራ ነው፡፡ ጥበባዊ ክህሎትን የሚጠይቅም ነው፡፡ ከሁሉም በላይ አዕምሮአዊ ነው፡፡ በመሆኑም ምዕራባዊያኑ ሊቃውንት፣ “አዕምሮአዊ አረዳዱ ዝቅተኛ የሆነ ሰው ሥነ-ጽሑፍም ስለማይገባው፣ ጥበባዊ (ክላሲክ) ሙዚቃም ምን እንደሆነ በግልፅ አይታየውም፤” ይላሉ፡፡ ስለሆነም፣ ምዕራባውያን ዜማንና ሥነ-ጽሑፍን ጎን ለጎን ለታዳጊዎቻቸው ያስተምራሉ፡፡ የታዳጊው አዕምሮ በዜማና በሥነ-ጽሑፍ ረገድ መንትያ ዕድገት እንዲኖረው ይደረጋል፡፡ በመጨረሻም፣ ታዳጊው ወደሚያዘነብልበት በኩል እንዲያተኩር ይደረጋል፡፡    

በኢትዮጵያ ባህላዊ አስተምህሮት ግን ነገሩ የተለየ ነው፡፡ አንድ ሰው የዜማ ቤትን ሲያጠናቅቅ ወደ ቅኔ ቤትና ወደ መጽሐፍት ቤት ያመራል፡፡ ዜማ ማለዘቢያ ነው፡፡ ዜማ የቅኔና የመጽሐፍት ቤቶች መንደርደሪያ ነው፡፡ አዕምሮን ለጥልቁና ረቂቁ የቅኔና የመጽሐፍት እንዲሁም የሊቃውንት ጥናት የሚያዘጋጀው ዜማ ነው፡፡ ያም ሆነ ይህ፣ ዜማና ሥነ-ጽሑፍ በኢትዮጵያም ሆነ በአውሮፓውያን አስተምህሮቶች ዘንድ የአንድ አላድ ሁለት ገፅታዎች ናቸው፡፡ ይህንን መረዳትና መገንዘብም የተገባ ነው፡፡   
ከላይ እንዳወሳነው፣ መዚቃና ሥነ-ጽሑፍ በተለይም ሙዚቃና ግጥም መንትያ ናቸው፡፡ ግጥምና ሙዚቃ የሚከወኑት ለጆሮ ነው፡፡ ለዕዝነ-ልቦና ነው፡፡ ግጥም በአሰኛኘቱ በስድስት ቤቶች ይከፈላል፡፡ ማለትም፤ የቡሄ በሉ ቤት፣ የሠደፌ ቤት፣ የወል ቤት፣ የሰንጎ መገን ቤት፣ የወዳጄ ዘመዴ ቤትና የመዲና ቤት ናቸው (ተሾመ ይመር፣ የኢትዮጵያ ጥናት መጽሔት፡፡ ሐምሌ 1997፡፡ ገጽ 89-123)፡፡ እንደግጥም ሁሉ፣ ሙዚቃም ብዙ ዓይነቶች አሉት፡፡ በድምፅ አሳክቶና አቀናብሮ የታቀደውን ሃሳብ በሰሚው መንፈስና ስሜት፣ እንዲሁም በሰሚው አእምሮ ላይ ትርጉም እንዲያገኝ ለማድረግ ዘዴውንና እውቀቱን ከችሎታ ጋር መጠየቁን ማወቅ የሙዚቃ ባለሙያው ግዴታ ነው፡፡ አድማጩም ቢሆን ለዚህ ዓይነቱ የሙዚቃ ዝግጅት የሠለጠነ መሆን ያስፈልገዋል፡፡

ከይዘት አንጻር ግጥም በሁለት ይከፈላል፡፡ ኃይማኖታዊና ዓለማዊ ይዘት ያላቸው ግጥሞች ይባላሉ፡፡ ለአንባቢውና ለአድማጩ ዕዝነ-ልቦና ባላቸው የመደመጥና የመነበብ ኃይላቸው በሁለት ይከፈላሉ፡፡ የዱሮውንም የአሁኑንና የመጪውን ትውልድ ዓይንና ጆሮ በመያዝና ባለመያዝ አቅማቸው በሁለት ይከፈላሉ፡፡ እነርሱም ጥበባዊ (Classical) ኃይል ያላቸው እና ጊዜያዊ (popular) ስሜትን ለማጫር ሲባል የሚገጠሙ ግጥሞች ናቸው፡፡ አከፋፈሉ ከአድማጩ አንፃር መሆኑን መረዳት ይገባል፡፡ 

በተመሳሳይ ሁናቴም ከይዘት አንፃር፣ “ማንኛውም ሙዚቃ ሁለት ታላላቅ የዓይነት መክፈያዎች አሉት፡፡ እነርሱም 1ኛ/ ሃይማኖታዊ ይዘት ያላቸው ሙዚቃዎችና 2ኛ/ ዓለማዊ ይዘት ያላቸው ሙዚቃዎች ተብለው ነው፡፡ እንደግጥም ሁሉ ሙዚቃዎችም በአድማጩ ዕዝነ-ልቦና ላይ ባላቸው የመደመጥ ኃይልና እንደወይን እያደር በቀማሹ ላይ በሚኖራቸው የማምጠቅ ቃና በሁለት ታላላቅ ክፍሎች ይከፈላሉ፡፡ 1ኛ/ ጥበባዊ (Classical music) ሙዚቃ የሚባሉት ሲሆኑ 2ኛ/ ደግሞ ጊዜያዊ (popular music) ሙዚቃ ተብለው ነው፡፡ ጥበባዊና ጊዜያዊ ሙዚቃዎች በአቀራረብ ስልታቸው መሰረት በሦስት ንዑስ ክፍሎችና ዓይነቶች ይከፈላሉ፡፡ 1ኛ/ ድምፃዊ ሙዚቃ 2ኛ/ መሳሪያዊ ሙዚቃ ሲሆኑ 3ኛ/ የድምጻዊና የመሳሪያዊ ሙዚቃዎች ውሁድነት የሚቀርቡና የሚቀርቡበት ስልት ነው” (ፕሮፌሰር አሸናፊ ከበደ፡፡ አዲስ ዘመን ጋዜጣ፡፡ የካቲት 8 ቀን 1960 ዓ.ም፤ ገጽ 5)፡፡
ከላይ ያተትነውን አከፋፈል በምሳሌ እናብራራው፡፡ አንደኛ፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ሙዚቃ በጠቅላላው ከይዘት አንፃር ሃይማኖታዊ ነው፡፡ በአድማጩ ዕዝነ-ልቦናም ላይ ባለው አቅም ጥበባዊ ክፍልም ውስጥ ይመደባል፡፡ በዚያ ላይ ድምፃዊም ነው፡፡ በሌላ በኩል፣ ሁለተኛነትም የምናያቸው ሙዚቃዎች እነ“ምን ታደርጊዋለሽ” ወይም እነ“ሸግዬ - ሸግዬ” የተባሉትን  ዘፈኖች ነው፡፡ በጠቅላላው እነዚህን የመሳሰሉት የአዝማሪዎችም ሆነ የዘመናዊዎቹ ድምፃዊያን የሚዜሙትን ዘፈኖች ከይዘት አንፃር በዓለማዊ የሙዚቃ አይነትነት ስር እንመድባቸዋለን፡፡ በአድማጩ ዕዝነ-ልቦና ላይ ባላቸውም ኃይል ጊዜያዊ የሙዚቃ ስልትነት ውስጥ ይመደባሉ፡፡ ድምፃዊና መሣሪያዊ የሙዚቃ ዓይነቶችም ናቸው፡፡ (ድምፃዊው በመሣሪያ ታጅቦ የሚያቀርባቸው ንዑስ ክፍሎች ናቸው፡፡)

3ኛ/ የፕሮፌሰር አሸናፊ ከበደ “እረኛው ባለዋሽንት”ና ወይም “ኒርቫናህ” የተባሉት ሙዚቃዎች፣ ወይም የሙላቱ አስታጥቄ “የልቤ ትዝታ” እና ሌሎቹም ቅንብሮቹ ደግሞ ጥበባዊ ናቸው፡፡ ዓለማዊም ናቸው፡፡ መሳሪያዊ ብቻ ናቸው፡፡ ..... “ጥበባዊ ሙዚቃ” ናቸው ስልም፤ “የታቀደውን የሙዚቃ አርእስትና ሃሳብ በድምፅ አሳክቶ፣ አዳብሮና አስፋፍቶ ለአድማጩ መንፈስ፣ አእምሮና ስሜት እንደታቀደው ለማስተላለፍ የሚችለውን ዓይነት ሙዚቃዎች ናቸው” ለማለት ነው፡፡ እነዚህ ሙዚቃዎች የደራሲውን የጥበባዊ ሙዚቃ ቅመራ ችሎታ ብቻ ሳይሆን የአድማጩንም የአእምሮ ጉልምስና ይጠይቃሉ፡፡ ጆሮና ዕዝነ-ልቦናው ያልተገራውን አድማጭ ጨርሶ ላይወዘውዙትም ይችላሉ፡፡

ጊዜያዊ (Popular Music) ሙዚቃ የሚባለው ዓይነት ብዙው ጊዜ የስሜት ብቻ ማስደሰቻ፣ የዳንኪራ መምቻ፣ የሽለላና የፉከራም ማሰሚያ ነው፡፡ ግጥሙም ሆነ ሙዚቃው ያልተያያዘና ያልተገጣጠመ፣ በመሳሪያና በድምፅ ጩኸትና ኳኳታ ብቻ የተሸፋፈነ ሲሆን ጠለቅ ብለው የማይመራመሩና ጊዜያዊ ጭፈራዎችን የሚሹትን አድማጮች ስሜት ቀስቃሽ ነው፡፡ በብዙ መልኩ ከንግድና ከትርፍ ጋር የተያያዘ ነው፡፡

ጊዜያዊ (Popular Music) ሙዚቃ ብዙውን ጊዜ የአድማጮችን “ጊዜያዊ ደስታ” ብቻ ዓላማው ስለሚያደርግ በጥበባዊ ዝግጅት በኩል በብዛት “ባዶ” መሆኑ የተረጋገጠ ነው፡፡ “ባዶ ጩኸት ብቻ ነው፡፡” ምክንያቱም 1ኛ/ ተጫዋቾቹ የመዚቃ ችሎታ ስለሌላቸውና ችሎታቸውንም ለማሻሻል ስለማይጥሩ፤ ሲሆን 2ኛ/ የሚበዛው የዓለም ሕዝብ የሚወደው ይሄንኑ ዓይነት ጩኸትና አደንቋሪ ስልት ስለሆነ ነው፡፡ ተለይም በትንሽ ድካም ብዙ ገንዘብ የሚተረፍበት የሙዚቃ ዓይነት ስለሆነ ነው ጥበባዊ ይዘቱ ኦና ነው፡፡ 3ኛ/ ሙዚቃውና ግጥሙም በትንሽ ድካምና ልምምድ (የውጭ አገሩን ዜማ በመመንዘርና በመኮረጅ የጊዜውን ትኩሳት ለመቀስቀሻነት የሚሆኑትን ቃላት በግጥም መልክ በማሳካት) ተዘጋጅቶ የሚቀርብበት ስልት ነው፡፡

4ኛ/ የተጫዋቾች የቀለምና የሙዚቃ ትምህርት ደረጃቸው በጣም በዝቅተኛ ደረጃ ላይ የሚገኝ በመሆኑ መጥፎውንና ጥሩውን ግጥምና ዜማም ስለማይዩት የለብ ለብ ስራ ይሰራሉ፡፡ የሆነው ሆኖ፣ ባላቸው አቅምና ችሎታ ሕዝብን ለማስደሰት ከመጣጣር አላቋረጡም፡፡ 

የቀለም ትምህርቱንና የሙዚቃ ትምህርቱን ያጣመሩ ባለሙያዎች ያስፈልጉናል፡፡ የኢትዮጵያን ቅኔና ዜማ ስልት ጠንቅቀው ያጠኑና የሚያውቁ የባሕላዊና ዘመናዊ መሣሪያዎችን ለመጫወት የሚችሉ፣ የሙዚቃ ሰዋሰውንና አገባብን በቅጡ የሚያውቁ፣ ድምፅንና ሙዚቃን በአንድነት የሚያቀናብሩና የሚያቀርቡ የሙዚቃ ደራሲዎች ያስፈልጉናል፡፡ ጊዜያዊው ሙዚቃም በነርሱ ምሳሌነት ይሻሻላል፡፡ የምዕራብ አፍሪካን ወይም የሱዳን፣ የደቡብ አፍሪካን ወይም የመካከለኛው አፍሪካን ስልቶችና ዜማዎች በመኮረጅ የትም አንደርስም፡፡ የምዕራባዊያኑንም ሆነ የአረቦቹን ስልት ከኦሪጂናል ድምፃዊያኑ ልሳንና አልበሞች ልንሰማው እንችላለን፡፡ ወደ አማርኛ ወይም ኦሮምኛ ቋንቋ የሚተረጉምልን ቱርጁማን አያስፈልገንም፡፡ ምክንያቱም ሙዚቃ ዓለም አቀፋዊ ቋንቋ ነው፡፡ የቃላቱን ፍቺ ባናውቀው ግድ አይሰጠንም፤ ወይም ሙዚቃ ውስጥ የቃላቱ ረብ ሳየሆን የአርዕስቱ ጉልበት ነው ዕዝነ-ልቦናን የሚገዛው፡፡ 

አድማጩን አያውቅም ብሎ መናቅ ወይም ለመሸወድ መሞከር ይቅር፡፡ አድማጭ ከሌለ ማንኛውም ሙዚቃ ሊዳብርም ሆነ ሊሻሻል አይችልም፡፡ ጊዜያዊ ሙዚቃና ግጥሙ (ጥሩም ሆነ መጥፎ) አሁን ብዙ አድማጭና ፈላጊ እንዳለው እናውቃለን፡፡ ሆኖም፣ በኢትዮጵያ ጥበባዊ ሙዚቃ ከቤተ - ክህነት ውጪ ገና አልተጀመረም ለማለት ያስደፍራል፡፡ ቢኖሩም ከሦስትና አራት የማይበልጡ የተናጠል ጥረቶች ናቸው የሚስተዋሉት፡፡ በ1960ዎቹ ከቤተ-ክህነት ውጭ ጅምሮች ነበሩ፡፡ በብሔራዊ ቴያትር ነርሲስ ናልባንዲያን፣ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ - የባሕል ማዕከል ውስጥ አቶ ተስፋዬ ለማ እና በተፈሪ መኮንን ት/ቤት እንዲሁም በናዝሬት የአፄ ገላውዲዮስ ትምህርት ቤት ሕብረ-ዝማሬዎች ብቅ-ብቅ ማለት ጀምረው ነበር፡፡ ግን ወዲያው ጠፉ፡፡ በደርጉ ዘመን፣ ኪነት ለጥበባዊነቷ ሳይሆን በጊዜያዊ የፕሮፖጋንዳ ተግባር ላይ ተጠምዳ ኖረች፡፡ አሁንም ቢሆን ያው ነው፡፡ ጊዜያዊ ነው! ጊዜያዊ ሆያ ሆዬ የተጠናወታት ነች! በአንድ ሙዚቃ ውስጥ የሰባት ስምንት ብሔረሰቦችን ችፋሮ ማየት ልማድ ሆኗል፡፡ ጥበባዊነት ቀርቶ ስልቱ የሰመረ መሆኑ እንኳን ግር ያሰኛል፡፡ በልዩነት ውስጥ አንድነትን እናሳያለን የሚሉት ቀማሪዎች የወቅቱ ፖለቲካ ደራሽ ጎርፍ ሆኖ እብስ አደረጋቸው፡፡ የከያኒ ነፍሳቸው በፖለቲካ አሸብሻቢነት ተዋጠች፡፡ ጥበባዊት ቆሌያቸውን የወቅቱ ሁናቴ አስደነበረባቸው፡፡ሙዚቃዊ ምቱ፣ ስልቱም ሆነ ጭፈራው ሚስቶ ሆነ፡፡...በቃ ይሄው ነው! ይሄንን ነው በየቴሌቪዥኑ መስኮት የምናየው፡፡ “አፍሪካ! አፍሪካ! አፍሪካ! አገራችን!” የምትለውን የነርሲስ ናልባንዲያንን ሕብረ-ዝማሬ የሚተካከል ሙዚቃ አቀናባሪ ጠፍቶ ሌት ከእንቅልፍ እንደሚቀሰቀስ አረሆ ጯሂ ተራ ስልት ያለ ድብልቅልቅ ነው የሚሰማው፡፡..... 
የጥበባዊ ሙዚቃ አድማጮች ውሱን ናቸው፡፡ ጥበባዊ ሙዚቃ ሰሪዎቹም ውሱን ናቸው፡፡ በሸራተን አዲስና በጣይቱ ሆቴልም የተጀመሩ የግለሰብ ሙከራዎች አሉ፡፡ ከነዚህ ግለሰቦች ጥረትም፣... ለወደፊቱ የጥበባዊ ሙዚቃ አፍሪቃዎችና አድማጮች ይፈጠራሉ፡፡ ቁጥራቸው ያነሱ ቢሆኑም ቅሉ ዛሬም አሉ፡፡ ወደፊት ደግሞ ይጨምራሉ፡፡ የዛሬዎቹ ግን ቢያንሱም በመሪነታቸው ብዙ ተከታዮችን ያገኛሉ፡፡ የሙላቱ አስታጥቄን ስኬት መመልከቱ ብቻ ይበቃል፡፡
ሙዚቃ በቃላት (ወይም በጽሑፍ) የሚገለጥና የሚከራከሩበት ጉዳይ አይደለም፡፡ ሙዚቃ በድምፅ የሚደረስ ወይም የሚጫወቱት፣ በሰሚውና በተጫዋቹ መካከል የሚደረግ የመንፈስ ግንኙነትና መግባባትን የሚፈጠር አስቸጋሪ የኪነ-ጥበብ ዘርፍ ነው፡፡ ስለዚህም፣ ለሙዚቀኛ በቃላት ኃይል መጠቀምና መልዕክቱን ማስተላለፍ ቅር ያሰኘዋል፡፡ ትንሽም ሆነ ትልቅ በሙዚቃ ምሳሌነት ያለው ሙዚቃዊ በረከት፣ ፍሬያማ ውጤት ሊያስገኝ ይችላል፡፡ ስለሙዚቃ ሰው ማወቅ የሚችለው በሙዚቃ ትምህርት ውስጥ ገብቶ ሲማር ነው፡፡ ያን ጊዜ፣ ብዙ ብዙ አሸናፊ ከበደዎች፣ ነርሲስ ናልባዲያኖች፣ ሙላቱ አስታጥቄዎችና ግርማ ይፍራሸዋዎች እናገኛለን፡፡ እነርሱም፣ የኢትዮጵያን ሙዚቃ ጥበባዊ ያደርጉታል፡፡ ዳግማዊ የሆኑ ያሬዶችን በጉጉት እንጠባበቃለን፡፡ የዚያ ሰው ይበለን!
*********************************************************************************
ምንጭ:--http://semnaworeq.blogspot.com

ሰኞ, ሜይ 20, 2013

ከስፖርቱ ዓለም

ጃፓናዊያን ሴቶች በፍቅር ያበዱለት የማራቶን ጀግና

                                            በ ፍስሃ ተገኝ
***************************************************
በአንድ ወቅት ጃፓናውያን ሴቶች አብረውት ለመሆን በቁጥር አንድነት የሚመኙት ጎረምሳ ነበር። እሱ ያለበትን ሁኔታ በንቃት ይከታተላሉ፣ ባዩት ቁጥር በደስታ ይጮሀሉ። ስለ ብራድ ፒት ወይም ዴቪድ ቤካም እያወራሁ አይደለም፤ ስለ አበበ ቢቂላ እንጂ። እ.አ.አ በ1961 ዓ.ም በጃፓኗ ኦሳካ ከተማ በተካሄደው የማራቶን ውድድር ላይ ተሳትፎ  በአሸናፊነት ካጠናቀቀ በኋላ በጃፓናውያን ሴቶች ልብ ውስጥ መግባት የጀመረው አበበ ቢቂላ በ1964ቱ የቶኪዮ ኦሎምፒክ ለመሳተፍ ወደጃፓን ሲሄድ በሰውነት አቋማቸው ከሚበልጡትና በእድሜ ከሱ ከሚያንሱት ፈርጣማና ጡንቸኛ አሜሪካዊን የኦሎምፒኩ ተሳታፊዎች ቦክሰኛው ጆን ፍሬዠርና ዋናተኛው ዶናልድ አርቱር ሾላንደር ይልቅ የሀገሪቷን ሴቶች ቀልብና ልብ መስረቅ ችሏል።
እ.አ.አ በ1932 ዓ.ም ሰሜን ሸዋ ጃቶ ውስጥ የተወለደው አበበ፤ ከእናቱ ጋር ለመኖር በሚል የትውልድ ቦታውን ትቶ ወደ አዲስ አበባ ከሄደ በኋላ በቅድሚያ ከከተማዋ የወደደው ነግር ቢኖር ጥርት ያለና ስርአት ያለው የደንብ ልብስ የሚለብሱት የአጼ ኃይለ ስላሴ ክቡር ዘበኛ አባሎች ነው። እናም በ1956 ዓ.ም አበበ ክቡር ዘበኛን ተቀልቀለ። ክቡር ዘበኛ ውስጥ በጥሩ ዋናተኛነት፣ በጎበዝ ፈረስ ጋላቢነትና በገና ተጨዋችነት ከመታወቁ በስተቀር በሩጫ ማንም ግምት አይሰጠውም ነበር።
በጊዜው የአበበ ቢቂላ አሰልጣኝ የነበሩት ሲውዲናዊው ኦኒ ኒስከነን አበበን አስመልክተው ሲናገሩ “ከ1959 ዓ.ም በፊት አበበን በጭራሽ አላውቀውም ነበር። የኦሎምፒክ የመጀመሪያ ማጣሪያ ውድድር ላይ ሶስተኛ ቢወጣም የሩጫ ብቃቱ አሳማኝ አልነበረም። ምክንያቱም እጆቹ እዛና እዚህ ሲወራጩ ማየትና የሚዛን አጠባበቅ ችግር አበበ ላይ ማየት የተለመደ በመሆኑ አንዳንድ ጊዜ እጮህበት ነበር። በርግጥ መስዋእትነት መክፈልንና ጠንክሮ መስራትን ከእሱ ጋር የሚስተካከል ማንም አልነበረም። ታላቁ አበበን የፈጠረው እራሱ አበበ ነው። እኔ ለእርሱ ታላቅነት ምንም አስተውጾ አላበረከትኩም” አሉ።
ወደሮም ለ1960ው ኦሎምፒክ ከመሄዱ በፊት ከኢትዮጵያ ውጪ አንድም ውድድር ያላደረገውና ሩጫን ዘግይቶ የጀመረው አበበ፤ ለኦሎምፒኩም የመጀመሪያ ተመራጭ አልነበረም። የመጀመሪያ ተመራጭ የነበረው ዋሚ ቢራቱ ጉዳት ደረሰበትና አበበ ዋሚን ተክቶ ቡድኑን ተቀላቀለና ጉዞ ወደ ሮም ሆነ።
የኦሎምፒኩ የማራቶን ውድድር ከመጀመሩ ሁለት ሰአታት በፊት አበበ ሌላ አስገራሚ ክስተት አጋጣመው። በውድድሩ ለአትሌቶች ጫማዎችን ሲያቀርብ የነበረው አዲዳስ በቂ ጫማዎች ስላልነበሩት ለአበበ እግር ይበቃሉ ተብለው የተገመቱ የተለያዩ ጫማዎች ቢሞከሩም ሊገኙ አልቻሉም፤ የተቃረቡትም ያበረከቱት አስተዋጾ ቢኖር አለመመቸትና እግሩን ማቁሰል ነበር። ሀገሩ በልምምድ ወቅት በአብዛኛው ያለጫማ ይሮጥ የነበረው አበበም “በባዶ እግሬ እሮጣለሁ” የሚል ሀሳብ አቀረበና አሰልጣኙም በሀሳቡ ተስማሙ።
ውድድሩ ተጀመሮ የርቀቱን ሩብ ያህል እንደሮጡ ከመሪዎቹ በትንሽ የሚርቀው አበበ ፍጥነቱን ጨመረና ቤልጄማዊው ኦውሬል ቫን ዴን ሬሽኽ፣ ብሪታኒያዊው አርቱር ኬሊ እና ሞሮኳዊው ራህዲ ቤን አብዲሰላም የሚገኙበትን የመሪዎቹን ቡድን ተቀላቀለ። የ42.196 ኪሎ ሜትሩን ግማሽ ካለፉ በኋላ አበበና ራህዲ ከሌሎች ተገንጥለው በመውጣት መሪነቱን ለብቻቸው ተቆጣጠሩ።

አበበ በሮም ጎዳናዎች ላይ በባዶ እግሩ ሲገሰግስ
ውድድሩ ከመጀመሩ በፊት አሰልጣኝ ኦነኒስከን የአበበ ተፎካካሪ 26 ቁጥር የተጻፈበት መለያ የሚለብሰው ሞሮኳዊው ራህዲ ሊሆን እንደሚችል በመገንዘባቸው ለአበበ “26 ቁጥር የለበሰው አትሌት ላይ ትኩረትህን አድርግ” የሚል መለክት አስተላልፈው ነበር። በሚገርም ሁኔታ ታዲያ ውድድሩ ከተጀመረ በኋላ ራህዲ የለበሰው 26 ቁጥር ሳይሆን 10 ሺህ ሜትር ሲሮጥ የለበሰው 185 ቁጥር የተጻፈበት ማሊያን መሆኑ ነው። ውድድሩ እየተጋመሰ ሲሄድ አበበ ወደ ግራና ቀኝ፣ እንዲሁም ወደኋላ ዘውር እያለ 26 ቁጥር የለበሰ ሲፈልግ ሊያየውና ሊያገኘው አልቻለም። ለካ ራህዲ አብሮት ከአበበ ቢቂላ አጠገብ በመሪነት እየሮጠ የነበረው 185 ቁጥር የለበሰው አትሌት ሆኗል።
ማራቶኑ ሊጠናቀቅ ሶስት ኪሎ ሜትሮች ያህል እስኪቀሩት ድረስ አበበና ራህዲ ጎን ለጎን አብረው ከሮጡ በኋላ፤ አበበ ፍጥነቱን ጨመረና ራህዲን በ200 ሜትሮች ያህል በመቅደም አንደኛ ወጥቶ ለኢትዮጵያና ለጥቁር አፍሪካ በኦሎምፒክ የመጀመሪያውን የወርቅ ሜዳሊያ አስገኘ። በስታዲዬሙ የተገኘውን ተመልካችና አለም አቀፉን መገነኛ ብዙሃን ያስገረመው ሌሎቹ ሯጮች ሲያለክልኩና ጥቂቶቹም ራሳቸውን መቆጣጠር አቅቷቸው ሲውድቁ፤ በባዶ እግሩ ማራቶኑን የሮጠው አበበ ስታዲየሙ ውስጥ ሲያሟሙቅና ሰውነቱን ሲያፍታታ ማየታቸው ነበር።
ከውድድሩ በኋላ የአበበ በባዶ እግር ሮጦ ማሸነፍ ያስገረማቸው ጋዜጠኞች አሰልጣኝ ኦኒ ኒስካነን ሁኔታውን እንዲያብራሩላቸው ሲጠይቋቸው “በባዶ እግሩ መሮጡ ምንም አያስገርምም። ልምምድ ላይ በባዶ እግሩ ሲሮጥ አንድ ደቂቃን በ98 ርምጃዎች ሲሸፍን፤ በጫማ ሲሮጥ ደግሞ ደቂቃን በ96 ርምጃዎች ሲሸፍን አይቻለሁ። እናም ብዙ ልዩነት አይኖረውም ብዬ ስላሰብኩ በባዶ እግሩ ተመችቶት እንዲሮጥ ወሰንን። ምን አልባት ጫማ በኮረኮንቻማ ቦታዎች ላይ ሊጠቅምህ ይችላል፤ ብዙ እግርህን ሊያቆስሉህ የሚችሉ ነገሮች ይኖራሉና። የሮም ጎዳናዎች ግን እንደዛ አይደሉም። ስለዚህ አበበ ‘በባዶ እግሬ ልሩጥና ለአፍሪካ ታሪክ እንስራ አለኝ፤ እኔም ተስማማሁ።’ በጣም አርበኝነት የሚሰማው ሰው ነው” የሚል ነበር መልሳቸው።
የአበበ ቢቂላ ወርቅ ሜዳሊያና የሞሮኳዊው ራህዲ ብር ሜዳሊያ በወደፊት የኦሎምፒክና የተለያዩ አለም አቀፍ ውድድሮች ላይ አፍሪካዊያን ሩጫን በበላይነት ሊቆጣጠሩ እንደሚችሉ ምልክት የሰጠ ነበር።

ቁጥር አንዱ አበበ ቢቂላ
በሮም የኦሎምፒክ ወርቅ ሜዳሊያ ባለቤት ከሆነ በኋላ በግሪክ፣ ጃፓንና ቼኮዝሎቫኪያ ላይ የተካሄዱ የማራቶን ውድድሮችን ያሸነፈው አበበ ቢቂላ እስከ ቶኪዮ ኦሎምፒክ መቃረቢያ ድረስ ያሉትን ጊዜያት በጥሩ ሁኔታ አላሰለፈም ማለት ይቻላል። የአበበን በጥሩ አቁም ላይ አለመገኘት የተገነዘቡት በርካታ የዘርፉ ባለሞያዎችና መገናኛ ብዙሀን ከኦሎምፒኩ መጀመር አራት ወር ቀደም ብሎ አዲስ የአለም የማራቶን ክብረወሰንን 2 ሰአት ከ13 ደቂቃ 55 ሰከንድ በሆነ ጊዜ ያስመዘገበው ብሪታኒያዊው ቤንጃሚን ባሲል ሄትሊ የቶኪዮው ኦሎምፒክ ወርቅ ሜዳሊያ ባለቤት ይሆናል የሚል ግምት ሰጡ። ይባስ ብሎ አበበ ጠንካራ ልምምዶችን በማድረግ ድክመቱን ለማካካስ ጥረት እያደረገ እያለ የትርፍ አንጀት ህመም አጋጠመውና ኦሎምፒኩ ከመጀመሩ ከአራት እስከ ስድስት ሳምንታት ቀደም ብሎ የቀዶ ጥገና ህክምና በማድረጉ ልምምዱ ተሰናከለ። ሆኖም ልክ ሀኪሞቹ ለአሰልጣኝ ኒስከነን እንደነገሯቸው አበበ በቶሎ አገገመና የቀዶ ጥገና ህክምናውን ካደረገ ከሁለት ሳምንታት ቆይታ በኋላ ልምምድ መስራት ጀመረ።
ለኦሎምፒኩ ማሟሟቂያና ማጣሪያ እንዲሆን አዲስ አበባ ውስጥ በተካሄደ የማራቶን ሩጫ ውድድር ማሞ ወልዴን በአንድ ሰከንድ ቀድሞ አንደኛ የወጣው አበበ ያስመዘገበው 2 ሰአት ከ16 ደቂቃ 18.8 ሰከንድ የሆነ ጊዜ ምን አልባትም ሁለተኛ የወርቅ ሜዳሊያውን ለማግኘት እድል እንዳለው ያሳየ ነበር።
64 ተወዳዳሪዎች በተሳተፉበት የ1964ቱ የቶኪዮ ኦሎምፒክ የማራቶን ውድድር ሻምበል አበበ ቢቂላ ርቀቱን ለማጠናቀቅ 10 ኪሎ ሜትሮች እስኪቀሩ ድረስ መሪነቱን በተረጋጋ ሁኔታ ለመያዝ ቻለ። ብዙም ሳይቆይ ታዲያ አበበ ከሌሎቹ አትሌቶች ተገንጥሎ ወጣና ለብቻው መሪነቱን በመቆጣጠር ብሪታኒያዊውን የአለም ክብረወሰን ባለቤት ባሲል ሄትሊን በአራት ደቂቃዎች ልዩነት ቀድሞ 2 ሰአት ከ12 ደቂቃ 12.2 ሰከንድ በሆነ ጊዜ የአለም ክብረወሰንን በመስበር አንደኛ ወጥቶ ለሁለተኛ ጊዜ የኦሎምፒክ የወርቅ ሜዳሊያ ባለቤት ሆነ።
አሶሺዬትድ ፕሬስ ሁኔታውን እንዲህ በማለት ነበር የዘገበው። “አበበ ተከታዩን በሰፊ ልዩነት በመቅደም ወደቶኪዮ ስታዲዬም ከገባ በኋላ ሁለት እጆቹን ወደላይ አንስቶ የመጨረሻውን ገመድ በደረቱ በጥሶ አንደኛ ወጣ። ከዛም ወደሜዳው መሀል ገባና ሳሩ ላይ በጀርባው ተኝቶ እግሮቹን ልክ የብስክሌት ፔዳል እንደሚመታ ሰው አይነት እያወራጨ በማፍታታት ስታዲዬም የተገኘው ተመልካችን አስደመመ።”
ከቶኪዮው ወርቅ ሜዳሊያ በኋላ አበበ በ1965 ዓ.ም ወደ ጃፓን በመመለስ የኦትሱ ማራቶንን አሸነፈ። በቀጣዩ አመት ደግሞ የባርሴሎናው ዛራውትዝ ማራቶንን በማሸነፍ ለ1968ቱ የሜክሲኮ ኦሎምፒክ ዝግጁ መሆኑን ለአለም አረጋገጠ። የ36 አመቱ አበበ ቢቂላ ለሶስተኛ ተከታታይ ጊዜ የማራቶን ወርቅ ሜዳሊያን ለማግኘት ሜክሲኮ ሲገባ በጥሩ አቋም ላይ ይገኝ ነበር። እሱ እራሱ በጊዜው በሰጠው አስተያየት “በጣም በጥሩ አቋም ላይ ስለምገኝ አሸንፋለሁ ብዬ እጠብቃለሁ። ነገር ግን በእንደዚህ አይነት ረጅም ሩጫ ያልተጠበቀ ነገር ሊፈጠር ይችላል። ያልተጠበቀው ተከስቶ የምሸነፍ ከሆነ በሀገሬ ልጆች ማሞ ወልዴና መርሀዊ ገብሩ ብሸነፍ ይሻለኛል” አለ።
የሜክሲኮው ኦሎምፒክ የማራቶን ውድድር ከመጀመሩ በፊት የነበሩት አራት ቀኖች ለአበበ መጥፎ ጊዜዎች ነበሩና ቀናቶቹን በህመም አሳለፈ። ውድድሩ ተጀምሮ 10 ኪሎ ሜትሮች ያህል እንደሮጠ ታላቁ አትሌት ውድድሩን አቋርጦ ወጣና ሌላው ኢትዮጵያዊ ማሞ ወልዴ አንደኛ በመውጣት አሸንፎ የወርቅ ሜዳሊያ ባለቤት በመሆን ለኢትዮጵያ ሶስተኛውን ተከታታይ የማራቶን ወርቅ ሜዳሊያዎች አገኘ።

ቀስተኛው አቤ ለድል ሲያነጣጥር
መጋቢት ወር አጋማሽ 1969 ዓ.ም ላይ ይነዳት የነበረችው ፎልስቫገን መኪና ተገልብጣ አደጋ የደረሰበትና እግሮቹ ፓራላይዝ የሆኑት ሻምበል አበበ ቢቂላ፤ እነዛ የወርቅ ሜዳሊያዎች ያስገኙለት አስደናቂ እግሮቹን ወደስራ እንደገና ለመመለስ ህክምናዎችን ቢያደርግም የተደረገው የህክምና ጥረት ውጤታም አልሆነም። የመጨረሻ አማራጭና ተስፋ በሚል ወደእንግሊዝ ተወስዶ በስቶክ ማንዴቪል ሆስፒታል ህክምና ቢደረግለትም አበበን እንደገና ወደሩጫው መመለስ ሳይቻል ቀረ። ታዲያ ተስፋ የማይቆርጠው አበበ “መሮጥ አልችልም” ብሎ ከስፖርቱ አለም ከመራቅ ይልቅ ራሱን ወደቀስት ወርዋሪነት አሸጋገረና በእግሮቹ ያገኛቸውን ድሎች በእጆቹም ለመድገም ወሰነ። ምንም እንኳን እንዳሰበው ውጤታማ ባይሆንም በ1969 ዓ.ም በተካሄደው የዊልቸር ኦሎምፒክ በጀማሪ ቀስት ወርዋሪዎች ክፍል ተወዳድሮ ዘጠነኛ ደረጃን አግኝቶን ጨረሰ።
የሚያሳዝነው ነገር ታላቁ አበበ ቢቂላ ገና በ41 አመቱ በ1973 ዓ.ም ከዚህ አለም በሞት ተለየና የአትሌቲክስ ስፖርት አፍቃሪው አለምና ኢትዮጵያ ታላቅ ሰው አጡ።
በቅርቡ የአለም አቀፉ አትሌቲክስ ፌዴሬሽኖች ማህበር መቶኛ አመት ምስረታን አስመልክቶ የስፖርቱ የታላቆች ታላቅ ተብለው ከተመረጡት ቀዳሚ 12 አትሌቶች መካከል ኢትዮጵያዊው ጀግና አበበ ቢቂላ አንዱ ነበር። ወረቀት ላይ ከተነደፉ እቅዶች ይልቅ የራሱን የተፈጥሮ የሩጫ ችሎታን እና ነገሮችን እንደየአመጣጣቸው የማንበብ ብቃቱን በመጠቀም ታላቅ ታሪክን የሰራው የአበበ ቢቂላን ሩጫዎች ያላዩ ታሪኩን ሲሰሙ የአፈታሪክ ያህል ነው የሚሆንባቸው። “ማራቶንን በባዶ እግሩ ሮጦ መጨረስ ብቻ ሳይሆን አንደኛ ወጥቶ የወርቅ ሜዳሊያ ባለቤት የሆነ አትሌት አለ” ብሎ አንድ ሰው ጎዳና ላይ ላገኘው ሰው ቢያወራ “አብደሀል ወይ፤ ለምን የማይሆን ነገር ታወራለህ” ነው የሚባለው። አበበ ግን ተአምረኛ ነበርና አድርጎታል፤ ለሰሚ እውነት የማይመስል እውነትን ያውም በታላቁ ኦሎምፒክ ላይ ፈጽሟል።
******************************************************************************
ምንጭ:---http://www.total433.com

ኪነ ጥበብ

ፊልም፣ "ሰባተኛው ስነ-ጥበብ"
በሰሎሞን ተሠማ ጂ. (semnaworeq.blogspot.com)
የአንድ ሀገር ህዝብ በጦር ሜዳ ግንባር የመጣበትን ወራሪ ጠላት መክቶ በድል አድራጊነት ቢወጣ ባለድል መሆኑ እሙን ነው፡፡ ድሉ በወታደራዊው ጦርነት የመጨረሻውን ትግል አድርጎ ለማሸነፉ ምስክር ነው፡፡ በባህሉና በማንነቱ በኩል ግን የሚመገበው፣ የሚለብሰውና የሚነጋገርበት ዘዬ፣ ወራሪዎቹ ትተውት የሄዱትን ርዝራዥ ብኂል ነው፡፡ ጦርነቱ ብርቱ ብርቱ የጦር አበጋዞችን እንጂ፣ ቆራጥ የባህል ጠበቆችን ወይም ስለባህልና ስለሥነ-ጥበብ ተምረው የተዘጋጁ ኃይሎችን (ልሂቃን) ስላላዘጋጀ፣ ከፍ ያለ የጥበባዊ ሽንፈት ይከተላል፡፡ የባዕዳንን ርዝራዥ ባህል በሲኒማና በመዝናኛ ውጤቶች እየተመገበ የሚያድግ ወጣት እንደምን አድርጎ የራሱን ታሪክ ሊተርክ ይችላል? እንዴትስ የራሱን እሴቶች ዋጋ ሊሰጥ ይችላል? ስለሆነም ወጣቱ  የውንብድናና የወላባነትን ባህሪ ብሂሉ ያደርገዋል፡፡ የደቡብ አፍሪካ፣ የቬትናም፣ የላቲን አሜሪካንና የበርካታ የመካከለኛው ምስራቅ አገር ሕዝቦች የጦር ሜዳ ወራሪዎቻቸውን በወኔ ቢመክቱም ቅሉ፣ የወረራቸውን የምዕራባዊያን ባህል ማሸነፍ አልቻሉም፡፡ ምክንያቱም፣ ኤድዋርድ ሳይድ፣ Orientalism በተሰኘው መጽሐፉ ውስጥ እንዳተተው፣ “መሪዎቹና ሕዝቡ ሙሉ ኃይላቸውን ጦርነቱ ላይ አድርገውት ስለቆዩ፤ ታሪካቸውን፣ ባህላቸውንና ማንነታቸውን በዝንጓዔና በቀልበ-ቢስነትም ስለሚዘነጉት ነው” ይላል፡፡   
ኢትዮጵያዊያንም የአድዋንና የአምስቱን ዓመት የፀረ-ወረራ ትግል ካካሄዱ በኋላ ታሪካቸውንና ባህላቸውን እንዲዘነጉ የጣሊያን ወራሪዎችም ሆኑ ቆንስላዎቹ ያልተቆጠበ ጥረት አድርገዋል፡፡ ፕሮፌሰር ሥርግው ኃብለ ሥላሴ “ዳግማዊ አጼ ሚኒሊክ፣ የአዲሱ ሥልጣኔ መስራች” በተባለው መጽሐፋቸው ላይ እንደገለጹት “የመጀመሪያው የሲኒማ ቤት በአንድ የፈረንሳይ ተወላጅ በ1890ዎቹ ተከፍቶ የነበረ ቢሆንም ቅሉ፣ በዚያን ጊዜ አዲስ አበባ ውስጥ የነበሩት የውጭ አገር ሰዎች ቁጥር መጠነኛ ስለነበረ፣ ያሉትም ሲኒማ ለማየት ስላልፈለጉ፣ ኢትዮጵያዊያኑም ቶሎ ስላልለመዱ ኪሳራ ላይ ወደቀ፡፡ የሲኒማ ቤቱ ባለቤትም ይህ ንግድ እንደማያዋጣው ስላወቀ መሣሪያውን ለኢጣሊያው ሚኒስትር ቺኮዲኮሳ ሸጠለት” (ገጽ 444)፡፡ ቺኮዲኮሳም የሲኒማ ማሳያውን፣ አፄ ሚኒሊክ ለአዲስ ግኝት የነበራቸውን ጉጉት ስለሚያውቅ ገጸ በረከት አቀረበላቸው፡፡ በደስታም ተቀበሉት፡፡ አንድ የአርመን ተወላጅ እያንቀሳቀሰው ለብዙ ጊዜ ንጉሱና ንግስቲቱ ሲኒማ ሲያዩ ከቆዩ በኋላ በድንገት ተሰናከለ፡፡ አውቶሞቢል ይዞ የመጣው እንድሊዛዊው ቤንትሌይ ጠግኖት እንደገና መታየቱ ቀጠለ (ፕ/ር ሥርግው፤ ገጽ 444)፡፡
በ1902 ዓ.ም የመጀመሪያው ሲኒማ ቤት ቴድሮስ አደባባይ አጠገብ “ፓቲ” የሚሰኘው ሲሆን (የዛሬው ሜጋ አምፊ ቴያትር ያለበት ቦታ ላይ) የተከፈተ ሲሆን ያቋቋሙትም ሁለቱ ወንድማማቾች ነበሩ፡፡ ምንም እንኳን የፈረንሳይ ተወላጆች ቢሆኑ፣ የጣሊያን ዜግነት ነበራቸው፡፡ ሕዝቡም ሲኒማ ቤቱን “የሰይጣን ቤት” እያለ ነበር የሚጠራው፡፡ ከ1908 እስከ 1926 ዓ.ም ድረስም አምስት ሲኒማ ቤቶች ተከፍተው ሲኒማ ያሳዩ ነበር፡፡ የኢጣሊያ ወራሪዎች ወደአዲስ አበባ ሲገቡ ከሰይጣን ቤት በስተቀር ሁሉም ሲኒማ ቤቶች ተቃጠሉ (የፊልም ማዳበሪያና መቆጣጠሪያ ዋና ክፍል፣ ገጽ 4-7)፡፡
ሆኖም ወራሪው ኃይል የሲኒማን ጠንከራ የፕሮፓጋንዳ መሣሪያነቱንና ኃይሉን ስለተረዳ በአጭር ጊዜ ውስጥ የተቃጠሉትን ሲኒማ ቤቶች አድሶ፤ ሲኒማ ኢታሊያ (የዛሬው ሲኒማ ኢትዮጵያ ነው)፣ ሲኒማ አምፒር (አሁንም በቦታው ላይ አለ)፣ ሲኒማ ማርኮኒ (አሁን የብሔራዊ ቲያትር ሕንፃ ያረፈበት ቦታ ላይ ነበር)፣ ሲኒማ ቺንኮ ማጆ (አራት ኪሎ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ሣይንስ ፋኩሊቲ ቅጥር ግቢ ውስጥ ይገኝ ነበር)፣ ሲኒማ ዲ መርካቶ (የዛሬው ራስ ቴያትር ነው)፣ ሲኒማ ዲፖላቮሮ (የተግባረ ዕድ ት/ቤት የፊት ለፊቱ ህንፃ ወስጥ) እና በድሬዳዋ ሲኒማ አምፒርና ሲኒማ ማጀስቲ የተባሉትን፤ በሐረር ሲኒማ ዲ ሮማን፣ በጅማና በጎንደር እንዲሁም በደሴ ሲኒማ ቤቶችን የወራሪ ኢጣሊያን ሹማምንትና ዜጎቻቸው ከፍተው ነበር (የፊልም ማዳበሪያና መቆጣጠሪያ ዋና ክፍል፣ ገጽ 4-7)፡፡
ከላይ የቀረቡት ማስረጃዎች እንደሚያሳዩት ከሆነ፣ በአድዋና በሌሎችም የጦር ግንባሮች የተመከተው የወራሪ ኢጣሊያ ኃይል፣ የኢትዮጵያውያንን መንፈስና ወኔ ለማኮላሸት ሲኒማን እንደትልቅ የፕሮጋንዳ መሣሪያ ስለመጠቀሙ ነው፡፡ ታዳጊዎቹ ኢትዮጵያውያንም የራሳቸውን ታሪክ ሳያውቁ፣ የወራሪውን ኃይል ስልጣኔና ዕድገት ያለምንም ከልካይ እንዲጋቱ ተደረጉ፡፡ ስለሆነም፤ “ሀ፣ ራስህን እወቅ!” የሚለው መሪ-ቃል ተዘንግቶ “ለ፣ ሌሎችን አጥና! ሌሎችንም ምሰል!” ወደሚል አጓጉል ፈሊጥ አሽቆለቆለ፡፡ ይባስ ብሎም፣ “የሌሎችን ታሪክና ኪነ-ጥበብ ኮርጅ፣ የሌሎችንም ሥነ-ጥበብ ቅዳ!” ወደሚል አዘቅት ውስጥ ጅው ብሎ ገባ፡፡ ይኼው የመውጫው ጭላንጭል የጠፋቸው የፊልም ሰሪዎች በተለይ፣ የጥበብ ባለሙያዎች በጅምላ በሥመ-አርቲስትነት ጭለማ ውስጥ ገብተው ይደናበራሉ፡፡              
                        ***************************************      


የፊልም “ዘይቤ” ማለት የፊልምና የሲኒማ “ምንትነት”ን ለመበየን የሚውል ትርጓሜ ነው፡፡ “ፊልም” የተንቀሳቃሽ ምስሎች ሁሉ የወል ስያሜ ነው፡፡ ለብዙኃኑ፣ “ፊልም” ማለት የእንግሊዝኛውን ‘movie’ እንደማለት ነው፡፡ የእንግሊዝኛው ‘movie’ ልማዳዊ ባህልን እንጂ ጥበባዊነትን አይገልጽም፡፡ የፈረንሳይኛው ሲኒማ (cinema) ስርወ-ቃሉ እንደሚያመለክተው ከግሪክኛው ‘kineine’ ተንቀሳቃሽ ምስል or ‘to move’ ጋር የተወራረሰ ነው፡፡ ተንቀሳቃሽ ምስሎቹም ጥበባዊ ለሆነ ፋይዳ እስከዋሉና ጥበባዊነታቸውንም እስከጠበቁ ድረስ “ሲኒማ” ናቸው (Anatomy of Film, 2005: 1-2)፡፡
የሲኒማነት ደረጃ ላይ የደረሱ ፊልሞች ሊያሟላቸው የሚገባቸው አራት ነገሮች አሉ፡፡ አንደኛ፣ የመተረክ ዕውቀትና ክህሎት ነው፡፡ ለመተረክ ደግሞ የራስን ታሪክ ማወቅ ያስፈልጋል፡፡ አንድ ሰው የራሱን ታሪክ ሳያውቅ አንደምን አድርጎ የሌሎችን ታሪክ ለመተረክ ይችላል? የራስን ታሪክ ማወቁ ሁለት ጠቀሜታዎች አሉት፡፡ በመጀመሪያ፣ በራስ ታሪክ ላይ እምነት ለማሳደር ማስቻሉ ነው፡፡ የራስን ታሪክ አውቆና አቀላጥፎ መተረክ የሚችል፣ የሌሎችም ታሪክ ለመተረክ ይችላል (ሃይሌ ገሪማ፣ 1996)፡፡ ቀጥሎም፣ የራስን ታሪክ ካለማወቅና ካለመተረክ የሚመነጩ ችግሮች ዞሮ ዞሮ ወደ ኩረጃና ወደ ጥራዝ-ነጠቅነት ስለሚከቱ ውጤቱ አደገኛ ነው የሚሆነው፡፡
የሲኒማነት ደረጃ ላይ የደረሱ ፊልሞች በሁለተኛነት ሊያሟሉ የሚገባቸው ነጥብ አለ፤ እርሱም ብሔራዊ እውነትና ውበት እንዴት እንደሚሰምር መረዳት ነው፡፡ “እውነት” ሲባልም የከያኒው ውስጣዊ እምነትና አቋም ከከያኒው ውጫዊና ከባቢያዊ እውነታ ጋር የታረቀና ስምም እንዲሆን ማድረግ ነው፡፡ ራሱ የማያምንበትን ነገር ለሌሎች መናገርም ሆነ፣ የሌሎችን እውነት ክዶ መሟገት ትርፉ ባዶ ልፈፋ ነው፡፡ ብሎም ለፕሮፓጋንዳና ለወቅታዊ ፍጆታ ሰልፈኛ ከመሆን አያድንም፡፡ መገናኛ ብዙኃን ዓባይ-ዓባይ እያሉ ሲያላዝኑ ሰምቶ፣ “ዓባይ” ወይም ናይል ብሎ መስገብገብ ትርፉ ባዶ ነው፡፡ ስለባህር በር ጉዳይ ወቅታዊ አጀንዳ ሲሆንም “የባህር በር” ብሎ መጣደፍ ትዝብት ላይ ይጥላል፡፡ እነዚያን “ፊልሞች” ከጥቂት አመታት በኋላ ዞር ብሎም የሚያየው ተመልካች አይገኝም፡፡ የፊልም ሰሪውንም ለእውነት ያልቆመና ሸቃይ መሆኑን ያጋልጣል፡፡
በወቅታዊ ጉዳይ ላይ በስገብገብም የፊልም ስራውን በተለይ፣ የስነ-ጥበቡን ዘርፍ ባጠቃላይ ቅጥ የለሽ (Formless) ያደርገዋል፡፡ ከአርስቶትል ጀምሮ እስካሁን ድረስ የተነሡት የስነ-ውበት ሊቃውንት እንደሚያስገነዝቡት ከሆነ፣ ያለቅርጽ ምንም ዓይነት ውበት መግለጫ መንገድ የለም፡፡ “ሲያዩት ያላማረ….” የሚለው የሃገራችን አባባል ከንጽሕና ጋር ባቻ ሳይሆን ከቅርጽ ጋርም ቀጥተኛ ግንኙነት አለው፡፡ ስለሆነም፣ ስነ-ውበትን መረዳትና ለኪነ-ጥበባዊ ስራውንም ተስማሚ ቅርጽ መስጠት የአንድ ከያኒ ግዴታው ነው፡፡ “የፊልም ይዘቱና የአቀራረብ ስልቱም ስነ-ጽሑፋዊ ነውና ቅርጽና ቅጥ ያስፈልገዋል፤” ይላል በርናርድ ዲክ Anatomy of Film በተባለው መጽሐፉ ውስጥ፣ ገጽ 254-6 ይመልከቱ)፡፡
በሦስተኛ ደረጃም፣ አንድ የፊልም ሠሪ ስለቋንቋውና በቋንቋው አማካይነት ሊያስተላልፈው ስለሚፈልገው እውነትና ውበት ትክክለኛ አቋም ሊኖረው ይገባል፡፡ የብዙኃኑን ሕይወትና አኗኗር ለማሳየት ተነስቶ የተንጣለለ የተውሦ ቪላና ፎቅ ቤት ውስጥ መንከላወስ የቋንቋ እጥረትን ያስከትላል፡፡ ስለሆን፣ ከያኒው ስለሚያውቀውና እየኖረበት ስላለው ሕያወት ቢተርክ ያዋጣዋል፡፡ እውነታውን በሚያውቀውና በገባው መልኩ ሌሎች እንዲያውቁትና እንዲገባቸው ለማድረግ ቋንቋና እውነታ እንደሰልባጅ አያጥረውም፡፡ የፈረደባቸው የዩኒቨርሲቲ ፕሮፌሰሮችና ፖለቲከኞች፣ ቀሳውስትና ባለጸጐች ላይ ፊጥ ከማለቱ በፊት የራሱን ኑሮና ሕይወት፣ ታሪክና እምነት መርምሮና ተፈላልጎ መጻፍ ከግልብነት ያድናል፡፡ የፕሮፌሰሩን የመነጽር አደራረግና አስተያየት ሳይመረምሩ፣ ወይም የኢንቨስተሩን ሚስት የመዋቢያ ቁሳቁስ አጠቃቀምና አኳኋን ሳያጠኑ፣ የአዛውንቱን የእጅና የፊት እንዲሁም የሰውነት እንቅስቃሴዎች ከነለዛቸው ሳይረዱና ሳያውቁ የተዋናዩ ላንቃና መንጋጋ ውስጥ ለመጠቅጠቅ መጀል አጉል ነው፡፡ የፊልም ሠሪ መጀመሪያውኑ ስለባለታሪኮቹ ማንነትና ስለሚናገሩት ቋንቋም በቅጡ ሊያውቅ ይገባዋል፡፡
በአራተኛ ደረጃም፣ አንድ የፊልም ሠሪ የፈጠራቸው ገጸ-ባህሪያት ባለው ህብረሰብ፣ ባህል፣  ተፈጥሮና በስርዓቱ ጉድፎች ላይ የሚያምጽ መሆን አለበት፡፡ ዓመፁም ለበጎ ነው፡፡ ለለውጥ ነው፡፡ ወደ ለውጥ ነው፡፡ የሰው ልጅ ታሪክ የማያቋርጥ የለውጥ ሂደትና ትግልም ነው፡፡ የለውጥ ትግሉና መፍጨርጨሩም ስልጣኔን ለማወጅ ነው፡፡ ሥልጣኔ፣ የብዙ እሴቶች ድምር ነው፡፡ ሰው ወደ ፍትህ፣ እኩልነት፣ ሠላም፣ ፍቅር፣ እውነት፣ ነፃነትና ሌሎችም ረቂቅ እሴቶች ዝንት ዓለም ሲፍገመገም ይኖራል፡፡ በፊልም ወስጥ ያሉት ገጸ-ባህሪያትና ፊልሙም ሰብዓዊ ውበትንና እውነትን ለማምጣት ስለሚታገሉና ስለሚያምጹ ሰዎች መሆን ይገበዋል፡፡ ሲረገጡና ሲበደሉ፣ “በጄ!.....እሺ!....አሜን!....ወይም ተመስጌን!” የሚሉ ልፍስፍስ ባለታሪኮችን ይዞ የሚነሳ ፊልም ሠሪ ሁለት ግድፈቶችን ፈጽሟል፤ አንደኛ፣ የሰው ልጅ በለውጥ ጅረት ውስጥ ወደ ስልጣኔ የሚያደርገውን በውጣ ውረድ የተሞላ ትግልና፤ ሁለተኛም፣ ከያኒው ለሰብዓዊ ውበትና ክብርም ያለውን ዝቅተኛ ግንዛቤ ያሳያሉ፡፡
ከላይ የጠቀስኳቸውን አራት ነጥቦች ቸለል ካልናቸው ወደብሔራዊ የፊልም ግብና ዓላማ መቼውንም አንደርስም፡፡ ዛሬ በተስፋና በጉጉት ለሰዓታት ፊልም ቤቶች ደጃፍ ላይ ተሰልፎ ለማየት የተነቃነቀው ተመልካቸም ደብዛው የጠፋል፡፡ የተመልካቹ ንቃተ-ሕሊናም እያደገና እየጎለበተ ነው፡፡ በTV-Africa ፋንታ፣ ደህና ደህና ፊልሞችን በተለያዩ Channels በማየት ላይ ነው፡፡ በተንቀሳቃሽ ምስሎች በኩል ንቃተ-ሕሊናው እያደገ ነው፡፡ ዓይኖቹንና ቀልቡን ከተንቀሳቃሽ ምስልና ከቴክኖሎጂ ጋር እያለማመደ ነው፡፡ አንድ ቀን፣ ዛሬ ላይ የተሠሩለትንና የተሠሩበትን “ነገሮች” አሽቀንጥሮ ይጥላቸዋል፡፡  
***************************************
      
የአገራችን ፊልም ሞካሪና ሠሪ “ነን ባዮች” የፊልምንና የሲኒማቶግራፊን ዘይቤዎች በቅጡ ሳይረዱ፣ ድርጉስ ብለው ከገቡ በኋላ አጉል መንፈራገጥ ላይ ናቸው፡፡ ፕሮፌሰር ሃይሌ ገሪማ በታኅሣሥ 2001 ዓ.ም እንደገለጸው፣ “ወደ ፊልም ድርጉስ ብለው የመጡት ወጣቶች በመምጣታቸው መበበረታታት አለባቸው፡፡ ሆኖም፣ ፊልምና ሲኒማቶግራፊ ከባድ ዋናተኛ መሆንንና የሲኒማ ቋንቋንም መልመድ የግድ ይፈልጋል፡፡ በተለይም ‘ከቋንቋው ጋር የእኔ ባህልና የምሠራው ፊልም ዘይቤ እንዴት ነው የሚዛመደው?’ ብሎ ፊልም ሠሪው ራሱን መጠየቅ አለበት፡፡”
በአገራችን ለወጣቶች አእምሮ መደናበር አንዱ ዋና ምክንያት፣ ከውጭ እየተግበሰበሰ የሚገባው ዝባዝንኬ ፊልምና ስነ-ጥሑፍ መሆኑ እሙን ነው፡፡ ጥሩ ቴአትር አቅርቦ ብዙ ተመልካች ያጣ አንድ ዝነኛ ደራሲ፣ “አዝናለሁ ከነቶም ክሮዝና ከነብራድ ቢት ጋር መወዳደር አልችልበትም!” ሲል ተደምጧል፡፡ እውነቱን ነው፡፡ ነገር ግን ፈላጊ አለው ተብሎ ደግሞ የባሕር ማዶውን ዝባዝንኬና እንቶፈንቶ ዓይነት በኢትዮጵያችንና በኢጥዮጵዩውያንም ዘንድ እንዲስፋፋ አያስፈልግም፡፡ መፈቀድም የለበትም፡፡ ግባችን የሰብዓዊነትን ውበት የሚያሳምር፣ የአዲሲቱን ኢትዮጵያዊነት ባሕሪ የሚያጎለምስና የረቀቀ ሥነ-ጥበብ መሆን አለበት፡፡ “አዲሱን ኢትዮጵያዊነት” ሲባልም፣ ወደዕድገትና መሻሻል ለመገሥገሥ በፖለቲካ፣ በኢኮኖሚ፣ በወታደራዊ፣ ማህበራዊና በሥነ-ጥበብ መስኮችም የሚዋትተውን ሕዝብ ውጣ ውረድ መስታወት ሆነው ማሳየት አለባቸው፡፡
ፊልምን ከመስታወት ጋር የሚያመሳስሉት ብዙ የማርክሲዝምን ፈለግ የሚያቀነቅኑ ሊቃውንት አሉ፡፡  “በፊት መስታወት አማካይነት አንድ ሰው መልኩን አይቶና መርምሮ ለማሳመር ይችላል፡፡ በፊልም አማካይነትም አንድ ሰው ወይም ሕዝብ መልኩን፣ መንፈሱን፣ ሞራሉንና በጠቅላላው አኗኗሩን ተመልክቶና ተመራምሮ፣ ስሕተቱን ለማረምና ኑሮውንም ለማቃናት ፊልም የዋጋ ድልድል አለው” ይላሉ፡፡ ለነዚህ ሊቃውንት ፊልም ከሰፊው ሕዝብ ጋር የመገናኛ ዘዴ (means of Communication) ነው፡፡
ይህ እውነት ነው፡፡ ምክንያቱም ፊልም፤ የስነ-ጽሑፍን፣ የፎቶግራፊን፣ የሙዚቃንና የዳንስን፣ የቲያትርንና የሰርከሥን፣ የስዕልን፣ የምትሃትን (የአስማትን)ና የሌሎችንም ጥበባዊ ዘርፎች ባንድነት አዋሕዶ የያዘ በመሆኑ “ሰባተኛው ስነ-ጥበብ” ብለው የሚጠሩትም አልጠፉ (ሲን ኩቢት፣ History of Ideas በተባለው መጽሐፍ ውስጥ በገጽ 327 ላይ እንደገለጸው) ነው፡፡ በተመልካቹም ዘንድ ከፍተኛ የሆነ ግምት አለው፡፡ የፊልም ስራ ንግድን ብቻ ሳይሆን፣ ስነ-ጥበባዊ በሆነ አቀራረቡ ከዋነኛዎቹ የመገናኛ ብዙኃን ዘዴዎች መሃከልም አንዱ ነው፡፡ በመሆኑም፣ “የፊልም ሠሪው ከባድ ሕዝባዊ ኃላፊነት ያለበት ነው” ይላሉ የማርክሲስት ፈለግ አቀንቃኝ ሊቃውንት፡፡
ያምሆነ ይህ፣ አንድ ብሔራዊ ፊልም፣ መመሥረቱና የፊልም ስራ ሙከራው መጀመሩ ምስጋናና መደፋፈር የሚገባው ቢሆንም፣ ቀጣዩቹ ፊልሞች አባት እንደሌለው ዲቃላ “…አባቷ ማነው?” ወይም ….የራሳችን የመረጃና የደሕንነት ቤት እንደሌለን ሁሉ “FBI” ማለቱ፣ ወይም የራሳችን የሚስጥርና የማዕከላዊ ድርጅት እንደሌለን ሁሉ “CIA” መሆኑ ያስተዛዝባል፡፡ ይባስ ብሎም እንደወረደ The Mechanic የሚለውን “ሜካኒኩ”፣ The Transporter የመለውን “ባለታክሲው፣ ቅብርጥሱ” ማለቱ፣ የፊልም ሥነ-ጥበባችን አንዳችም ብሔራዊ ግብና ዓላማ የሌለው “ድቅል” መሆኑን ያሳብቃል፡፡ (ይኼ ሁሉ ሃተታ የቀረበው ወደ ፊልሞቹ ይዘትና መልዕክት ገና ሳንገባ ነው፡፡ ወደዚህ ጉዳይ ላይ በቀጣዮቹ ጽሑፎቼ ተራ በተራ እመለስባቸዋለሁ፡፡)
ብሔራዊ ግብና ዓላማ ያለው ፊልም ስለመደርጀቱ ጉዳይ ተስፋዬና እምነቴ በታዳጊ ወጣቶቹ ላይ ነው፡፡ እውቀትንና ብሔራዊ ስሜትን ከጥበባዊነት ጋር አጣምረው ዕፁብ-ድንቅ ፊልሞችን እንደሚያሳዩን  የጸና ዕምነት አለኝ፡፡ የፊልም ቋንቋን ከቲያትራዊ ቋንቋና ትወና ለይተው ያወቁ፣ የራሳቸውን ታሪክና ባህል በትክክል የተረዱ፣ ታሪክን መተረክ የሚችሉ፣ እውነትንና ውበት አጣምረው መመርመር የሚችሉ፣ የሚናገሩትን ቋንቋና የባለ-ታሪኮቹንም ቋንቋ በደንብ ያወቁ፤ ብሎም ለሰብዓዊ ክብርና ውበት ዕቁብ ያላቸው ወጣቶች ወደመድረኩ በድንገት ብቅ እንደሚሉ አልጠራጠርም፡፡ እንደሻንበል አበበ ቢቂላ በባዶ እግራቸው ሮጠው ታሪክ የሚሰሩ የፊልም ስነ-ጥበብ ባለድሎችን በቅርቡ እናገኛለን፡፡ (የዚያ ሰው ይበለን!!!)    
****************************
ምንጭ፡-http://semnaworeq.blogspot.com

ረቡዕ, ፌብሩዋሪ 13, 2013

ከመጻሕፍት ዓለም

“ዣንቶዣራ” ዓይናችንን የገለጠልን ልብወለድ! 

በእርግጥ የቀዳሚ እና የተከታይ ደረጃ ለመስጠት ያዳግተኛል፡፡ ይስማዕከ ግን በአማርኛ ልብወለድ ውስጥ ከተለመደው አብራሪነት፣ ገላጭነት፣ (ለምሳሌ በዕውቀቱ ሥዩም እንደሚተቸው ቀኑ ደመናማ ነው ሰማዩ ብልጭ ድርግም ይላል…) እያልን ከምንወርድበት ዘልማዳዊ ጥንወት መንጭቆ ሊያወጣን ይታትራል፡፡ የ”ዣንቶዣራ” ቁጥር አንድ እምርታ ሁነትን ከማብራራት እና ከመተረክ ይልቅ በገጸ ባሕርያት አማካኝነት የሰላ ትችትን መሰንዘር፣ ጥልቅ ፍልስፍናን መወንጨፍ፣ የሕዝቡን ብሶት ማስተጋባት ወዘተ. ነው፡፡ በህዳሴ እንቅስቀሴአችን ውስጥ ያላየነውን እናይ ዘንድ (ግልብ ስልጣኔአችንን እየገለበ) የሚሞግተው ኪራኮስ በተባለ ገጸ ባሕርይ አማካኝነት ነው፡፡
እርጅና ያልሆነ ሰንፍና ካልተጠናወተኝ በስተቀር አስታውሳለሁ! ከአንድ ድፍን ዓመት በፊት መጽሐፍ እያሳተሙ ከደራሲ ወገን የሚሆኑ ሰዎች እንደመብዛታቸው ፖለቲካችንን እና የአስተዳዳሪዎቻችንን የአስተዳደር ዘይቤ የሚደፍር ትጉህ ብዕረኛ እምብዛም እንደሌለ ጽፌ ነበር፡፡ በዚህኛው ጋዜጣ አልነበረም፡፡ ያኔ በዕውቀቱ ሥዩምን ስለፖለቲካዊ ሽሙጡ፣ ይስማዕከ ወርቁን ስለ የሀገር ፍቅር ቀስቃሽ ጽሑፎቹ መጥቀሴን ግን ኮራሁበት፡፡
ዴርቶጋዳን ለአንባቢዎቹ ባቀረበ ጊዜ የንባብን አብዮት በኢትዮጵያ ላይ የለኮሰው ይስማዕከ ወርቁ ለአማርኛ ሥነ ጽሑፍ መዳበር፣ መታተም፣ መነበብ የራሱ የሆነ አዎንታዊ ተጽዕኖ አሳርፏል፡፡ “ዴርቶጋዳ”ን ነግደው የከበሩ መጽሐፍ ሻጮችንም ሳንዘነጋ!
በተከታታይ ያሳተማቸውን መጽሐፎቹን ብዙዎቹ በጉጉት ሲሻሟቸው አስተውለናል፡፡ በቅርቡ ያወጣው አምስተኛ ልብወለዱ ሲሆን ግጥሞቹን ስንጨምር ሰባተኛ መጽሐፉ መሆኑ ነው፡፡ የአሁኑ መጽሐፉ “ዣንቶዣራ” ይስማዕከ ሁለገብ በሆነ መልኩ እምርታ ያሳየበት መሆኑን አምናለሁ፡፡ በዘመኔም ይህን መጽሐፍ በማንበቤ ራሴን እድለኛ አድርጌ እቆጥረዋለሁ|፡፡ ለመሆኑ ይህን ለምን እላለሁ?
ከታክሲ ግፊያ፣ ከኑሮ ጥድፊያ፣ ከሽሮ ጥልፊያ፣ ከጤና  መጠበቂያ ጋር እልህ አስጨራሽ  ግብግብ እየገጠምን በምንቆጥበው ሳንቲም የምንገዛቸው ብዙ መጻሕፍት ማጠንጠኛቸው በቀል፣ ውርስ፣ ተረት  ከዚህ ሲያልፍ ወሬ፣ ወሲብ፣ ቅንዝረኝነት፣ ብልግና እና መሰል አርቲቡርቲ እየሆነ ተረብሸናል፡፡ የመጽሐፉን ገበያ የሚጋፉት ‹‹ፀሐፊዎች›› ትርኪ ምርኪ ትርጉሞችን ሲያስነብቡን አሜን ብለን የተቀበልናቸው እንመስላለን፡፡ በዚህ የሰቆቃ ጭስ እተጨናበስን ስንማትር “ዣንቶዣራ” ከሰማይ እንደተምዘገዘገ መብረቅ ብልጭ ሲል ውስጥህ ከምን ብለን ጓጓንለት፡፡
የሚያስተምሩን ሲያስተምሩን፣ ልምድ የሚያካፍሉን ሲያወጉን፣ ወገኞች ወግ ሲጠርቁልን፡- ሀዲስ ዓለማየሁ በዘመናቸው የነበረውን የአጼ ሥርዓት መጃጃት በ”ፍቅር እስከመቃብር” አጋለጡ፡፡ ወይም ጥቆማቸውን አደረሱ፡፡ በዓሉ ግርማ የዘመኑን እንቅልፋም ምሁራን በ”አድማስ ባሻገር” ንቁ! ብሎ የደርግን ቦርጫም ባለስልጣናት በኦሮማይ አጋልጦ ተሰዋ፡፡
ፖለቲካንና አስተዳደርን የሚነኩ፣ የሀገር ቁስልን የሚያኩ ምሳሌ ሆነው ብዙ ጊዜ የሚጠቀሱልንን መጥቀሴ ነው፡፡ እኔም እላለሁ፡፡ “ዣንቶዣራ” በሕይወት ላለን፣ ሩጠን ላልጠገብን የጽሑፍ ቤተሰቦች ዐይን ገላጭ ነው፡፡ የዘመናችንን የሀሳብ ስስት፣ አድርባይነትና ሆዳምነት፣ የፍርሃት ብዕረኝነት፣ ደኅና ይሰንብት፣ ሀገር ሕዝብ ሞራል ይቅደም አለን፡፡
በ304 ገጾች የተቀነበበው “ዣንቶዣራ” ለአያያዝና ለዕይታ በሚያመች የመጽሐፍ ቅርጽ ተደጉሷል፡፡ በአርባአምስት ብር ዋጋ ነው ለአንባቢው የቀረበው፡፡ የመነሻው ገጽ እንዲህ ይላል፡-
‹‹ግልቡን ስልጣኔ መግልብ››
ግልቡን ስልጣኔ የሚገልብልን ደራሲ እንፈልግ ነበር፡፡ በእርግጥ ግልቡን ስልጣኔ ገልበን እናሳያለን ያሉ ጋዜጠኞች መልካም እጣ እንዳልገጠማቸው ሳናስብ አንቀርም፡፡ መሰልጠናችን ከነአሻሚነቱ ቢያስማም እንኳ ስልጣኔአችን ግልብ እንዳልሆነ ልንሟገት አቅም አይኖረንም፡፡ ይህን ግልብ ስልጣኔ ይስማዕከ በ”ዣንቶዣራ” ገጽ 80 ጀምሮ እንዲህ ይገልጠዋል፡-
‹የኢትዮጵያን ዳግም ልደት ለመጠንሰስ፣ እውነተኛውን ዳግም ልደት ለመጽነስ ከየት መጀመር አለበት?›› ሲል አሰበ፡
‹‹ከአብርኾት መሆን አለበት! Enlightenment የጥንቱን ስልጣኔ አሁን ካለው ነባራዊ የዓለም እርምጃ ጋር ማዛመድ አለብን፡፡ መጀመርያ የተበላሸውን ከመወርወር ጠግኖ ወደ መጠቀም፣ ያለፈውን ከማዳፈን አራግፎ መልካም መልካሙን ወደመጠቀም መመለስ አለብን፡፡ መጀመርያ ጥበባችን ማበብ አለበት፡፡ ከአብርኾት Enlightenment ያልተነሣ ሕዳሴ (renaissance) ምንጭ እንደሌለው ወንዝ ነው፡፡ ጎርፍ የፈጠረው የክረምት ወንዝ፡፡ ጎርፉ ሲቆም ወንዙም መቆሙ አይቀርም፡፡
‹‹ሥነ ልቦናችን ራሱ የእኛ አይደለም፡፡ ሁለነገራችን የለማኝ አዝመራ ሆኗል፡፡ ታዲያ ለዚህ ምሱ ምንድን ነው?››
‹‹… ኢትዮጵያ ውስጥ ሕዳሴ ከሚለው የኢህአዴግ እንቅስቃሴ ጋር አነጻፅረው፡፡ ‹ግማሽ ተሠርታ ግማሽ ተላጭታ› የሚለውን ብሂል አስታውሶት ፈገግ አለ፡፡ ሁለንተናዊ ያልሆነ ሕዳሴ እንደ ተልባ ስፍር በዚህ ሲቆልሉት በዚያ የሚናድ ነው፡፡ (82)
በእርግጥ የቀዳሚ እና የተከታይ ደረጃ ለመስጠት ያዳግተኛል፡፡ ይስማዕከ ግን በአማርኛ ልብወለድ ውስጥ ከተለመደው አብራሪነት፣ ገላጭነት፣ (ለምሳሌ በዕውቀቱ ሥዩም እንደሚተቸው ቀኑ ደመናማ ነው ሰማዩ ብልጭ ድርግም ይላል…) እያልን ከምንወርድበት ዘልማዳዊ ጥንወት መንጭቆ ሊያወጣን ይታትራል፡፡ የ”ዣንቶዣራ” ቁጥር አንድ እምርታ ሁነትን ከማብራራት እና ከመተረክ ይልቅ በገጸ ባሕርያት አማካኝነት የሰላ ትችትን መሰንዘር፣ ጥልቅ ፍልስፍናን መወንጨፍ፣ የሕዝቡን ብሶት ማስተጋባት ወዘተ. ነው፡፡ በህዳሴ እንቅስቀሴአችን ውስጥ ያላየነውን እናይ ዘንድ (ግልብ ስልጣኔአችንን እየገለበ) የሚሞግተው ኪራኮስ በተባለ ገጸ ባሕርይ አማካኝነት ነው፡፡
በ”ዴርቶጋዳ” ተነስቶ በ”ራማቶሐራ” ሸለቆ አቋርጦ ወደ “ዣንቶዣራ” የሚምዘገዘገው የይስማዕከ ምናብ፣ መሠረታዊ ዓላማ የሰለጠነ ትውልድ ማምጣት፤ ስልጣኔን ከውጭ ሳይሆን ከሀገር ውስጥ የማብቀል ከብሔር፣ ከሃይማኖት፣ ከዘር መለያየት እና መቋጠር፤ ፍጹማዊ ንጽህናን ወርሶ ‹‹ሀገር›› ለተባለችው ‹‹ህዝብ›› ሆኖ ስለመገኘት ለመስበክ ነው፡፡
‹‹ከሆድ ያለፈ ዓላማ፤ ከዳቦ ያለፈ ሕልም ያለን ሰዎች ነን›› የሚለውን ቅቡል ንግግር ሚራዥ በገጽ 252 ላይ ይናገራል፡፡ ይህ የሆነበት ምክንያት ምንድን ነው? በእኔና በእናንተ ልብ ውስጥ ብዙ መከፋት አለ፡፡ ከቀበሌ እስከ ፌደራል የተቀመጡ የሥራ ኃላፊዎች፣ የፖለቲካ ሰዎች፣ ሠራተኞች መካከል ሀገር ከምትጥልባቸው አደራ ባለፈ የግል ጥቅም ቀድሞ ትዝ የሚላቸው፣ ይህን ሒሳብ እየሠሩ የሚንቀሳቀሱም ጥቂት አይደሉም፡፡
እነዚህ ነቀዞች ሀገር ለእነሱ ምንም ናት፡፡ አደራ ለእነሱ ተራ  ነገር ነው፡፡ ጥቁር ጋዎን ለብሰው የሚገቡት ቃልኪዳን በጥቂት ብሮች የሚደረመስ የሸንበቆ ድልድይ ነው፡፡ በምርጫ ካርድ ያገኙት ያደራ ስልጣን በሰው ላይ ምራቅ ጥቂ ብሎ እስከመትፋት የሚያደርስ ትእቢትን ያዋድዳቸዋል፡፡ እነዚህን ነቀዞች መደራደር ያላማረው ሚራዥ፤ ከሆድ ያለፈ ዓላማ ከዳቦ የበለጠ ህልም ያለው ትውልድ መምጣት እንዳለበት ተናገረ፡፡ ታዲያ ይህ ማንን አያሳምንም? ከአንገት ሳይሆን ከአንጀት ሀገሩን ለሚወድ ስለዚህ ቃሉ ብቻ መጽሐፉ የእውነት መጽሐፍ ነው፡፡
ከፍ ብዬ እንደጠቀስኩት ደራሲዎቻችን በፍርሃት ሸምቀቆ በተቀረቀቡበት በአሁኑ ወቅት፣ የጋዜጦች መዘጋት ተራ ጨዋታ በሆነበት በዚህ ሰሞን፣ እጅን በአፍ የሚያስጭን ድፍረት በ”ዣንቶዣራ” እናያለን፡፡
‹‹ ጤፍ ተወደደ ብሎ ማማረር ሽብርተኛ የሚያስብልበት ጊዜ ላይ ነው ያለነው፡፡ ለተገቢው ስራ ክፍያ ይከፈለኝ ብሎ መጠየቅ ሽብርተኛ የሚያስብልበት ጊዜ ላይ ነው ያለነው፡፡ ስርዓቱ ላለፉት ሃያ ዓመታት በላይ ያልመለሳቸውን ጥያቄዎች ማንሳት ሽብርተኛ የሚያስብልበት ጊዜ ላይ ነው ያለነው፡፡ ቋንቋን መሠረት ያደረገው ፌደራላዊ ሥርዓት ጸረ አንድነት እና ጸረ እድገት ነው ብሎ መከራከር ሽብርተኛ የሚያስብልበት ጊዜ ላይ ነው ያለነው፡፡ የተናገርኩትን ሁሉ መናገርም በሽብርተኝነት እንደሚያስጠይቅ አለመጠርጠር አይቻልም፡፡›› ይህ የተሟጋቹ የዣንጊዳ ንግግር ነው፡፡ (ገፅ 110)
‹‹ልብወለድ›› ከፕሮፌሰር አፈወርቅ ገ/ኢየሱስ የወረስነው ቃል ይሁን እንጂ ልብ የወለደውን ብቻ ትረካ የሚገልጽ እንዳልሆነ የሙያው ሰዎች ይናገራሉ፡፡ “የገሀዱ ዓለም ነጸብራቅ ነው ነው” የሚለውን ንድፈ ሐሳብ ሊያብራራ ቢያሻው፣ ከዚህ በላይ የተቀመጠውን የመፅሃፉን ክፍል ማንበብ እና ካለንበት ነባራዊ ሀቅ ጋር ማነጻጸር በቂ ነው፡፡ እንግዲህ የደራሲው እምርታ ሆኖ እንዳይመዘገብለት ማን ይቃወማል፡፡
ሃይማኖትን ወይ ቋንቋን ወይም ብሔርን ሽፋን በማድረግ ዜጎችን የማለያየት ዓላማ ያነገቡ የገዥው ይሁኑ የተቃዋሚ ፓርቲ ብልጣብልጥ አባላት፣ ጻፍን ያሉትን ክርታሳቸውን ባስነበቡበት የመጻሕፍት መድረክ ላይ ስለሀገር የተዘመረ ድርሳን በዚህኛው ዘመን የስነ ጽሑፍ ታሪክ ትልቁን ስፍራ ቢይዝ አይገርምም ፡፡ አንባቢዎች ተሻምተው ቢገዙት ምክንያቱ ይህ ነው፡፡ መጽሐፍ መሸጥ መተዳደርያቸው ያልሆኑ የሱቅና የጎዳና ነጋዴዎች “ዣንቶዣራን” ቆልለው ሲቸበችቡ መታዘባችንም በልባችን የሚፈላውን የአንድነት፣ የኅብርና የፍቅር ስሜት የሚጠቁም ነው፡፡
ዙርያ ገባውን ያሁኑን ዘመን ህዝብ እና መንግስት ብሎም ሀገሪቱን ለታሪኩ ማጠንጠኛ ያደረገው መፅሃፉ፤ በየገጸባህርያቱ የሚንቀለቀል ወኔ አንድነትን እንደሚያሳየን ሁሉ ቀንጠፋውን እና አክሎግን በመሰሉ ገጸባህርያት ደግሞ ገዥውን ፓርቲ ጥግ አድርገው ፓርቲውንና ህዝቡን የሚመጠምጡ መዥገሮችን ያጋልጣል፡፡
በገዥው ፓርቲ ብዙ እምነት ተጥሎበት ከፍተኛ የደህንነት ሃላፊነት የተሰጠው ቀንጠፋው ለገንዘብ ሲል የሀገሩን አደራ ይዘነጋል፡፡ መዘንጋቱ ሳይሆን አደራውን ሊበላበት ያለው መንገድ ይበልጡን ይሰቀጥጣል፡፡ የሀገሩ አንጡራ ሀብት የሆነውን ኢንጅነር ከነነፍሱ ለሲአይኤ ሊሸጥ ሲዳረደር ማየት እንባን የሚያስመጣ አሊያም በቁጣ የሚያገረጣ ክስተት ነው፡፡
ታዲያ ቀንጠፋውንና አክሎግን ለመሳሰሉ ሀገርና ህዝብ ለሚቸረችሩ ብኩኖች ተስፈኞቹ፣ አዲሶቹ፣ ሀገርን በቅንነት ሊረከቡ ያሉቱ ‹‹ሴቶቿን ለአረብ ምሁሮቿን ለምዕራብ ከእንግዲህ አትሸጡም›› ብለው ሲቋቋሟቸው ማየት፣ በሆነ ከሚለው ምኞት ጋር ቀውቤ መጠጣት ነው፡፡ ሞራልን ስነምግባርን እና ብጽዕናን ለአንባቢ ማቀናጀት የሥነ ጽሑፍ ትልቁ ጥቅም ነው፡፡ ይህን ማድረግ የቻለው ይስማዕከ ዕምርታ ሆኖለታል እላለሁ፡፡
ይስማዕከ በ”ዣንቶዣራ” ብዙ አዲስ ነገሮችን አምጥቷል፡፡ በ”ዴርቶዳጋ” እና በ”ራማቶሐራ” ከታየው ይበልጥ በበረሃ እንዳለ ምንጭ ኮለል የሚል የቋንቋ አጠቃቀምን እናይበታለን፡፡ የመጽሐፉ ሕትመት በራሱ ለማንበብ ምቹ መሆኑን መመስከር የቀደመውን ማጣጣል ይመስላል ብዬ አልገምትም፡፡ ሰላም ለአንባቢያን!
*********************************************************************************
ምንጭ:--አዲስ አድማስ ጋዜጣ
            Saturday, 22 September 2012

 

ማሞ ካቻ (አቶ ማሞ ይንበርብሩ)

  አቶ ማሞ ይንበርብሩ (ማሞ ካቻ) እስቲ እናስታውሳቸው፣ ተቀብሮ እንዳይቀር አኩሪ ታሪካቸው  (ደረጀ መላኩ)   አቶቢሲ ማሞ ካቻ የት ትሄዳለህ? ገብረ ጉራቻ… ታዳጊው ማሞ ይንበርበሩ ገና በጨቅላ እድሜው አባቱ አቶ...