ቅዳሜ, ዲሴምበር 22, 2012

ሞክሼ የአማርኛ ፊደላት እና የባለሙያዎች ማብራሪያ

ክፍል አንድ

የፊደል ዘር ይጠበቅ ባህሉም ይከበር
በፊታውራሪ አበበ ሥዩም ደስታ
በፊደሎቻችን ላይ ሦስት ሀ - ሐ - ኀ፣ ሁለት አ - ዐ -፣ ሁለት ሠ - ሰ ሁለት፣ ጸ - ፀ አሉ፡፡ እነዚህ ፊደሎች የራሳቸው የሆነ የስም አጠራርም አላቸው፤ ሀሌታው ሀ፣ ሐመሩ ሐ፣ ብዙኃን ኀ፣ ንጉሡ ሠ፣ እሳቱ ሰ፣ ጸሎት ጸ፣ ፀሐዩ ፀ ይባላሉ፡፡ በጽሑፍ የሚገቡበትን ተገቢ (ተስማሚ) ቦታም አላቸው፡፡ ለምሳሌ በሁለት ፊደሎች መጠቀም ይቻላል፡፡ ሀገር አገር ይህ ትክክለኛ አጻጻፍ ሲሆን፤ ነገር ግን ከዚህ ውጪ ሐገር፣ ኀገር ብሎ መጻፍ ግን ስሕተት ይሆናል፤ የሚከተሉትን ደግሞ እንመልከት፤

ሕገ መንግሥት፣ ሕገ ወጥ፣ ሕዝብ፣ ሕብረት፣ ዓቃቤ ሕግ፣ ወዘተ. የመሳሰሉት አጻጻፋቸው ትክክል ነው፡፡ ከዚህ ልማዳዊ አሠራር ውጪ ህገ መንግሥት፤ ህገወጥ፤ ህዝብ፤ ህብረት፤ አቃቤ ህግ ስሕተታዊ አጻጻፍ ይሆናል፤ ሌላ ማስረጃ ቢፈለግ፤ ኃይለሥላሴ የሚለው ስም ሦስት የተለያዩ ፊደሎች ይዟል፡፡ የመጀመርያው ፊደል ብዙኀን - ኃ - ሲሆን፣ ከንጉሡ -ሥ- ሳድስ፣ ከእሳቱ -ስ- ሃምስን በመጻፍ እንዲካተት ተደርጓል፡፡ ሀይለ ስላሴ ብሎ ቢጻፍ ግን የፊደሎቻችን የአጻጻፍ ሥርዓት ማፋለስ ይሆናል፤ በአቦ ሰጡኝ ፊደሎቻችን አለቦታቸው መግባትም፣ መጻፍም የለባቸውም፡፡

በዓፄ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት በማስታወቂያ ሚኒስቴር ረዳት ሚኒስትር የነበሩት የተከበሩ ብላታ ወልደ ጊዮርጊስ ወልደ ዮሐንስ የቅድሚያ ዓይነተኛ ሥራቸው የፊደሎች ዘሮች አለቦታቸው እንዳይጻፉ መጠበቅ ነበር፤ በዚያን ወቅት ተማሪ ሁኜ አልፎ አልፎ በጋዜጣ እንዲወጣልኝ አንድ አንድ ሐሳብ በማመንጨት እጽፍ ስለነበር ብዙ ጊዜ አርመውኛል፡፡

ከእሳቸው በተማርኩት ትምህርትና ባገኘሁት ልምድ አእምሮዬን አሻሽያለሁ፡፡ በቀድሞው የንጉሠ ነገሥቱ ዘመነ ሥርዓት የክፍል ሹም የመጀመርያ ሹመት ሆኖ ወደ ላይ እንደሚከተለው ይዘልቃል፡፡ ዲሬክተር ዋና ዲሬክተር፤ ረዳት ሚኒስትር ምክትል ሚኒስትር፣ ሚኒስትር ዲ-ኤታ፤ ሚኒስትር፡፡ ከምክትል ሚኒስትር ወደ ላይ ያሉት እስከ ሚኒስትር ማዕረግ የደረሱት ክቡር ይባላሉ፡፡ ከዚህ በታች ያሉትን ግን ክቡር አይባሉም፡፡ በተመሳሳይ ያሉትን ማለት ኮሚሽነሮች፤ ሌ/ጀኔራሎች፣ አምባሳደሮች ክቡር ይባላሉ፡፡ ሚኒስትሮች የነበሩ በዳሬክተርና በሥራ አስኪያጅነት ሥራ ቢመደቡ እንኳን የቀድሞውን የሚኒስትር ማዕረጋቸውና ክብራቸው አይቀነስባቸውም፡፡ ክቡር መባል አለባቸው፡፡ ሥርዓት ነውና፡፡ ይህንኑ መለመድ ይገባዋል፤ በወታደሩ ሹመት አሰጣጥ ግን ያለው ሥርዓት የተጠበቀ ስለሆነ መልካም ነው እላለሁ፡፡ ከዚሁ ሌላ የምለው አለኝ፡፡ ባሁኑ በኢሕአዴግ መንግሥት ዘመን አምባሳደር ነዋሪ የማዕረግ መጠሪያ ስም ሆኖአል፡፡ አንድ አምባሳደር የዲፕሎማሲውን ሥራ አቁሞ ሲዛወር ልክ በሥራው እንዳለ ተቆጥሮ “አምባሳደር” እየተባለ መጠራት የለበትም፡፡

ለምሳሌ በዓፄ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት አምባሳደርነት ተሹመው የነበሩት ክቡር አቶ ጋሻው ዘለቀ፣ ክቡር አቶ ዘነበ ኃይለ፣ ክቡር ልጅ መንበረ ያየህ ይራድ፤ ክቡር ፊታውራሪ መሐመድ ሲራጅ ብዙ ዘመን በአምባሳደርነት ሲሠሩ ቆይተው ተልእኮዋቸውን ፈጽመው ወደ አገራቸው ሲመለሱ አምባሳደር የሚል ቀርቶ በቀድሞ ስማቸው አቶ ተብለው ነበር የሚጠሩት፤ ይህንኑ ጠይቆ ለማረጋገጥ ይቻላል፡፡ ፊታውራሪ የነበሩትም፤ ፊታውራሪ ተብለው ይጠራሉ፡፡ ዘላቂ ሆኖ ከሰው ጋር ቅጽል የማዕረግ ስም ሆኖ የሚያገለግል ነው፡፡ በራሴ ምሳሌ ልውሰድ፤ ከግርማዊ ጃንሆይ በአዋጅ የተሰጠኝ የማዕረግ ስም ፊታውራሪ ነው፤ በዚህ ምድራዊው ዓለም እስካለሁ ድረስ የምጠራበት ሲሆን፣ ከሞትኩም በኋላ እጠራበታለሁ፡፡ እንዲሁም በንጉሠ ነገሥቱ መልካም ፈቃድ የሚሰጠው የሥልጣንና ማዕረግ ተዋረድ ባላምባራስ፣ ግራዝማች፣ ቀኛዝማች ፊታውራሪ፣ ደጀዝማች፣ ቢትወደድ፣ ራስ ቢትወደድ፣ ልዑል ራስ፣ አልጋ ወራሽ፣ ንጉሥ ንጉሠ ነገሥት ሲሆን፣ በሌላ በኩል ደግሞ ብላታ፣ ብላቴን ጌታ፣ ፀሐፊ ትዕዛዝ፣ ሊቀ መኳስ በሕይወት ሳሉ ይጠሩበታል፡፡ ከሞቱም በኋላ ስማቸውና ታሪካቸው በተነሣ ቁጥር ከመቃብር በላይ ሆኖ በማዕረጉ ስም ይጠሩበታል፡፡


አምባሳደር ግን የማዕረግ ስም መጠሪያ ስላልሆነ የዲፕሎማሲ ሥራቸውን ሲያቋርጡ አምባሳደር ተብለው ሊጠሩበት አይገባም፡፡ በሌላ መንግሥት የማይሠራበት ሲሆን የኢትዮጵያ መንግሥት ለብቻው በዚህ ስም አጠራር ሕጋዊ ማድረጉ ተገቢ አይመስለኝም፡፡ እንደ ማዕረግ በዘላቂነት ይጠሩበት ከተባለ እኔ ከማሳሰብ በቀር እምጎዳበት የለም፡፡ ከዚህ ጋር የማያይዘው ሌላም አለ፤ ከላይ በዝርዝር እንደገለጽኩት ባሁኑ ሰዓት ዲሬክተር ጄኔራል እየተባሉ አንዳንድ ሹማምንት ይጠሩበታል፡፡ በእኔ አስተያየት ዲሬክተር ጄኔራል ከማለት ይልቅ ዋና ዲሬክተር ቢባሉ ወይም ለስም አጠራሩ የሚቀል ስለሆነ ረዳት ሚኒስትር እየተባሉ ቢጠሩ መልካም ነው፡፡ በዚህ ቢታረም ያማረ ይሆናል፡፡

በማጠቃለያ የማቀርበው ሐሳብ በየዕለቱ እና በየሳምንቱ በሚታተሙ ጋዜጦች መጽሔቶች፣ መጻሕፍት የፊደሎቻችን ዘሮችና ልማዳዊ የአጻጻፍ ሥርዓቶች ይጠብቁ (ይከበሩ) በማለት ሐሳቤን እቋጫለሁ፡፡ እንዲሁም የኮምፒውተር ፀሐፊዎች ይህንኑ የአጻጻፍ ስልት (ፈለግ) ተከትለው ይጠቀሙበት በማለት መልእክቴን አስተላልፋለሁ፡፡ በተጨማሪም ደራስያን፣ አስተማሪዎች፣ ማተሚያ ቤቶች፣ ከያኒያን ይህንኑ እንዲተገብሩ ማድረግ የግል ኃላፊነት ስላለባቸው ትኩረት ይስጡበት እላለሁ፡፡

ሌላው መታረም የሚገባው፣ “ስፖርት” እየተባለ የሚጻፈው ነው፡፡ ምክንያቱም የአውሮፓ ፊደል ኤስ (S) የእ ፊደል ድምፅ ስላለው፣ Sport ቢጻፍ ትክክል ነው፤ የእኛው ፊደል (ስ) ግን ድምፁ የተዋጠ ስለሆነ እ ፊደል ተጨምሮበት “እስፖርት” ቢባል የተሻለ ነው፤ እንዲሁም ለርምጃ እርምጃ ቢባል፣ በኔ በኩል ጥሩ ስለሆነ ታስቦበት ቢታረም መልካም ይመስለኛል፡፡
***********************
ምንጭ:-- ሪፖርተር ጋዜጣ

 

እሑድ, ዲሴምበር 09, 2012

ተፅዕኖ ፈጣሪው ቀኝ ጌታ ዮፍታሄ ንጉሴ

“ሰውን ሰው ቢወደው አይሆንም እንደራስ ታመህ ሳልጠይቅህ መቅረቴን አትውቀስ ባውቀው ነው የመጣሁ እንደማልመለስ ይማርህ መሀሪው እስመጣ ድረስ”
/ዮፍታሄ ንጉሴ በቅድመ ፋሺስትና 
በድህረ ወረራ በርካታ ስራዎቻቸውን 
አበርክተው ላለፉት ብላቴን ጌታ ህሩይ ወ/ስላሴ 
ህልፈት የጻፉት የሀዘን እንጉርጉሮ ነበር፡፡/

“ጎነዛዚቴ ሆይ ወይ ቆነጃጅቴ
ምንኛ ነደደ ተቃጠለ አንዠቴ
እንመለሳለን ባዲሱ ጉልበቴ
እናንተም ተምርኮ እኔም ተስደቴ”
***************************************************************************
የአማርኛን ስነ ጽሁፍ ካሳደጉት ታላላቅ ኢትዮጵያዊያን መካከል ባለቅኔው ዮፍታሄ ንጉሴ ይጠቀሳሉ፡፡ ዮፍታሄ ንጉሴ የተወለዱት በጎጃም ክፍለ ሀገር በደብረ ኤልያስ በ1885 ዓ.ም ሲሆን በደብረ ኤልያስ ደብር የጥንቱን የኢትዮጵያ ቤተክርስትያን ትምህርት በሚገባ ተምረዋል፡፡ ዮፍታሄ በልጅነታቸው የዜማ ትምህርት ያስተማሯቸው መሪጌታ አደላ ንጉሴ ሲሆኑ የቅኔን ትምህርት ያስተማሯቸው የኔታ ገብረስላሴ ነበሩ፡፡ የኔታ ገብረስላሴ በደብረ ኤልያስ ደብር ታዋቂ የቅኔ መምህር ሲሆኑ ሁለተኛው ኢትዮጵያዊ ፓትርያርክ አቡነ ቴዎፍሎስን ቅኔ እንዳስተማሯቸው በታሪክ ይታወቃል፡፡ ደብረ ኤልያስ ደብር የ”ፍቅር እስከ መቃብር” ደራሲ ሃዲስ አለማየው የተማሩበት ደብር ነው፡፡
አቶ ሙሉጌታ ስዩም በ1964 ዓ.ም በቀዳማዊ ኃይለ ስላሴ ዩኒቨርስቲ በመመረቂያ ጽሁፉ ላይ እንደገለፀው፤ በደብረ ኤልያስ ደብር የነበሩ መምህራን “ማህበረ ኤልያስ” በሚል ስም እግረ ኤልያስ ብለው ደቀመዛሙርት ተማሪዎቻቸውን ይጠራሉ፡፡ በዮፍታሄ የዜማና የቅኔ ችሎታ መምህራኖቹ ከመደነቃቸው የተነሳ ለአምስት ተከታታይ ዓመታት እግረ ኤልያስ የሚለውን ምርጥ ስም ሰጥተውታል፡፡ ለዮፍታሔ ገና በልጅነቱ የአባቶችን ማእረግ ቀኝ ጌታ ሾመውታል፡፡
ቀኝ ጌታ ዮፍታሄ በ1911 ዓ.ም አዲስ አበባ እንደመጡ፣ ወዲያውኑ በአቦ ደብር በአጋፋሪነት፤ በመቀጠልም በደብረ አለቅነት ተሹመዋል፡፡ ከቤተክርስቲያን አገልጋይነት ቀጥለው በሊጋባ ወዳጆ ጽ/ቤት የጽሕፈት ስራ እየሰሩ ለተወሰነ አመት ቆዩ፡፡
በኋላም ዶክተር አምሳሉ አክሊሉ ባልታተመ ጥናታቸው እንደገለፁት፤ ቀኝ ጌታ ዮፍታሄ በዳግማዊ ሚኒሊክ ትምህርት ቤት በአስተማሪነት ተቀጥረው ልዩ ልዩ መዝሙሮችን እየደረሱ ማስተማር ጀመሩ፡፡ በቀድሞ ጊዜ ዳግማዊ ምኒሊክ ትምህርት ቤት ያስተምሩ የነበሩ መምህራን በየጊዜው በትምህርት ቤቱ ቅጥር ጊቢ ልዩ ልዩ ትያትሮች እየደረሱ ለተማሪዎች ያሳዩ ነበር፡፡ ይህም ሁኔታ የመዝሙር መምህሩን ዮፍታሄን ከቲያትር ጋር አስተዋወቃቸው፡፡ ዮፍታሄም አዳዲስ ትያትሮችን በተለየ አቅጣጫ መድረስ ጀመሩ፡፡
ቀኝ ጌታ ዮፍታሄ ንጉሴ ከደረሷቸው በርከት ያሉ ትያትሮች መካከል “አፋጀሽኝ”፣ “የሆድ አምላኩ ቅጣት”፣ “የደንቆሮዎች ትያትር”፣ “እርበተ ፀሐይ” እና “ጎበዝ አየን” ይጠቀሳሉ፡፡
የትያትር መምህሩና ተዋናዩ ተስፋዬ ገሰሰ በጥናታዊ ጽሁፋቸው እንደገለፁት፤ ዮፍታሄ ንጉሴ በድርሰት ችሎታቸው ብዙ የተመሰገኑ እና ከግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ስላሴ ብዙ ሽልማቶችን ያገኙ ነበር፡፡
ከጦርነቱ በፊት በመናገሻ ቅጥር ጊቢ ውስጥ የጊዮርጊስ ትምህርት ቤት ሲባል ከነበረው ቀበና ከሚገኘው ሊሴ ኃይለ ስላሴ ትምህርት ቤት፣ ከተፈሪ መኮንንና ከዳግማዊ ምኒሊክ ትምህርት ቤቶች ተማሪዎች ተመርጠው ልዩ ልዩ ትያትሮችን እያዘጋጁ ያበረክቱ ነበር፡፡ አቶ ሙሉጌታ ስዩም በጥናቱ እንደጠቆመው፣ አንድ ጊዜ ጃንሆይ ዮፍታሄን ትያትር በመመልከት ላይ እያሉ በጣም ከመደሰታቸው የተነሳ ከልዑል አልጋ ወራሽ አንገት ወርቅ አውልቀው፤ ለዮፍታሄ አድርገውላቸዋል፡፡
ቀኝ ጌታ ዮፍታሄ በርካታ የመድረክ ድርሰቶች አዘጋጅተው አሳይተዋል፡፡ ነገር ግን ድርሰቶቹ ባለመታተማቸው የተገኙት በጣም ጥቂቶች ናቸው፡፡ “ጎበዝ አየን” የሚባለው ድርሰታቸው የህትመት ብርሀን አይቷል፡፡
ለመድረክ ከቀረቡት ውስጥ የተመልካችን አድናቆት ያተረፈው “አፋጀሽኝ” የተባለው ድርሰታቸው ነው፡፡ ይሄን ድርሰት ዮፍታሄ የጀመሩት ከጣሊያን ወረራ በፊት ሲሆን ድርሰቱን የፈፀሙት ከወረራው በኋላ ነው፡፡
“አፋጀሽኝ” ድርሰት ምሳሌያዊ ሲሆን በወቅቱ የነበረውን የአለም ፖለቲካዊ አዝማሚያ የሚጠቁም ከመሆኑም በላይ በድርሰቱ ውስጥ የተመሰለችው እናት ሀገር ኢትዮጵያ በሚከጅሏት ዘንድ የነበራትን የፖለቲካ ሁኔታ የሚያሳይ ነው፡፡ “አፋጀሽኝ” ዋና ጭብጡ በጣሊያንና በኢትዮጵያ የነበረውን ጦርነት የሚያመለክት ነው፡፡ ይሄም የጊዜው አንገብጋቢ ፖለቲካዊ መልእክት ነበር፡፡ ድርሰቱ የዮፍታሄን ኪናዊ ችሎታ በቅጡ የሚያንፀባርቅ እንደሆነ ይነገርለታል፡፡
በኢትዮጵያ የድራማ ታሪክ የመድረክ ተውኔቶችን ካቀጣጠሉት ፈር ቀዳጆች መካከል በቅድሚያ የሚጠቀሱት በጅሮንድ ተክለሀዋርያትና እና ቀኝ ጌታ ዮፍታሄ ንጉሴ ናቸው፡፡
ዮፍታሄ የድራማ ሰው የነበሩትን ማቲዎስ በቀለን አስተምረዋል፡፡ “ሙናዬ ሙናዬ” የተሰኘው ዘፈን የዮፍታሄ ግጥም ሲሆን ዜማው በአገር ፍቅር ማህበር ይገኛል፡፡
ቀኝ ጌታ ዮፍታሄ ከተውኔት ድርሰታቸው በተጨማሪ መዝሙሮችንና ግጥሞችን ደርሰዋል፡፡ የኢትዮጵያ አንድነትና የህብረት መዝሙር የሚገልጽልንን የኢትዮጵያ ህዝብ መዝሙር (ተፈሪ ማርሽ)፣ ወላድ ኢትዮጵያ፣ አጥንቱን ልልቀመው፣ ድንግል አገሬ ሆይ የሚባሉ መዝሙሮችን ደርሰዋል፡፡ አጥንቱን ልልቀመው የሚለው ግጥም አርበኞቹን የዶጋሊውን አሉላ አባ ነጋ እና ራስ ጎበናን በማነፃፀር የገጠሙት ግጥም ሲሆን ድንግል ሀገሬ ሆይ የተሰኘውን ድርሰት የፃፉት በስደት ኢሊባቡር ሆነው በ1929 ዓ.ም ነበር፡፡ ይህ መዝሙር ከመጀመሪያ ረድፍ ከሚጠቀሱት ስራዎቻቸው ቀዳሚው ነው፡፡
ድንግል ሀገሩ ሆይ ጥንተ ተደንግሎ
ጥንተ ተደንግሎ ጥንተ ተደንግሎ
ህፃናቱ ታርደው ያንቺም ልብ ቆስሎ
ልጅሽ ተሰደደ አንቺን ተከትሎ
የህፃናቱ ደም አዘክሪ ኩሎ፡፡
አዝማች፤ አስጨነቀኝ ስደትሽ
እመቤቴ ተመለሺ እመቤቴ ተመለሺ
ይሄ ግጥም ዮፍታሄ ንጉሴ ህዝቡ በፋሺስት ወረራ የደረሰበትን ስደት የገለፁበት ስንኝ ነው፡፡ ቅድስት ድንግል ማርያም ከእስራኤል ወደ ግብጽ ያደረገችውን ስደት እና በኤሮድስ ህፃናት መቀላታቸውን ከኢትዮጵያ ስደት ጋር ያነፃፀሩበት ግጥምም ነው፡፡
የቀኝ ጌታ ዮፍታሄ ግጥሞች ትንቢታዊ ሲሆኑ በአንድ ስንኝ የሚጽፉት ግጥም ተሰጦአቸው የላቀ መሆኑን ያሳየናል፡
የሰማይ አሞራ ልጠይቅሽ ወሬ፣
ተቃጥሏል መሰለኝ ሸተተኝ አገሬ፡፡
በጣሊያን ወረራ ወቅት ለፋሺስት ያገለገሉ ባንዳዎችን በማስመልከት የገጠሙት ምፀታዊ ግጥም እንዲህ ይላል፡-
ለጌሾ ወቀጣ ማንም ሰው አልመጣ
ለመጠጡ ጊዜ ከየጐሬው ወጣ፡፡
ቀኝ ጌታ ዮፍታሄ በተለይ የግእዙን ቅኔ መንገድ ለአማርኛ ለማውረስና የግእዙን ኪነታዊ ጠባይ አማርኛ እንዲኖረው ለማድረግ ታላቅ አስተዋጽኦ እንዳደረጉ ከግጥሞቻቸው እንረዳለን፡፡ ዶክተር አምሳሉ አክሊሉ በጥናታቸው እንደፃፉት፤ ይህም በግእዝ ቋንቋ ያላቸውን እውቀትና ብስለት የሚያረጋግጥ ነው፡፡ ከሳቸው በፊት እንዲህ ያለ ሙከራ ያደረገ ሰው መኖሩም ያጠራጥራል፡፡ የተፃፈም ነገር አላጋጠመንም፡፡ ግን ኋላ ላይ ይህን መንገድ ብዙዎቹ ባለቅኔዎች ተከትለው ሰርተውበታል፡፡
ቆሞ የስኳር ጠጅ
ውስተ ደብረ ማሕው ልብነ ሀገሩ ስቃይ ወተድላ፤
ወደይነ በበተራሆሙ አረቄ ወጠላ፤
በውስተ በርሜል ልብነ ምስትግቡአ በቀለ አተላ፤
እሳተ አራዳ ኮኛክ እሷው ተቃጥላ፤
አወያይታ ለባቢሎን ገላ፡፡
ግማሽ አማርኛ ግማሽ ግእዝ አድርገው የሚያዘጋጇቸው ማህሌተ ገንቦ የተባሉት መዝሙሮቻቸው አድማጭ የሚስቡ ነበሩ፡፡ በተጨማሪም በቀኝ ጌታ ዮፍታሄ ንጉሴ ድርሰት ላይ ጐልቶ እንደታየው የዮፍታሄ አፃፃፍ ከቀበሌኛ ወይም ከአገራቸው ከጐጃም አማርኛ የነፃ ነው፡፡ ለማንም አማርኛ ተናጋሪ ሳይቸግር ይገባል፡፡ የግእዝ ብስለታቸው ለዚህ አፃፃፍ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አድርጓል፡፡
ማሽላና ስንዴ በአንድ አብረን ስንቆላ፤
እያረረ ሳቀ የባህር ማሽላ፡፡
ከሰል የሚሆኑ ብዙ እንጨቶች ሳሉ፤
ዝግባ ለምን ይሆን ይቆረጥ የሚሉ፡፡
የቀኝ ጌታ ዮፍታሄ አፃፃፍ ለተከታዮቹ ደራሲያን ምሳሌ ስለነበር አንጋፋነታቸው ታላቅ ዋጋ የሚሰጠው ነው፡፡ ዮፍታሄ በግእዝ ቅኔ የበሰሉ ስለነበሩ አማርኛ የስነ ጽሑፍ ቋንቋ እንዲሆንና እንዲያድግ የላቀ አስተዋፅኦ አበርክተዋል፡፡
የአማርኛ ስነ ጽሑፍን ለማሳደግ በተውኔት፣ በግጥም፣ በዘፈን እና በመዝሙር ባደረጉት ጥረት በኢትዮጵያ ስነ ጽሑፍ ታሪክ ውስጥ ከፍተኛ የክብር ቦታ አላቸው፡፡ ባለ ቅኔው ዮፍታሄ ከጣሊያን ወረራ በኋላ እስከ 1941 ዓ.ም የህግ መወሰኛ ምክር ቤት ምክትል ፕሬዝዳንት ሆነው ሲሰሩ ቆይተው በ1942 ዓ.ም አርፈዋል፡፡ የባለ ቅኔው ዮፍታሄ ስራዎች ግን ተጽእኖ ፈጥረው ከትውልድ ወደ ትውልድ ይሸጋገራሉ፡፡

*********************************************************************************
ምንጭ:--http://www.addisadmassnews.com
            --http://www.ethiosalon.com
            --http://ethioliteraturepaltalk.blogspot.com

ሰኞ, ዲሴምበር 03, 2012

የሸገር ሬዲዮ መዓዛ

 ክፍል --፪
**************

እዚህ አዲስ አበባ ውስጥ የሬዲዮ መቀበያችንን መስመር በኤፍ ኤም በኩል ከአንዱ ጫፍ ወደ ሌላው ጫፍ ብንዘውረው ሰባት ያህል የሬዲዮ ጣቢያዎችን ማግኘት እንችላለን፡፡
ሬዲዮ ጣቢያዎቹ የተለያዩ ቢሆኑም አብዛኞቹ የሚያቀርቡት ተመሳሳይ “ዝግጅት” ነው፡፡
አንዱን ጣቢያ ከሌላው ለመለየት የሚያስችል የራሳቸው የሆነ መለያ ቀለም ስለሌላቸው፤ የአንዱ ሬዲዮ ፕሮግራም በሰባት የሬዲዮ መስመሮች ውስጥ ተከፋፍሎ የሚሰማ እስኪመስል ድረስ ምንም ዓይነት ልዩነት አይታይባቸውም፡፡ የሚያቀርቧቸው ፕሮግራሞች በክሊሼ የታጀሉና ኦና ከመሆናቸው የተነሳ አድማጭን ያንገፈግፋሉ፡፡ መስፍን ሀብተማርያም በአንድ የወጐች መድበሉ ላይ እንዳለው፤ ለአንዳንዶቹ ሬዲዮኖች ሲባል “ምነው ጆሮም እንደ ዓይን ቆብ በኖረው” ያሰኛል፡፡
ለመሆኑ ጥሩ የሬዲዮ ፕሮግራም እንዴት ያለ ነው? ጥሩ የሬዲዮ ፕሮግራም፤ ባለሙያ መጥናና ቀምማ ባሰናዳችው መልካም ወጥ ሊመሰል ይችላል ይባላል፡፡
 
የባለሙያዋን ቅመም ዓይነትና መጠን እንዲሁም የአበሳሰል ዘዴ ባናውቀውም፣ በማድመጥ ግን ጥሩው የቱ እንደሆነ እናውቀዋለን፡፡ ለምሳሌ ለእኔ መልካም የሬዲዮ ፕሮግራም ማለት እንደ ቢቢሲ፣ እንደ ዶቼ ቬሌ፣ እንደ ቪኦኤ ወይም እንደ ሸገር ሬዲዮ ፕሮግራም ያለ ነው፡፡
የሬዲዮ ፕሮግራም ዝግጅት የማያቋርጥ መሰናዶ እንደሚሻ የዘርፉ ባለሙያዎች ይጠቁማሉ፡፡ በተጨማሪም ሙያው ከማንኛውም የጋዜጠኝነት ዘርፍ ያላነሰ ምርምር፣ ሐቀኛ መረጃ እና እንደ ጥበብ ደግሞ የፈጠራ ሥራ ያስፈልገዋል፡፡ በዚህ ላይ ተመስርቶ ቀላል፣ የተመጣጠነ ሆኖም አዝናኝ ወይም አስተማሪ የሆነ ፕሮግራም ከሙዚቃ ጋር ተዋህዶ ለዛ ባልተለየው ዘዴ ሲቀርብ የአድማጩን የዕውቀት አድማስ ያሰፋል ወይም ያዝናናል፡፡ በዚህ ረገድ በሀገራችን የተሻለ ሥራ በማከናወን የአድማጩን ስሜት ለማርካት የቻለው ሸገር 102.1 ኤፍ ኤም ሬዲዮ ነው፡፡
 
ይህ ሬዲዮ በተመሠረተ በአጭር ጊዜ ውስጥ ያሳየው ብቃት በአገራችን የሬዲዮ ሥርጭት ታሪክ ውስጥ ጉልህ ሥፍራን እንዲያገኝ አድርጐታል፡፡ የጣቢያው ብቃትና ችሎታም ምንጭ የአዘጋጆቹ የዓመታት የሬዲዮና የጥበብ ሥራ ቅምር ውጤት ነው፡፡ ሸገር ሬዲዮ የተፀነሰው፤ አንጋፋው የኢትዮጵያ ሬዲዮ በመሠረተውና የአገሪቱ የመጀመሪያው የኤፍኤም ሬዲዮ በሆነው በኤፍ ኤም አዲስ 97.1 ስቱዲዮ ውስጥ ከአስራ ሶስት ዓመታት በፊት በ1992 ዓ.ም ነበር፡፡

በአንድ ወቅት የሸገር ሬዲዮ አስኳል የሆነው የ“ጨዋታ” ፕሮግራምን ጅማሮ አስመልክተው የፕሮግራሙ ፕሮድዩሰር አቶ አበበ ባልቻ ሲገልጹ፤ የኤፍኤም አዲስ 97.1 ሥራ አስኪያጅ የነበሩ ሰው፤ ሬዲዮ ጣቢያቸው ለተባባሪ አዘጋጆች የአየር ሰዓቱን ክፍት ሊያደርግ እንዳሰበ እንዳጫወቷቸው አስታውሰው፤ “ስለዚህም በሬዲዮ ላይ የመሥራት ልምድም ሆነ ፍላጐትም ከነበራቸው ከወይዘሮ መዓዛ ብሩ እና ከአቶ ተፈሪ ዓለሙ ጋር በመሆን ቅዳሜ ከቀትር በኋላ ባለው ጊዜ የሚቀርብ ዝግጅት ለማቅረብ መሰናዶ ጀመርን” ብለው ነበር፡፡
 
በዚህም መሠረት ወይዘሮ መዓዛ ብሩ ቀደም ብለው ያቋቋሙት “አደይ ፕሮሞሽን” እና የአቶ ተፈሪ ዓለሙ “ትንሣኤ ኪነጥበባት” ተጣምረው “ጨዋታ” ሲሉ የሰየሙትን ዝግጅት ከኤፍ ኤም አዲስ 97.1 ጋር በመተባበር፣ ቅዳሜ ሐምሌ 1 ቀን 1992 ዓ.ም በአየር ላይ በማዋል ፕሮግራማቸውን በይፋ ጀመሩ፡፡ የጨዋታ ፕሮግራም ዘወትር ቅዳሜ ከሰባት ሰዓት ተኩል እስከ ምሽቱ ሁለት ሰዓት ተኩል ለ420 ደቂቃዎች ያህል የቃለመጠይቅ፣ የድራማና የግጥም፣ የስፖርትና የሙዚቃ ዝግጅቶችን ያቀርብ ጀመር፡፡ ፕሮግራሙ የአዘጋጆቹ ልምድ፣ ችሎታ፣ ጥረትና ለዛ የታከለበት በመሆኑ በአጭር ጊዜ ውስጥ በኤፍ ኤም አዲስ 97.1 ከሚቀርቡ ዝግጅቶች በተወዳጅነት ቀዳሚው ለመሆን በቃ፡፡
 
በዚህ ጊዜ በተለይ የማይዘነጋውና በጨዋታ ፕሮግራም ከሚቀርቡት ዝግጅቶች ሁሉ ተወዳጁ መጀመሪያ በደረጄ ኃይሌ፣ በኋላ በመዓዛ ብሩ ይቀርብ የነበረው “የጨዋታ እንግዳ” የተሰኘው የቃለመጠይቅ ፕሮግራም ነበር፡፡ በዚህ ፕሮግራም በርካታ የአገር ባለውለታ የሆኑ እንግዶች ቀርበው የሥራ እና የሕይወት ትውስታቸውን አካፍለው አድማጩን አስደስተውታል፡፡
በተጨማሪም አንደ ፍቃዱ ተክለማርያም ያሉ ስም ያላቸው ታዋቂ የጥበብ ባለሙያዎች የሚያቀርቧቸው ትረካዎችና የሬዲዮ ድራማዎች ለጨዋታ ፕሮግራም ውበት የሰጡ ፈርጦች ሆነውለት ነበር፡፡ የቅዳሜ ጨዋታ ተቀባይነት እየጨመረ ወደ ሸገር ሬዲዮ እስከተዘዋወረ ድረስ ቀጥሏል፡፡
 
ለመሆኑ ሸገር ሬዲዮ እንዴት ተመሠረተ? ባለቤቱስ ማን ነው የሚለው ጥያቄ የሬዲዮው ወዳጆችና አድናቂዎች ሁሉ ይመስለኛል፡፡ የዚህ ሬዲዮ መስራች፣ ባለቤትና ሥራ አስኪያጅ ወይዘሮ መዓዛ ብሩ ትባላለች፡፡

መዓዛ የተወለደችው እዚህ አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ሲሆን ዘመኑም 1951 ዓ.ም ነበር፡፡ ከአንደኛ እስከ ሶስተኛ ክፍል በሐረርጌ ክፍለ ሀገር በሒርና ከተማ ተምራ፣ ከአራተኛ እስከ 12ኛ ክፍል ያለውን ትምህርቷን ደግሞ በቅድስት ማርያም ትምህርት ቤት (Saint Mary School) ተከታትላ ፈጽማለች፡፡ መዓዛ በትምህርት ቤቷ በክፍል ውስጥ አጫጭር ታሪኮችን ለተማሪዎች በማንበብ ከመታወቋም ሌላ ከፍ ያለ የሥነ - ጽሑፍ ዝንባሌ እንደነበራት የሚያስታውሱት መምህራኗ “አንድ ቀን ታላቅ የጥበብ ሰው እንደሚወጣት እናውቅ ነበር” ይላሉ፡፡
 
መዓዛ በ1971 ዓ.ም በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሥነ - ቋንቋ ጥናት ተቋም ውስጥ በሥነ -ልሣን (Linguistics) ትምህርት ክፍል ተመደበች፡፡ ሥነ - ልሣን መዓዛ የምትፈልገው ጥናት ባለመሆኑ በምደባው ቅር ብትሰኝም፤ በንዑስ ትምህርት ደረጃ (minor study) የምትወስደው የውጭ ቋንቋና ሥነ - ጽሑፍ በመሆኑ ለነበራት ቅሬታ እንደማካካሻ ሆኖላታል፡፡ በዚህ ዩኒቨርሲቲ የሶስተኛ ዓመት ተማሪ ሳለች የተፈጠረ አንድ አጋጣሚ ደግሞ መዓዛንና ሬዲዮንን የሚያስተሳስር ይሆናል፡፡ ይኸውም የኢትዮጵያ ሬዲዮ የፕሮግራሞች ኃላፊ የነበረው አቶ ታደሰ ሙሉነህ ለሚያዘጋጀው የእሁድ የሬዲዮ ፕሮግራም ድራማ የሚጫወቱ ሸጋ ድምጽ ያላቸው ወጣቶችን ሲያፈላልግ ከመዓዛ ጋር ይተዋወቃል፡፡ ድራማው አስታጥቃቸው ይሁን ያሰናዳው ሲሆን የመዓዛ ድምጽ ለሙከራ በስቱዲዮ ተቀርጾ ሲሰማው፣ ታደሰ ሙሉነህ የሚፈልገውና የሚወደው ድምጽ ሆኖ ስላገኘው ይደሰታል፡፡ ከዚህ በኋላም ለእሁድ ፕሮግራም የሚሆኑ ጽሑፎችን በየሳምንቱ እንድታነብለት ያግባባትና የመዓዛና የሬዲዮ ፍቅር በኢትዮጵያ ሬዲዮ ይወለዳል፡፡ ከዚህ ጊዜ ጀምሮ የመዓዛ ድምጽ በእሁድ የሬዲዮ ፕሮግራም አድማጮች ዘንድ የተለመደና የተወደደ ሆነ፡፡ መዓዛም የሌሎችን ጽሑፎች በማንበብ ብቻ ሳትወሰን የራሷን ጽሁፎች እያዘጋጀች የምታቀርብ ንቁ ተሳታፊ በመሆን ከሬዲዮ ፕሮግራሙ ቤተሰቦች እንደ አንዱ ሆነች፡፡ በ1974 ዓ.ም ከዩኒቨርሲቲ ተመርቃ ትምህርቷ ፍጻሜውን እስካገኘ ድረስም መዓዛ ሬዲዮና ትምህርትን ጎን ለጎን ስታስኬድ ቆይታለች፡፡
የመዓዛ የሥራ ዓለም የተጀመረው ግን በምትወደውና በምትፈልገው በኢትዮጵያ ሬዲዮ ውስጥ ሳይሆን መንግስት በመደባት በባህል ሚኒስቴር መስሪያ ቤት ውስጥ ነበር፡፡ ስራዋም ባህልና ስፖርት የተባለው የመስሪያ ቤቱ መምሪያ በሚያሳትመው “መርሐ ስፖርት” የተሰኘ ወርሃዊ የስፖርት መጽሔት (በኋላ ጋዜጣ) ላይ ሆነ፡፡ ምንም እንኳ አዲሱ ስራዋ ከራዲዮ የሚያርቃት ቢሆንም መዓዛ ግን ሳትሸነፍ ሬዲዮን በትርፍ ጊዜ ሥራነት ተያያዘችው፡፡ ሬዲዮ ጣቢያው የሚሠጣትን አነስተኛ ክፍያ እየተቀበለችም ልዩ ልዩ ጭውውቶችን እና መጣጥፎችን በግልና በጋራ በማቅረብ ተወዳጅ ሥራዎቿን ለሕዝብ አበርክታለች፡፡
 
መዓዛ በእሁድ የሬዲዮ ፕሮግራም ታቀርባቸው የነበሩት ሥራዎች ይዘት ማህበራዊ ሕይወት እንዲሠምር በመጣር ላይ ያተኮሩ ሆነው ግልጽ፣ ቀላልና ለዛ ያልተለያቸው ስለነበሩ ከሶስት አሥርት ዓመታት በኋላም ትውስታቸው ከአድማጭ ህሊና አልጠፉም፡፡ በዚሁ ፕሮግራም ላይ መዓዛ ካበረከተቻቸው የፈጠራ ሥራዎቿ ውስጥ ጎልቶ የሚታወሰው “የአዲሱ ቤተሰብ” የተሰኘ ባለ ሰማንያ ስድስት ክፍል ድራማ ሲሆን በዘመኑ ከሊቅ እስከ ደቂቅ ሁሉም የሚያደምጠው ተወዳጅ የቤተሰብ ድራማ ነበር፡፡
መዓዛ በ “መርሀ ስፖርት” እና በሬዲዮ መካከል ሆና ከአራት ዓመት በላይ ከቆየች በኋላ በ1979 ዓ.ም የባህል ሚኒስቴርን ለቅቃ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ተቀጠረች፡፡
 
አዲሱን መስሪያ ቤቷን ከተቀላቀለችበት ከዚህ ጊዜ ጀምሮ ከሬዲዮ እየራቀች መጣች፡፡ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ውስጥ የቆየችው ለሶስት ዓመታት ያህል ሲሆን ከዚያ በኋላ የግሏን የማስታወቂያ ሥራ ድርጅት መሥርታ የራስዋ ተቀጣሪ ሆናለች፡፡ ከ1979 ዓ.ም ጀምሮ እስከ 1992 ዓ.ም ባሉት የአስራ ሶስት ዓመታት ጊዜ ግን መዓዛና ሬዲዮ ተራራቁ፡፡
መዓዛና ሬዲዮ ዳግም የተዋደዱት ከላይ እንደተገለጸው በ1992 ዓ.ም ሳምንታዊውን የ “ጨዋታ” ፕሮግራም በኤፍ ኤም 97.1 ከተፈሪ ዓለሙ ጋር በጋራ ማቅረብ ሲጀምሩ ነበር፡፡ የ “ጨዋታ” ፕሮግራም እስከ 1999 ዓ.ም ድረስ በአድማጮቹ እንደተወደደ በኤፍ ኤም አዲስ 97.1 ላይ ሲቀርብ ቆይቷል፡፡ መንግሥት ለመጀመሪያ ጊዜ ሁለት የኤፍ ኤም ሬዲዮ ፈቃዶችን ለግሉ ዘርፍ ለመስጠት ሲዘጋጅ፣ ዝርዝር የሥራ እቅድ አቅርባ ባመለከተችው መሠረት፤ ከረጅም ጊዜ ቆይታ በኋላ ከአስር አመልካቾች መካከል አንዷ ሆና የመጀመሪያ የግል የኤፍ ኤም ሬዲዮ ባለቤት ያደረጋትን ፈቃድ ተቀበለች፡፡
መዓዛ የሬዲዮ ማሰራጫ መሳሪያዎችን ውድነት፣ የማሰራጫ ቦታ እና የባለሙያ እጦትን ተቋቁማ ሸገር 102.1 ኤፍ ኤም ሬዲዮን በታህሳስ 2009 ዓ.ም አበረከተችልን፡፡

ባለትዳርና የሶስት ልጆች እናት የሆነችው መዓዛ እንደ ባለቤት፣ ሥራ አስኪያጅና ጋዜጠኛ በመሆን በኢትዮጵያ ተወዳጁንና የመጀመሪያውን የግል የኤፍ ኤም ሬዲዮ ጣቢያ ትመራለች፡፡ በመዓዛ ህይወትና ሥራዎችዋ ላይ የመመረቂያ ጥናቱን ለሠራው ለኤርምያስ ወሌ በሚያዝያ ወር 2002 ዓ.ም በሰጠችው ቃለምልልስ “የማይክራፎን ፍቅር አይለቀኝም፤ እስካሁን ድረስ ከሬዲዮ ባለመለየቴም እጅግ ደስተኛ ነኝ” በማለት ስለ ስራዋ ያላትን ስሜት ተናግራለች፡፡
 
ሸገር በዚህ ዓመት የተመሠረተበትን የአምስተኛ ዓመት የልደት በዓሉን ያከብራል፡፡ ሸገር ደካማውን ጎኑን አጠንክሮ፣ ጠንካራውን እያጎለበተ ገና ብዙ ሻማዎች እንደሚለኩስ የአድማጮቹ ተስፋ ነው፡፡ በዚህ አጋጣሚ ወይዘሮ መዓዛ ብሩን፣ አቶ ተፈሪ ዓለሙን እና መላውን የሸገር ሬዲዮ ጣቢያ ሠራተኞችና ጋዜጠኞች እንኳን ለሸገር ሬዲዮ የአምስተኛ ዓመት የልደት በዓል አደረሳችሁ እላለሁ፡፡
“ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኑር!!!”

ጠያቂዋ መዓዛ ብሩ ስትጠየቅ /መዓዛ ብሩ ስለጨዋታ ፕሮግራም ምን ትላለች ?



ቀኝ ጌታ ዮፍታሄ ንጉሴ

ማሽላና ስንዴ በአንድ አብረን ስንቆላ፤
እያረረ ሳቀ የባህር ማሽላ፡፡

ከሰል የሚሆኑ ብዙ እንጨቶች ሳሉ፤
ዝግባ ለምን ይሆን ይቆረጥ የሚሉ፡፡


         የሰማይ አሞራ ልጠይቅሽ ወሬ፣
         ተቃጥሏል መሰለኝ ሸተተኝ አገሬ፡፡

       
         ለጌሾ ወቀጣ ማንም ሰው አልመጣ
         ለመጠጡ ጊዜ ከየጐሬው ወጣ፡፡

         ቀኝ ጌታ ዮፍታሄ ከተውኔት ድርሰታቸው በተጨማሪ መዝሙሮችንና ግጥሞችን ደርሰዋል፡፡ የኢትዮጵያ አንድነትና የህብረት መዝሙር የሚገልጽልንን የኢትዮጵያ ህዝብ መዝሙር (ተፈሪ ማርሽ)፣ ወላድ ኢትዮጵያ፣ አጥንቱን ልልቀመው፣ ድንግል አገሬ ሆይ የሚባሉ መዝሙሮችን ደርሰዋል፡፡ አጥንቱን ልልቀመው የሚለው ግጥም አርበኞቹን የዶጋሊውን አሉላ አባ ነጋ እና ራስ ጎበናን በማነፃፀር የገጠሙት ግጥም ሲሆን ድንግል ሀገሬ ሆይ የተሰኘውን ድርሰት የፃፉት በስደት ኢሊባቡር ሆነው በ1929 ዓ.ም ነበር፡፡ ይህ መዝሙር ከመጀመሪያ ረድፍ ከሚጠቀሱት ስራዎቻቸው ቀዳሚው ነው፡፡

             ድንግል ሀገሩ ሆይ ጥንተ ተደንግሎ
             ጥንተ ተደንግሎ ጥንተ ተደንግሎ
             ህፃናቱ ታርደው ያንቺም ልብ ቆስሎ
             ልጅሽ ተሰደደ አንቺን ተከትሎ
             የህፃናቱ ደም አዘክሪ ኩሎ፡፡
             አዝማች፤ አስጨነቀኝ ስደትሽ
             እመቤቴ ተመለሺ እመቤቴ ተመለሺ


ይሄ ግጥም ዮፍታሄ ንጉሴ ህዝቡ በፋሺስት ወረራ የደረሰበትን ስደት የገለፁበት ስንኝ ነው፡፡ ቅድስት ድንግል ማርያም ከእስራኤል ወደ ግብጽ ያደረገችውን ስደት እና በኤሮድስ ህፃናት መቀላታቸውን ከኢትዮጵያ ስደት ጋር ያነፃፀሩበት ግጥምም ነው፡፡ የቀኝ ጌታ ዮፍታሄ ግጥሞች ትንቢታዊ ሲሆኑ በአንድ ስንኝ የሚጽፉት ግጥም ተሰጦአቸው የላቀ መሆኑን ያሳየናል፡
የቀኝ ጌታ ዮፍታሄ አፃፃፍ ለተከታዮቹ ደራሲያን ምሳሌ ስለነበር አንጋፋነታቸው ታላቅ ዋጋ የሚሰጠው ነው፡፡ ዮፍታሄ በግእዝ ቅኔ የበሰሉ ስለነበሩ አማርኛ የስነ ጽሑፍ ቋንቋ እንዲሆንና እንዲያድግ የላቀ አስተዋፅኦ አበርክተዋል፡፡

     የአማርኛ ስነ ጽሑፍን ለማሳደግ በተውኔት፣ በግጥም፣ በዘፈን እና በመዝሙር ባደረጉት ጥረት በኢትዮጵያ ስነ ጽሑፍ ታሪክ ውስጥ ከፍተኛ የክብር ቦታ አላቸው፡፡ ባለ ቅኔው ዮፍታሄ ከጣሊያን ወረራ በኋላ እስከ 1941 ዓ.ም የህግ መወሰኛ ምክር ቤት ምክትል ፕሬዝዳንት ሆነው ሲሰሩ ቆይተው በ1942 ዓ.ም አርፈዋል፡፡ የባለ ቅኔው ዮፍታሄ ስራዎች ግን ተጽእኖ ፈጥረው ከትውልድ ወደ ትውልድ ይሸጋገራሉ፡፡

ቀኝ ጌታ ዮፍታሄ ንጉሴ  ሥራዎች:--

1. እኔ አይኔን ሰው አማረው (ግጥምና ቅኔ)
2. ዐጥንቱን ልልቀመው፥ መቃብር ቆፍሬ (ግጥምና ቅኔ)
3. ወላድ ኢትዮጵያ ለልጆቿ ብላ (ግጥምና ቅኔ)
4. ጎበዛዝቴ ሆይ ወይ ቆነጃጅቴ (ግጥምና ቅኔ)
5. ሰውን ሰው ቢወደው አይኾንም እንደራስ (ግጥምና ቅኔ)
6. አወይ ጥርሴ ሞኙ ዘወትር ይሥቃል (ግጥምና ቅኔ)
7. ሙናዬ (ግጥምና ቅኔ)
8. የኛማ ሙሽራ (ግጥምና ቅኔ)
9. አንተ ባለጐዛ (ግጥምና ቅኔ)
10. ድንግል አገሬ ሆይ ጥንተ ተደንግሎ (ግጥምና ቅኔ)
11. የእኛማ ሀገር (ግጥምና ቅኔ)
12. ሰለኢትዮጵያ (ግጥምና ቅኔ)
13. ትንሽ ዐማርኛ (ግጥምና ቅኔ)
14. የሥነ- በዓል መዝሙር...እንደመፋቂያ (ግጥምና ቅኔ)
15. ጉሰማዬ (ግጥምና ቅኔ)
16. ተነሱ ታጠቁ (ግጥምና ቅኔ)
17. አብሪ ብርሃንሽን (ግጥምና ቅኔ)
18. የባሕር ዳር ጨፌ (ግጥምና ቅኔ)
19. ባገር ገዳይ፥ቋጥኝ ድንጋይ... (ግጥምና ቅኔ)
20. በለስ ለመለመች (ግጥምና ቅኔ)
21. እስክትመጣ ድረስ... (ግጥምና ቅኔ)
22. ጎሐ ጽባሕ (ግጥምና ቅኔ)
23. አገሬ ኢትዮጵያ...ሞኝ ነሽ ተላላ... (ግጥምና ቅኔ)
24. የኢትዮጵያ ሕዝብ መዝሙር (ግጥምና ቅኔ)
25. የሰንደቅ ዓላማ መዝሙር ደሙን:ያፈሰሰ፥ተጣማጅ: አርበኛ (ግጥምና ቅኔ)
26. አፋጀሽኝ (ተውኔት)
27. እያዩ ማዘን (ተውኔት)
28. ስለአያ ከምሱና ስለአያ እነባንት ይቀጡ (ተውኔት)
29. እለቄጥሩ /ጎበዝ አየን /  (ተውኔት)
30. ጥቅም ያለበት ጨዋታ (ተውኔት)
31. የሕዝብ ፀፀት፥የእመት በልዩ ጉዳት (ተውኔት)
32. የሆድ አምላኩ ቅጣት (ተውኔት)
33. ዕርበተ ፀሐይ (ተውኔት)
34. ምስክር (ተውኔት)
35. ያማረ ምላሽ (ተውኔት)
36. ዳዲቱራ (ተውኔት)
37. ሞሽሪት ሙሽራ (ተውኔት)
38. መሸ በከንቱ፥ ሥራ ለፈቱ (ተውኔት)
39. ጠረፍ ይጠበቅ (ተውኔት)
40. ዓለም አታላይ (ተውኔት)
41. የደንቆሮዎች ትያትር (ተውኔት)
42. ንጉሡና ዘውድ (ተውኔት)




        ምንጭ:-- http://mekilit.blogspot.com/2014/02/1885.html





አኮቴት ስለሚገባት እንስት ጋዜጠኛ

ክፍል- ፩
 *****
ሀተታ ሀ…
የዚህ ፅሁፍ መነሻ እውነት ነው…. እውነት እንደመነሻ እንጂ ያላግባብ ምስጋና ለማቅረብ ታስቦ አይደለም፡፡ ለመተዋወቅና ዝምድና ለመፍጠርም አይደለም፡፡
ጉርሻ ቢጤ ነገር ለማግኘት ማሞካሸት የሚል እሳቤም አልያዘም፡፡ የብልጠት ምስጋና እንዲሆን ታስቦ የተደረገም አይደለም፡፡ በፍፁም፡፡ በእውነት እውቀት እንጂ በብልጣብልጥነት የኖረ… የሚቀጥል ሀገር አለ ብሎ ጸሐፊው አያምንም፡፡ በመሆኑም የብልጠት መወድስ አይደለም፡፡ እውነት ግን ምክንያት ነበር፡፡ የሰራ ስው ሊወደስ እና ሊመሰገን ይገባል፡፡ የሚል እውነት ነው፡፡ ቤቴ ከባልንጀሮቼ ጋር ቁጭ ብዬ የማወራው… የሚያስወራ ርዕሰ ጉዳይ ከብዙ ጊዜ በኋላ በማግኘቴ የልቤን የእውነት ምስጋና ለማቀበል ያህል ነው፡፡
ሀተታ ሁ…
ጠጠር በምታክል የህይወት ተሞክሮዬ ውስጥ የማይረሱ እና ሊዘነጉ የማይችሉ የሬዲዮ ፕሮግራሞችን መጥቀስ እችላለሁ፡፡ የእውነትም ነበሩ፡፡ታዲያ ለኔ ቀድሞ የሚመጣው ዶ/ር እጓለ ገ/ዮሀንስ “የከፍተኛ ትምህርት ዘይቤ” ብለው በሬዲዮ ያደረጉት ንግግር ነው፡፡ በሬዲዮ ሲተላለፍ ባላዳምጠውም በመፅሀፍ መልክ በመታተሙ ለማንበብ እድል አግኝቻለሁ፡፡ ንግግሩ የተደረገበት ዋና መንስኤም አፄ ሀይለስላሴ ገነተ ልዑል ቤተመንግስትን ለዩኒቨርስቲ መገልገያ እንዲውል በማድረጋቸው ነበር፡፡ ንግግር ተባለ እንጂ ታስቦ የተፃፈ የሊቅ መፅሀፍ ነው ለኔ፡፡ ሀገሬ እንዴት ያለች የሊቅ ሀገር እንደሆነች ከሚያስረግጡ የሬዲዮ ንግግሮች መካከል እንዱ ነው ማለት ይቻላል፡፡
መፅሀፉን ያላነበባችሁት ብታነቡት መልካም ፍሬን ታገኙበታላችሁ በማለት ወደ ሚቀጥለው ሀሳቤ ልሻገር፡፡
ከሰማኋቸው እና እውቀት እውቀት ከሚሸቱ የሬዲዮ ፕሮግራሞች መካከል ከዛሬ 13 ዓመት በፊት ገደማ በኢትዮጵያ ሬዲዮ ይቀርቡ የነበሩት የ “እሁድ ጥዋት” እና “ቅዳሜ ወጣቶች” ፕሮግራም የማይዘነጉኝ ናቸው፡፡ በአንዲት ትንሽ የገጠር መንደር…በሰፈሩ ብቸኛ በሆነችው… በመቀጥቀጥ ብዛት የቢራ ጠርሙስ በመሳሰሉ ባትሪዎች በምትንቀሳቀሰው ያላምሬ ሬዲዮ የሱማሌ፣ የትግራይ እና የደቡብ ወንድሜን የሕይወት ልምድ፣ ተሞክሮ ያሳውቀኝ እና እሩቅ ሀገር ስላለው ኢትዮጵያዊ ወንድሜ መንፈሳዊ ቅናት ይፈጥርብኝ የነበረው የቅዳሜ የወጣቶች ፕሮግራም ድንቅ ነበር፡፡ ፕሮግራሞቹ ኢትዮጵያዊነትን የሚሰብኩ፣ ወጣትነትን በእጅጉ የሚገልፁ እና የሚያንፁም ነበሩ፡፡ ወይ ጉድ! … እኔም በዚች እድሜዬ ነበሩ ካልኩ የሆነ ቦታ የተቋረጠ እና የተረሳ ነገር አለ ማለት ነው፡፡ ችግር አለ እንደማለትም ያስኬዳል፡፡
ትምህርት ቤት ሰኞ ጠዋት በእረፍት ጊዜ ለ15 ደቂቃ የምንወያይበትን ዕርሰ ጉዳይ የሚሰጠን ሌላው የሬዲዮ ፕሮግራም “ከመጻህፍት ዓለም” ነበር፡፡ በሚጢጢ አንጎላችን ስለገፀባህሪ አሳሳል፣ ስለሰው ምንነት የተከራከረንበትን ጊዜ አልረሳውም፡፡ ቃል የተባል መጸሕፍ ሲተረክ ጥጉ ይልማ ከጸሀይ ይበልጣል ብዬ በመከራከሬ የቀመስኩት ቦክስ ምልክቱ ዛሬም አለ፡፡ በአጠቃላይ ግን ለዛ ያላቸው እና ማንነትን የሚቀርጹ ፕሮግራሞች ነበሩ፡፡ ነበሩ… ነበሩ… ብቻ፡፡
ሀተታ…..
“ከትላንት ዛሬ ይሻላል ነው ይበልጣል” የሚለውን ሀረግ ከየት እንዳነበብኩት አላስታውሰውም፡፡ ዛሬ… በኔ ጊዜ ግን አብዛኞዎቹ በሬዲዮ የሚቀርቡ ፕሮግራሞች ልደትን ለማክበር የተሰናዱ ይመስላሉ፡፡ በኔ ጊዜ ያሉ የሬዲዮ ጣቢያዎች በአራዳ ቋንቋ ብገልፀው … ለ‘ኢንጆይ’ የተቋቋሙ ይመስለኛል፡፡ ድረ ገፅ ላይ የተፃፈ እንግሊዘኛን ወደ አማርኛ ገልብጦ ማንበቢያ ጣቢያም ይመስሉኛል፡፡ ያልተጣራ መረጃ እና መረጃን ብቻ ለማስተላለፍ የተቋቋሙም ይመስሉኛል፡፡ ለምሳሌ አንድ የክልል ከተማ ላይ የተቋቋመ የሬዲዮ ጣቢያ ስለ አንድ የውጭ ሀገር ዜጋ ሙሉ ጊዜውን ሰጥቶ መለፍለፍ ፋይዳው ለኔ አይገባኝም፡፡ እንዲገባኝም አልገደድም፡፡ ይልቁኑስ የአካባቢውን እውነታ፣ ውበት ማንነት እና በራስ የመኩራት ባህል፣ በአጠቃላይ ደግሞ ኢትዮጵያዊ ማንነት ተኮር ስለሆነ ነገር በሬዲዮ ማውራት ግን ለብዙ አርቆ
አሳቢዎች ይገባቸዋል፡፡
እንደ እውነቱ ከሆነ ‘ግሎባላይዜሽን’ ከሚያመጣው ጣጣ አንዱ መዋዋጥ ነው፡፡ የሀገሬ የሬዲዮ ፕሮግራሞችም መነሻ አላማ መሆን የነበረበት ከዚህ መዋዋጥ የምንወጣበትን መንገድ በማመልከት፤ ጥርት ባለ ኢትዮጵያዊነት መኩራት ምን ማለት ነው የሚል ሀገራዊ አንድምታ ያለውን ሀሳብ ይዞ መቅረብ ነው፡ ነገር ግን ፕሮግራማቸው ቀድሞ ከተዋጠ ወጤቱ አስፈሪ ነው የሚሆነው፡፡ በተለይ የሚዲያ ተፅዕኖ ክብደትን ሳስብ መጭው ጊዜ ያስፈራኛል፡፡ የወገኛ ነገር ሆኖብኝ እንጂ የጽሁፌ አላማ ስለጣቢያዎች የፕሮግራም ይዘት ማውራት አልነበረም፡፡ ግን ደግሞ በሰከነ አእምሮ እንዲያስቡ ጠቁሞ ማለፍ ክፋቱ አይታየኝም፡፡
ሀተታ አ…
ቀደም ብዬ ለማስገንዘብ እንደሞከርኩት የጽሑፌ መነሻ አላማ ስለ አንድ ብርቱ እንስት የሬድዮ ጋዜጠኛ አኮቴት ማቅረብ ነው፡፡ ብርቱ እንስት የሬዲዮ ጋዜጠኛ ብዬ መፃፍ ስጀምር፣ መዓዛ ብሩ የምትባል የሸገር በተለይ ደግሞ “የጨዋታ እንግዳ” አስተናጋጅ ጋዜጠኛ በአንባቢያን አእምሮ እንደምትከሰት እገምታለሁ፡፡ በኔ ጊዜ እየቀረቡ ካሉት የሬዲዮ ፕሮግራሞች በተለየ መልኩ ብርሀን ለመፈንጠቅ የምትታትር ጋዜጠኛ ነች፤ መዓዛ ብሩ፡፡ እውነት ነው፤ እኛ ወጣት ኢትዮጵያዊያን የሆነ ብርሀን በማጣት እና የባዕድ ሀገር ተብለጭላጭ ብርሃን መሳይን ነገር በመሻት ውቅያኖስ ላይ እንደተጣለ ኩበት እየዋለልን እንደሆንን እኔን እንደማስረጃ ማቅረብ ወይም የጎረቤቴን ልጅ መጥቀስ በቂ ነው፡፡ ዛሬ ከአድዋ ጀግኖች ይልቅ ቬትናም ላይ ጦርነት ያወጁ የአሜሪካ ‘ጀግኖች’ በልጠውብን በጣም በታመምንበት ሰዓት፣ “የጨዋታ እንግዳ” የተሰኘ የሬዲዮ ፕሮግራም መኖሩ እውነትም ይህች ሀገር ብዙ ተቆርቋሪ ዜጋ እንዳሏት የሚያመላክት ነው፡፡
አኮቴቴ የጨበጣ እንዳይሆን ግን ምክንያቶቼን ለመጥቀስ ልሞክር፡፡ የአዋቂ እይታ ስም ከማውጣት ይነሳልና ከስሙ ልጀምር፤ “የጨዋታ እንግዳ” ጨዋታ ለአብዛኛዎቻችን እንግዳ ቃል አይደለም፡፡ ከህፃን እስከ አዋቂ፣ ከሊቅ እስከ ደቂቅ ያለ የህይወት ምግብ ነው፡፡ ልብ ካላችሁ ደግሞ ቤተሰቦቻችን “ልጆች ጨዋታ ላይ ነን” ካሉ ቁም ነገር እየሰሩ ነው፡፡ እከሌ እኮ ጨዋታ አዋቂ ነውም ይባላል፡፡ በትያትረኛ ስንመለከተው ደግሞ በቅድመ-ቅኝ ግዛት በአፍሪካ ለትያትር መኖር ወይም መፈጠር ጨዋታ አዋቂዎች እንደመነሻ ምክንያት ይታያሉ፡፡ ጨዋታ የሚለው ቃል አስደንቆን ሳንጨርስ እንግዳ ይከተላል፡፡ እኔን፣ አንተን፣ አንችን፣ እኛን ሊገልፅ የሚችል ቃል ነው፡፡ በኢትዮጵያዊታችን ከምንኮራባቸው እና የጋራ መገለጫዎቻችን ከሆኑት አንዱ እንግዳ ተቀብለን ማክበራችን ነው፡፡ እንደ “ጨዋታ እንግዳ” አይነቱ ቀላል እና ሳቢ አገላለፅ የስነጥበብ አንዱ መገለጫ እንደሆነም ብዙዎች አስረግጠው ይናገራሉ፡፡ ከዚህ ይበልጥ ደግሞ አብረሀም በእንግዳ ተቀባይነቱ ሶስቱ ስላሴዎችን እንዳስተናገደ ሁሉ፤ በጨዋታ እንግዳ የቀረቡ ብዙ አዋቂ፣ መርማሪ፣ አርቆ አሳቢ እና ሀገርኛ የሆኑ ዘመዶቼ መሆናቸውን ሳስብ እውነትም ስምን መልዓክ ያወጣዋል እንድል ይስገድደኛል፡፡ ከስያሜው ወጣ ብዬ መዓዛ ብሩን በአደባባይ እንዳመሰግናት ስላደረጉኝ ብዙ ነገሮች ለማውራት ትህትና የበዛው ድፍረት በቂ ይመስለኛል፡፡ መዓዛ ብሩ አብዝታ የጋዜጠኛ ስነምግባርን የተላበሰች፣ ለበቃ የጋዜጠኝነት ሙያ የተፈጠረች ብቁ ጋዜጠኛ ነች፡፡ እንዴት?
ስለጋዜጠኝነት ስነምግባር ሲወራ ቀድሞ የሚመጣው ጋዜጠኛ እውነትን የመሻቱ ጉዳይ ነው፡፡ መዓዛ እንግዶቿን ስታጨዋውት የተረዳሁት ነገር ቢኖር ይሄ እና ይሄ ብቻ ነው፡፡ ሀቁን በራሷ እይታ ለመተንተን አትደፍርም፡፡ አንድ ጥያቄ ጠይቀው መልሱን እራሳቸው እንደሚመልሱት እና በእንግዳቸው ላይ ተፅኖ ለመፍጠር እንደሚታገሉ ጋዜጠኞች አይነት አይደለችም፡፡ ሀቁ እንዲወጣ ግን የበሰለ የቤት ስራዋን ሰርታ ትመጣለች፡፡ አንዳንዴ “እንግዶቿ ከየት ያገኘችው መረጃ ነው?” እስኪሉ ድረስ ጥናቷ እጅግ በጣም ጥልቀት አለው፡፡ እንደአብዛኛዎቹ ልደትህ መቼ ነው የሚከበረው? የምግብ የመጠጥ፣ እና የልብስ ምርጫህ ምን ይመስላል? ድመት አትወድም አሉ? ጀምስ ቦንድ የተባለው ፈረንጅ አብሮህ እንዲሰራ ጠይቆህ ነበር? የሚሉ አይነት ጥያቄዎች ከመዓዛ አንደበት አልሰማሁም፡፡ ይልቁንም እውነት… በተለይ ደግሞ ኢትዮጵያዊ ማንነትን ሊገነባ የሚችል ሀቅ እንዲወጣ እሳቷን ትለኩሳለች፡፡ ለኔ መረጃ እውቀት የሚሆነው በዚሁ ረገድ ነው ብዬ እተማመናለሁ፡፡
መዓዛ ለምታነሳው ርዕሠ ጉዳይ እራሷን ከምንጩ ትነጥላለች፡፡ ከስሜታዊነት የፀዱ ጥያቄዎችን በማሰናዳትም ከሙያው የሚጠበቀውን ስነምግባር ትጠብቃለች፡፡ በመዓዛ “የጨዋታ እንግዳ” የምናውቀው አንድ እና አንድ ነገር መዓዛ ብሩ የምትባል ጋዜጠኛ እንግዳ ስትጠይቅ ብቻ፡፡ ጥያቄዎቿም ከራስ ስሜት የፀዱ ናቸው፡፡
ለአድማጭ ፍላጎት እና ስሜት ቅድሚያ የምትሰጥ ጋዜጠኛ ናት፡፡ ይህ አይነቱ ስነምግባር አፍሪካ ውስጥ ለሚገኙ ጋዜጠኞች ፈታኝ እና የማይታሰብ ነው፡፡ መዓዛ ጥቁር እንግዳ ብላ ከጋበዘች፤ እንትና የሚባል ግለስብ፣ እነእንትና የሚባሉ ሰዎች ወይንም እንትን የሚባል መደብ ይከፋዋል የሚል የደካማ ምክንያት ተብትቦ ሲይዛት እስካሁን አልታዘብኩም፡፡ ጥያቄዎቿ የማንም ተፅዕኖ ሲያደበዝዘው አይታይም፡፡ የሀቁ ጠቀሜታ ለአድማጯ እስካመዘነ ድረስ ከመጠየቅ ወደ ኋላ አትልም፡፡
የመዓዛ ብሩ ሂስ እና የመቻቻል መድረክ
ይህ እንድፅፍ ካስገደደኝ ሁነኛ የመዓዛ ጥንካሬ መገለጫዎች የመጀመሪያውን ደረጃ ይዞ ይገኛል፡፡ የምንጠያየቅበትን፣ የምንተቻችበትን እና ካለፈው ተምረን የወደፊቱን የምንተነብይበትን መድረክ በማዘጋጀት መዓዛ ትልቅ ድርሻ እየተወጣች ትገኛለች፡፡ የታሪክ ክፍተቶች በበጎ እንዲሞሉ ትተጋለች፡፡ የትውልድ ቀጣይነት እንዲኖር መመኘት ብቻ ሳይሆን እውን እንዲሆን ትሮጣለች፡፡ በተለይ ደግሞ በ “ጨዋታ እንግዳ” የቀረቡ እንግዶች የዘነጋናቸው ወይንም በተዳፈነ አስተሳሰብ ከሆነ መደብ ጋር መድበን ቂም የያዘንባቸው፤ ሀቁ ሲወጣ ግን በየቤታችን ይቅር ይበሉን ያልናቸው ሊቃውንት ናቸው፡፡ እናም እንደ ሲኤንኤኑ ላሪ ኪንግ እና የሀርድ ቶኩ ስቴቨን ጆን ሳካር፣ መዓዛም ምርቱ ከገለባው የሚለይበት፣ ምክንያታዊ ዳኝነት ገዥ ሀሳብ የሚሆንብት መድረክ ነው የ “ጨዋታ እንግዳ”ዋ ፡፡አቦ መዓዛ ይመችሽ!
ከዚህ በላይ ስለመዓዛ ብቁ የጋዜጠኝነት ተሰጥኦ ለመተንተን ሰፊ እና ጥልቅ የጋዜጠኝነት እውቀት ይፈልጋል፡ለማድነቅ ግን ክፍት አእምሮ፣ ተራማጅ አስተሳሰብ እና ስሜት በቂ ነው ባይ ነኝ፡፡ነገ ብዙ መዓዛዎች እንዲመጡ እና ሌላ መዓዛ እንድናሸት ሁሌም በርችልን፡፡ በስተመጨረሻ መዓዛ “የጨዋታ እንግዳ” ብላ ሰዎችን መጋበዟ አንድምታው ምን ይሆን?.... ሙያው ውስጥ ላሉ ባልንጀሮቿ ብዙ ብዙ ነው መልዕክቱ፡፡ መቸም ለብልህ ሁለቴ አይነግሩትም፡፡
ለኛ… በየትኛውም ቦታ ተሰማርተን ቀና ደፋ ለምንል ወጣቶች ደግሞ ቃሉ ሰፊ ነው፡፡ በ “ጨዋታ እንግዳ” ከቀረቡ ልሂቃን መካከል የአንዱን ሊቅ ንግግር ልውሰድና እኔ እንደሚመቸኝ አድርጌ ላቅርበው፡፡ ለሁሉም ኢትዮጵያዊ የመጀመሪያ፣ የማትቀየር እና ምርጫ የሌላት እጮኛው ኢትዮጵያ ናት፡፡
የዚችን ድንቅ እጮኛ ሁኔታ እና ያልተፈታ እውነት ለማወቅ መጠየቅ፣ ጠይቆም ደጉን ከክፉ መለየት፡፡ ምክንያቱም እጅን አጣጥፎ ከመቀመጥ መጠየቅ ይበልጣል፡፡ ከመጠየቅም ደግሞ እጅግ በጣም መጠየቅ ያዋጣል፡፡ እንደ ሀገርም እንደራስም ለመኖር ሳናስተውል “አብቅቶላቸዋል… ያዛውንት ቃል ምንተዳዬ” ብለን የዘነጋናቸውን ፣ በአካባቢያችን ያሉ አዛውንትን እየጠየቅን መቅረፅ፣ መሠነድ ክፍተታችንን ለመሙላት አማራጭ የሌለው ማለፊያ መንገድ ነው፡፡
******************************************************
ምንጭ:---http://www.addisadmassnews.com

እሑድ, ኖቬምበር 25, 2012

ኢትዮጵያን ከእግዚአብሔር እጅ እንሻት


 (ሰኔ ፲፱፻፺፯ ዓ. ም.)
 
በ፲፱፻፹፫ ዓ.ም. ብዙ ሆነን ከአሰብ ተሰድደን በጅቡቲ በኩል ለማለፍ ስንሞክር የፈረንሳይ ወታደሮች አንድ ሜዳ ላይ አገቱን። እጅግ በጣም ሐሩር ስለነበር ከመንገላታት ጋር አንዳንዶቻችን በብርቱ ታመን ነበር። ከፊት ለፊቴ ቆሞ በጠላትነት አይን እያየ፣ በመሣሪያው እያስፈራራ፣ አንዳንዴም እየገፈተረ፣ መተላለፊያ የሚከለክለኝን ወጣት ፈረንሳዊ እያየሁ በሃሳብ ሰመጥኩ። እኔን የሚመስሉ ዘመዶቸ በሚኖሩበት መሬት እንዳላልፍ ከፈረንሳይ አገር መጥቶ ከለከለኝ ። መሰደዴ ደግሞ እሱን የሚመስሉ ሰዎች ባዘጋጁት ውጥን ነው። ይህ ወጣት ከሩቅ አገር መጥቶ በሰፈሬ እንዳላልፍ የከለከለኝ በጠማማ መንገድ ከሚሄድ ባለጠጋ ያለነውር የሚሄድ ደሀ ይሻላል ተብሎ እንደተጻፈው አባቱ ከሩቅ አገር መጥተው በአራጣ ብዛትና በቅሚያ የአባቴን ስለወሰዱ አይደለምን? ታዲያ ይህ ፈረንሳዊ ካባቱ አንድ ጊዜ ባገኘው አስነዋሪ ትርፍ ምክንያት የሱ ልጅ ከሩቅ አገር መጥቶ የሰው መብት ከልካይ፤ የኔ ልጅ ደግሞ በራሱ ሰፈር መብቱ የተዋረደ መሆኑ አይደለምን? ብየ አሰብኩ። ብዙ ሰው እንደዚህ አለማሰቡ መልካም ሆነ እንጂ ነገሩ መንፈስን የሚያውክ ነገር ነው። ከዚህ በሁዋላ ብዙወችን ነገሮች ሳያቸው ስለማናውቀው ነው እንጂ እኛ ፈልገን የምናመጣው የስብእና ውርደት በብዙ መልክ እንዳለ ተገነዘብኩ። እባካችሁ አገራችን ውስጥ ያለውን መንግሥት ቀይሩልን ብሎ ሌሎችን አገሮች ደጅ መጥናት እራሱ ውርደት ነው። በአገር ውስጥ፣ በቤተመንግሥቱ፣ በየመንገዱ፣ በየምግብ ቤቱ፣ በየመጠጥ ቤቱ፣ በየህዝብ አገልግሎት ተቅዋሙ የውጭ አገር ሰው ሲከበር ኢትዮጵያዊ ግን በኢትዮጵያውያን ዘንድ ተንቆ ማየት ውርደት ነው። ከኢትዮጵያዊ አዋቂወች ወይም ከአዛውንቶችዋ ምክር ይልቅ ኢትዮጵያን ጥቂት ቀን ጎብኝቶ ወይም በቴሌቪዢን አይቶ "ለኢትዮጵያ ችግር መፍትሔው ይሄ ነው" ብሎ የውጭ አገር ሰው የሚጽፈውን እያስተጋቡ መኖር ውርደት ነው። ከሊህቅ እስከ ደቂቅ ከኢትዮጵያዊነት ይልቅ የውጭ አገር ሰው መምሰልን መፈለግ ውርደት ነው። ስለኢትዮጵያ ችግር፣ ለችግሮችዋም መፍትሄ ይሆናል የሚለውን መልዕክቱን ሁሉም ሰው ሊያሰማ የሚፈልገው ለውጭ አገር ሰወች እንጅ ለኢትዮጵያውያን አለመሆኑ ውርደት ነው። ተማሪው እስከ መምህሩ፣ ልጅ እስከ አባቱ፣ ዲያቆኑ እስከ ጳጳሱ ድረስ አገርን ለቆ መሄድን መሻታቸው ለኢትዮጵያውያን ውርደት ነው።  አገርን ለቆ በውጭ አገር ለመኖር ከመፈለግ ብዛት ካህናት እንኩዋን ሳይቀሩ በየኤንንባሲው የሃሰት ምክንያትና ኑዛዜን ማቅረባቸው ውርደት ነው።  

በህሊና አስቦ በውን አመዛዝኖ መሥራትም ከቀረ ውሎ አድሮአል። የውጭ አገር ሰዎች ያሉትን እንደገደል ማሚቶ መልሶ መላልሶ ከማስተጋባት ብዛት እግዚአብሔር ያለጭንቅላት የፈጠረን እያስመሰልነው ነው። አንድ ጊዜ በውጭ አገር የቲዮሎጅ ትምህርት የማስትሬት ዲግሪ አግኝቻለሁ ብለው ኢትዮጵያ ካገኙት የክህነት ትምህርት ይልቅ በማስትሬቱ ዲግሪ የሚኮሩ አንድ ካህን "ኢትዮጵያ የሰው ልጅ መጀመሪያ የተገኘባት መሆንዋ በሳይንስም ተረጋግጥዋል" ብለዉ ስብከታቸውን "በሉሲ" ታሪክ ሲጀምሩ ትዝ ይለኛል። የፈረንጆቹ ትምህርት "ሉሲ ሰው መሆን የጀመረች ዝንጆሮ ናት" እንደሚል ካህኑ አላወቁም። ፈረንጅ የተናገረውን ያለጥያቄ ማስተጋባት ባህል እየሆነ ስለመጣ ፈረንጅ ከተናገረው እሱኑ መውሰድ እንጅ እሳቸው ምን በወጣቸው ምስጢሩን ይመርምሩ? ይህ ምሳሌ ነው፤ ይሁን እንጂ ከመቶ አመት ወዲህ የተወለደ ኢትዮጵያዊ እንደካህኑ "የምሠራውን፣ የምበላዉን፣ የማስበውንና የምናገረውን ነገር ፈረንጅ አዘጋጅቶ ይስጠኝ" የሚል ነው።
የራሳችን የሆነውን ማን ወሰደው?

የችግሩን ተፈጥሮ ለመንገር በሺህ የሚቆጠሩ ጽሁፎች በመቶ የሚቆጠሩ ጉዳዮችን በማንሳት ተግሣጽና ወቀሳን ሲያደርጉ ይሄው ሃምሳ አመት ሊሞላ ነው። ሁሉም በየተራው የችግሩ ምንጭ "ንጉሣዊ አገዛዝ፣ መሬት ያራሹ አለመሆን፣ ፊዩዳሊዝም፣ ቡርዥዋወች፣ ኢምፔሪያሊዝም፣ ወታደራዊ አገዛዝ፣ የዘር አገዛዝ፣ የዲሞክራሲ አለመኖር፣ የመብት መጥፋት፣ እገሌ የሚባለው ጎሣ ጨቁዋኝ መሆን፣ እገሌ የሚባለው ጎሣ ጦረኛ መሆን፣ ወዘተረፈ" እያሉ ጽፈዋል። የሚደማመጥ የለም እንጅ የሚጻጻፍ ሞልቶ ነበር። በመጻጻፍ የተግባባ እስካሁን አላየንም። በመጻጻፍ መበሻሸቅ ግን በየቀኑ የምናየው ትዕይንት ነው። ተጽፈው የምናነባቸው መፍትሄወችም "የትጥቅ ትግል ማድረግ፣ ተጨማሪ የሚወነጅሉ ጽሁፎችን መጻፍ፣ ሰላማዊ ሰልፍ ማድረግ፣ ጉልበት ላላቸው መንግሥታት ማመልከቻ ማቅረብ፣ ወዘተረፈ" የሚሉ ናቸው። ሁሉም ተደረጉ፤ መልካም ቀን አልመጣም። በጦር ብልጫ ወይም በተቃውሞ ብዛት አንዱ አሽናፊ ከሆነ ሌላው ደግሞ ጠመንጃ አንስቶ የተዋጊነት ዙር ይደርሰዋል። ኢትዮጵያን ከጦር ሜዳ፣ ወይም ከሰላማዊ ሰልፍ መንበር፣ ወይም ከኃያላን መንግሥታት ችሮታ ለማግኜት መሞከር ሞኝነት ነው። መልካምዋ ኢትዮጵያ ከኃያላን መንግሥታት ጀርባ አልተደበቀችም። በጦርነትና በሰላማዊ ሰልፍ ማህደር ውስጥም አልተሸሸገችም። በክፉ ሥራችን ከኛ ጠፍታለች፤
እንድናገኛት ከእግዚአብሔር እጅ እንሻት

የእግዚአብሔር ፍርድ ሳይዉል ሳያድር የሚፈጸምባት ወይም የሚፈጸምላት ክፉ ሥራችን ያጠፋት ኢትዮጵያ በእግዚአብሔር የተለየች ሀገር መሆንዋን ያልተገነዘቡ መልሰው መላልሰው ቢያስተዉሉ መልካም ነው። እንደራስ መሆንን ትቶ ሌሎችን ለመምሰል መጣር ይህን ካለማስተዋል የመነጨ ፍላጎት ነው።         

ልጅ እያሱ በግርማዊነታቸው በአፄ ኃይለሥላሴ ትእዛዝ እስር ቤት እያሉ ጣሊያን ኢትዮጵያን መውረር ጀመረ። ጣሊያን እየገሠገሠ ሲመጣ ግርማዊነታቸው ወደዉጭ አገር ገለል ብለው በውጭ ለመታገል ከመውጣታቸው በፊት የልጅ እያሱን ሁኔታ በተመለከተ ከቅርብ አማካሪወቻቸው ጋር ተነጋገሩ። ጣሊያን ሲገባ ህዝብን ለማሳመንና የፖለቲካ መጠቀምያ ለማድረግ ልጅ እያሱን "ንግሥና የሚገባው ንጉሥ ይሄዉና" ብሎ ንጉሥ አድርጎ ያነግሣል የሚል ፍራቻ በንጉሡና በአማካሪወቻቸው አደረ። ይህ ከሚሆን ብንገንድለውስ ብለው ተማከሩ። አፄ ኃይለሥላሴም "ንስኃውን እንዴት እንችለዋለን?" ሲሉ የነብስ አባታቸው አባ ሃና ጅማ "እንጾመዋለን" አሉዋቸው። ልጅ እያሱ በእስር ቤት ውስጥ ስንቅ ከሚያቀብላቸው ሠራተኛ ጋር እያወሩ የሚገድሉዋቸው ሰወች ከነሱም አንዱ የአባ ሀና ወንድም ኃይሌ ጅማ ሲመጡ ከሩቅ አዩና "ሊገድሉኝ እየመጡ ነው" ደህና ሰንብት ብለው ስንቅ አቀባያቸውን ተሰናበቱት። ከዚህ በሁዋላ የልጅ እያሱ አስከሬን የት እንደደረሰ አይታወቅም። [፩]  

ግርማዊ አፄ ኃይለሥላሴ በደርግ ትእዛዝ እስር ቤት እያሉ የደርግ አባሎች ምን እናድርጋቸው እያሉ መከሩ። እሳቸው በህይወት እያሉ የኢትዮጵያ ህዝብ እንዴት ሊገዛልን ይችላል ብለው አዲሶቹ የሀገር መሪ ወጣት የጦር መኮንኖች ንጉሡ በእስር ቤት እንዳሉ ለመግደል አቀዱ። አፄ ኃይለሥላሴ በእስር ቤት ዉስጥ ስንቅ ክሚያቀብላቸው ሠራተኛ ጋር ሲያወሩ ዛሬ ከእርስዎ ጋር እንደማላድር ተነግሮኛል አላቸው። አዝነው አለቀሱ። ወዲያውም የሚገድሉዋቸው መኮንኖች ሲመጡ ከሩቅ አዩና አወቁ። ከዚህ በሁዋላ አስከሬናቸው የት እንደደረሰ ሳይታወቅ ከደርግ መውደቅ በሁዋላ አጥንታቸው ተፈልጎ ተቀበረ ተባለ። የነብስ አባታቸው አባ ሃናም በሰው እጅ ነበር የጠፉት።  [፪]

ጣልያን ኢትዮጵያን በወረረ ጊዜ ግርማዊ አፄ ኃይለስላሴ ሊግ ኦፍ ኔሽንስ በተባለው የዓለም መንግሥታት ማህበር ስብሰባ "ጉልበተኛ ጉልበት የሌለውን በግፍ ሲያጠቃ ዝም ብላችሁ አትዩ፤ ነገ በናንተ ላይ ይደርሳልና" ብለው ጣልያን ከኢትዮጵያ ለቆ እንዲወጣ አቤቱታ አሰሙ። በጉባኤው የነበሩ የአውሮጳ ሃያላን መንግሥታት ተሳለቁባቸው።

ጣሊያን በኢትዮጵያ ዉሎ ሳያድር የጣሊያን ጉዋደኛ የሆነው ጀርመን የአውሮጳን ኃያላን በእግሩ እየረገጠ ማንበርከክ ጀመረ። አንድ ባንድ አውሮጳን ይወርም ጀመረ። በአፄ ኃይለሥላሴ አቤቱታ የተሳለቁት መንግሥታት በኢትዮጵያ ላይ የደረሰው በራሳቸው ላይ እየደረሰ በመምጣቱ ተደናገጡ። ከኢትዮጵያ ጎን በወታደርነት ተሰልፈው ጣልያንን እስኪአስወጡ ድረስ በኢትዮጵያ ላይ መሳለቃቸውን ረገሙ። የእግዚአብሔር ፍርድ እንዲህ ነው።

የጣልያኑ መሪ ቤኒቶ ሙሶሎኒ ኢትዮጵያን በወረሩበት ጊዜ ብዙ ግፎችን ሠርተው፣ አሰቃቂ ፍርዶችንም ፈርደው ነበረ። መነኮሳትን በየገዳሙ በጥይት ጨፍጭፈው ገድለዋል፤ በመርዝ ጋዝና በኬሚካል መሣሪያወች የኢትዮጵያን ህዝብ ጨፍጭፈዋል፤ አርበኞችን ከአውሮፕላን ከሰማይ ወደምድር ዘቅዝቀው ወርውረዋል። ቤኒቶ ሙሶሎኒ ከሠሩዋቸው ግፎች ዉስጥ አንዱ የእግዚአብሔርን ሰው አቡነ ጴጥሮስን አዲስ አበባ ላይ አስረው በተጣደፈ ችሎት የሞት ፍርድ አስፈርደው በጥይት አስደብድበው መግደላቸው ነው።

የጣሊያን ጦር ከኢትዮጵያ ከተባረረ በሁዋላ ትልቁ የጣሊያን ጠቅላይ ሚንስትር ቤኒቶ ሙሶሎኒ ከአገራቸው ሊወጡ ሲገሠግሱ የጣልያን ሶሻሊስቶች ይዘው በተጣደፈ ችሎት የሞት ፍርድ በየኑባቸው። በፍርዱ መሠረት ወዲያውኑ ቤኒቶ ሙሶሎኒ እንደ አቡነ ጴጥሮስ በጥይት ተደብድበው ተገደሉ። በሚላን ከተማ ሬሳቸው ተዘቅዝቆ ተሰቀለ። ከዚህ በኢትዮጵያ ላይ ከተፈፀመ የግፍ ወረራ ዘመን በሁዋላም ጣልያን ከአውሮጳ ጅራቶች ዉስጥ አንድዋ ሆና ቀረች።

የዛሬ አራት መቶ ሃምሳ አመት አካባቢ ኦስማኒየ ወይም ኦቶማን ኢምፓየር የተባለ ማእከሉ ቱርክ የሆነ በዘመኑ በዓለም ላይ አቻ የሌለው መንግሥት የውስጥ አመፀኛን በማስታጠቅ እንዲሁም ወታደሮቹን በአካል መሣሪያ አስይዞ ክርስትናን ከኢትዮጵያ ለማጥፋት ወደኢትዮጵያ መጣ። ትልቅ ጥፋትንም አደረሰ። አብያተክርስቲያናት ተቃጠሉ፣ መነኮሳት ታረዱ።

ለሁለት መቶ አምሳ አመታት በኃያልነት በማንም ሳይደፈር ከቆየ በሁዋላ የኦቶማን ኢምፓየር በኢትዮጵያ ላይ ጥፋትን አድርሶ ብዙ ሳይቆይ ለመጀመሪያ ጊዜ በላፔንቶ ጦርነት ተሽንፎ የሜዲትራንያንን ባህር መቆጣጠር አቃተው። ቀስ በቀስም እንደጉም በኖ ጠፋ። 

በተለይ የኦቶማን ኢምፓየር ቅሬታወች ነን የሚሉ መንግሥታት ባለፉት አምሳ አመታት ኢትዮጵያን በጦርነት አደህይተው፣ ወደቦችዋን ነጥቀው፣ የንግድ በርዋን ዘግተውና ህዝቦችዋን አናክሰው ህልውናዋን በማጥፋት ሥራ ላይ ተሰማርተው የሚፈልጉትን እስከሚችሉት አከናወኑ። እነዚህ መንግሥታት እንደአባቶቻቸው ኦቶማኖች የውስጥ አመፀኛን በማስታጠቅ ይህ ነው የማይባል ጥፋትን አድርሰዋል። አንድ ጊዜ መንፈሰ መራራ እንዲሆኑ በውጭ አገር ሰወች የተሰበኩ ኡስማን ሳልህ ሳቤ የተባሉ ሰዉየ ኢትዮጵያውያን ሱዳን አገር በሚገኝ የመዳህኒዓለም ቤተክርስትያን አብረው በመፀለይ ላይ እንዳሉ "ኤርትራውያን የተለያችሁ ናችሁ፤ ለናንተ እኔ ቤተክርስቲያን ለብቻችሁ እገዛላችሁዋለሁ" በማለት ከነዚህ መንግሥታት ባገኙት ገንዘብ ህንፃ ገዝተው የኤርትራውያን ሚካኤል ቤተክርስቲያን ብለው ሰየሙና ኢትዮጵያውያንን ከፋፈሉዋቸው። [፫] በተለይ የባዝ ፓርቲ ተብሎ የሚጠራው የኢራቅ ፓርቲ ቀይ ባህርን አረቦች ብቻ ይቆጣጠሩት ዘንድ ኤርትራ ከኢትዮጵያ እንድትገነጠልና ኢትዮጵያ ተቆራርጣ የንግድ በር እንድታጣ ለአረቦች ጥሪ አደረገ። የነዚህ መንግሥታትም ገንዘብ  እንደ ጥፋት ልኡክ ሆኖ ኢትዮጵያ ውስጥ ብዙ ደም ፈሰሰ።

እነሆ ለነዚህ መንግሥታት በጦርነት አደህይቶ፣ የንግድ በራቸውን ተቆጣጥሮ፣ ህዝባቸውን አናክሶ የሚፈልገውን የሚያከናውን ኃይለኛና የሚረግጥ የበላይ ሰጣቸው። አንዳቸው ብቻ አይደሉም - ሁሉም የሠሩትን ግፍ የሚያህል ፅዋ እየተጎነጩ ነው። ማን ያውቃል - እስላም ያልሆነው ኃይለኛው መንግሥት በመካከላቸው ባስቀመጠው ወኪል አማካኝነት ለአንዱ ዘር የተለየ መስጊድ ይገዛለት ይሆናል። 

አምባሳደሮችዋን ክንፍ ባላቸው መርከቦች በዓለም ላይ የምታሰማራው የአሜሪካ ልኡክ የሆኑ የመጣሁት አረቦች ኤርትራን ገንጥለው የራሳቸው ለማድረግ የሚያደርጉትን እንቅስቃሴ ለማጨናገፍ ነው እያሉ ከኤርትራው ጠቅላይ ገዥ ጋር በመሆን ከአቶ ኢሳያስ አፈወርቂ ጋር ለመገናኘት በቀጠሮ ወደቃኘው ሻለቃ አመሩ። ኤርትራን ከኢትዮጵያ ለመገንጠል ቢታገሉ እንደማይቃወሙ እንደሚረዱዋቸውም ከጠቅላይ ገዢው ዘወር አርገው ለአቶ ኢሳያስ አፈወርቂ ማበረታቻ ሰጡዋቸው። [፬] ከዚህ ጊዜ በሁዋላ ኤርትራ ከኢትዮጵያ ትገነጠል ዘንድ የኢትዮጵያን ሀገርነትና ኃይማኖትዋን የሚያጥላሉ ሚሽነሪወችን በማሰማራት፣ እንዲሁም ከሰላይ እስከ ደላይ፤ ከጋዜጠኛ እስከ ጎብኝ፣ ከስነፅሁፍ እርዳታ እስከገንዘብ ድረስ በማቅረብ ኢትዮጵያን አዳከሙ። ኢትዮጵያ ትከፋፈል ዘንድ፣ የንግድ በርም ታጣ ዘንድ ከአረቦች ጋር አላማቸው አንድ ሆነ። ሶስት መቶ ስልሳ አንድ ወደቦች ያላት ታላቁዋ አገር አሜሪካ አንድ ብቻ ያላትን የተራበችዉን፣ የደሃዋን አገር በር ለመንሳት አምባሳደርዋን ላከች። ፈፀመችም። ኢትዮጵያን ለመክፈል፣ የንግድ በርዋንም ለመዝጋት በሌላ አገር ላይ ተደርጎ የማይታወቅ ኢትዮጵያን ያለ በር ማስቀረት የሚያስችል የመንግሥታት ማህበር ድንጋጌ በልዩ ዘዴ ተነደፈ። ተጨበጨበ። ተፈጸመም።

ለምልክት እንዲሆን በኢትዮጵያ አዲስ አመት እለተ ቀን፣ ኢትዮጵያን ለማጎሳቆል አላማ  ከተወዳጀቻቸው ወገኖች የተሰነዘረ ጥቃት በአሜሪካ ላይ ደረሰ። በስማይም በባህርም ብዙ ሺ መንገድ ያላት አገር በሮችዋ እንደ አንድ በር ሆኑና ሰማዩም ባህሩም የስጋት ሆነባት። በአንድ እለተ ቀን የተፈፀመ ጥቃት አጥቂወቹም ተጠቂወቹም በማያውቁት መንገድ የእያንዳንዱን ሰው ኑሮ ዳሰሰ፤ አቃወሰ። የተጠቂዋ ንግድ በጥቃቱ ተጎዳ፣ ደስታዋም አነሰ። በሰማይዎችዋና በባህሮችዋ ያለባትን ስጋት ለመሸፈን በየቀኑ ቁጥር ስፍር የሌለው ኃብትዋን በመድፋት ላይ ትገኛለች።  

ኢትዮጵያን የበደለ ይበደላል። እነ ታላቅዋ ብሪታንያ፣ እነ ዩ ኤስ ኤስ አር፣ እነ ፖርቱጋል ወዘተረፈ የሚመጣጠነውን ዋጋቸውን አግኝተዋል። አንድ የእግዚአብሔር ሰው አንድ ጊዜ "ኢትዮጵያን አይነኩ፤ ቢነኩ ያድርዋል ሲታወኩ" ብለው የተናገሩት ያለምክንያት አይደለም። ትናንትናም ዛሬም ነገም አይቀየርም - የነካት ይነካል። በኢትዮጵያውያን የተሠራ ኃጢአትም ወዲያዉኑ ፍርድ ያገኛል። አሁን እየተጎነጨን ያለነው ፅዋ ለሠራነው ኃጢአት የሚመጣጠነውን ነው። ፍቅር የለን፤ እንዴት አንድ እንሁን? ምቀኝነት ምግባራችን፤ እንዴት እንበልጽግ? የውጭ የምናይ፤ እንዴት የራሳችን ይክበር? አጉል ምግባራችን ያጠፋት መልካምዋ ኢትዮጵያ በእግዚአብሔር እጅ ተይዛለች። የምትገኘው በሱ ነውና እሱን እንፈልገው።
እንድናገኘውም ከፍቅር ማህበር እንጥራው
 
እገሌ እንዲህ አድርጎ ስለበደለን እንዲህ ሆነናል እያልን ከዘመን ዘመን የተለያዩ ሰወችን እያማረርን፣ ተጠያቂወቹ እነሱ ናቸው እያልን እንኑር ወይ? ውድቀታችን ያመካኘንባቸው ሰወች ከየት መጡ? የውድቀት ተጠያቂወች የሚቀያየሩ ከሆነስ ውድቀት እንዴት ሊቆም ይችላል? ጨቁዋኞችስ ለምን መጡ? ሁከተኞች ለምን መጡ? አገር መገንጠል የሚፈልጉ ለምን መጡ? ያልተሰጣቸውን የሚነጥቁ ለምን መጡ? ዘጠና ስምንት ከመቶ በላይ የሚሆነው ኢትዮጵያዊ በእግዚአብሔር ያምናል። ከግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለስላሴ የንግሥና ዘመን ማለፍ በሁዋላ የተሰየሙት እግዚአብሔር የለም የሚሉ ሁለት መንግሥቶች በእግዚአብሔር ከሚያምን ህዝበ-ውቅያኖስ መካከል ወጥተው እንዴት መሪ ሊሆኑ ቻሉ? ልብ ላደረገው መልሱ እራሱ ከጥያቄው ዉስጥ ይገኛል።      

እግዚአብሔር ጭቆና አይወድም። ወንድሙን እና እህቱን የሚወድ ወንድሙንና እህቱን አይጨቁንም። ጉዋደኛዉን የሚወድ ጉዋደኛውን አያጭበረብርም። የተጨቆነ ወንድም ለመውደድ ይቸገራል። የተታለለ ባልንጀራ ግዋደኝነትን አይሻም። ክፉ አመልን እንደያዝን የምንገነባው ይፈርሳል። የምናደርገው ነገር ሁሉ ዉኃ ቢወግጡት ይሆናል። ባለዘመን ቢገነባ የሚከተለው ያፈርሰዋል። ዘንድሮ የተወደሰው ከርሞ ይረክሳል። ኢትዮጵያን ከክፉ ቀን ለማዳን የሚያስፈልገን አንድ ነገር ብቻ ነው። እሱም ፍቅር ነው። ፍቅር ካለ ጭቆና የለም። ፍቅር ካለ ማጭበርበር የለም። ፍቅር ካለ አመፅ የለም። በፍቅር የተገነባ በበቀል አይፈርስም። ፍቅር ካለ እንገነጣጠል የሚል ዛቻ የለም። ፍቅር ካለ ስብሰባውም ሆነ ስነፅሁፉ ስለ መገንባት ጉዳይ እንጂ ስለ ጦርነት ጉዳይ አይሆንም። እግዚአብሔር ፍቅር ነውና ስንፋቀር እግዚአብሔርን እናገኘዋለን። እግዚአብሔርም መዳብ መስሎን የነበረው እኛነታችን አይናችን ገልጦ ወርቅ መሆኑን ያሳየናል። የምንበላውና የምንጠጣው የሌለ የመሰለው ልቦናችንን አንቅቶ በኤደን ገነት ውስጥ እንደምንኖር ይስመለክተናል። የውጩ የሚያስጎመጅ የመሰለው አዕምሮአችንን ብሩህ አድርጎ በእጃችን ያለው እንቁ መሆኑን ያሳየናል። ስለዚህ የፍቅርን ሥራ እንጀምር።

**********************************************************************************
፩ ይህን ያሪክ ያጫወቱኝ በጊዜው ጉዳዩን የሚያውቁ አረጋዊ ናቸው።
፪ ይህን ያሪክ ያጫወቱኝ በጊዜው ጉዳዩን የሚያውቁ አረጋዊ ናቸው።
፫ ይህን ታሪክ ያጫወቱኝ በሱዳን አገር በስደት የኖሩና ጉዳዪን በአይናቸው ያዩ የባህረ ነጋሽ ተወላጅ ናቸው። 
፬ ሲ አይ ኤ በአፍሪካ፣ በአለሜ እሸቴ፣ ፲፱፻፺፬ ዓ.ም.

****************************************
 ምንጭ:--http://www.oftsion.org/SeektheLord.html

“የህይወት ጥቅሙ ምንድነው?”

 መቼም የማይሞት ሰው የለም
******************************

“በመልካም ስራው ሲታወስ ይኖራል” እንዳትሉ። ከሞተ በኋላ ታሪኩ ቢነገር መቼ ይሰማና!
“ስምና ስራ ከመቃብር በላይ ነው” እንዳትሉ። ከሞተ በኋላ አድናቆትና ክብር ምን ሊረባው!
“ድንቅ ስኬታቸው ዘላለማዊ ናቸው” አትበሉ። ከሞት በኋላ ምንም ነገር ትርጉም የለውም!
ጀግኖች፤ በህይወት እያሉ ነው በመልካም ስራና በድንቅ ስኬት ዘላለማዊነትን ያጣጣሙት!
የድፍረት አባባል እንዳይመስላችሁ። ርዕሱ ላይ፤ “የማይሞት ሰው የለም” ብዬ ስፅፍ፤ ... ዝግንን ብሎኛል። የተለመደ አባባል ስለሆነ፤ ብዙውን ጊዜ ያን ያህልም ስሜት ላይሰጣችሁ ይችላል። “ህይወት አላፊ ነው” ይባላል - እንደ ዋዛ። አንዳንዴ ግን፤ “የማይሞት ሰው የለም” ብላችሁ ስትናገሩ ወይም ስትሰሙ፤ ...የምር ውስጣችሁ ድረስ ጠልቆ ይሰማችኋል - ሰውነትን የሚያስፍቅ ሸካራ ስሜት። ሳይበርዳችሁ... ቆዳችሁ ተሸማቅቆ ፀጉራችሁ ይቆማል።
እስከ ዛሬ ያካበታችሁት እውቀትና ችሎታ፤ የሰራችሁትና ያፈራችሁት ነገር ሁሉ፤ ለወደፊት ያሰባችሁትና ያቀዳችሁት ሁሉ፤ የምታፈቅሩትና የምትሳሱለት፤ የሚያስደስታችሁና የሚያጓጓችሁ ነገር ሁሉ... ድንገት ትርጉም ሲያጣ ይታያችሁ። የምን ማየት! ከሞት በኋላ አንድ አፍታ ለማየትም እንኳ እድል የለም። ዛሬ አለሁ፤ ነገ የለሁም። ... አለቀ፤ እስከ መቼውም የለሁም። ለሞተ ሰው፤ “ከዚያ በኋላ....” የሚባል ነገር የለም። “ከዚያ በፊት... ከዚያ በኋላ” ብሎ ሊያስብና ሊናገር አይችልም። ጨርሶ የለማ። በቃ፤  ብን ብሎ ድንገት ጥፍት... ባዶ... ። ታዲያ የህይወት ትርጉም ምንድነው?
ሰው ቢሞትም፤ “ከዚያ በኋላ...” የሚባል ነገር ይኖረዋል ብሎ መሟገት እንደሚቻል አውቃለሁ። አሁን ግን፤ ጠያቂውና ተጠያቂው እኔ ራሴ ስለሆንኩ፤ መከራከሪያና ማሳመኛ አይሆነኝም። ከሞት በኋላ ህይወት እንዳለ ማየትና ማረጋገጥ ሳይቻል፤ ከራስ ጋር ተከራክሮ ማሳመን ከባድ ነው። ለነገሩ፤ ከዚህኛው ዓለም ባሻገር፤ ሌላ “የወዲያኛው ዓለም” ቢኖር እንኳ፤ እንዴት ማፅናኛ ሊሆን እንደሚችል አይገባኝም።
የሞተ ሰው፤ ወደ ወዲያኛው አለም ይሄዳል እንበል። ግን፤ ይሄኛውን አለም ተመልሶ ማየት አይችልም። የሚወደውን ስራ ተመልሶ ሊሰራ አይችልም። የሚወደውን ምግብ መቅመስ፣ ከሚያፈቅራቸው ሰዎች አጠገብ መሆንና ማነጋገር አይችልም። ምንም ማድረግ አይችልም። ሰዎችም ምንም አያደርጉለትም። ቢበዛ ቢበዛ፤ የትዝታቸው ቅንጣት ውስጥ ታሪኩን ያስታውሱ ይሆናል። እሱ ግን  ...የለም፤ ከእንግዲህ አይኖርም። ታዲያ፤ በህይወት ዘመኑ ውስጥ፤ እንዲያ ብዙ በሃሳብ መብሰልሰሉና ለነገ ማቀዱ፤ ማውጣትና ማውረዱ፣ ለስራ መድከሙና ለውጤት መጣጣሩ ምን ትርጉም አለው? የህይወት ፋይዳስ ምንድነው?
ዘመናዊ ማፅናኛዎቻችንን ሳላስባቸው የቀረሁ እንዳይመስላችሁ። “ሰው ይሞታል፤ ስራው ግን ህያው ነው” እንደሚባል አውቃለሁ። “ስምና ስራ ከመቃብር በላይ ናቸው” ሲባልም እሰማለሁ። “በአካል ብትለየንም በመንፈስ ከኛ ጋር ነህ” ይባላል። “ሰው በመልካም ስራውና በድንቅ ስኬቱ ህያው ይሆናል” ... ይህንንም ሰምቻለሁ፤ እንዲያውም እኔ ራሴ ብዙ ጊዜ የምለው ነገር ነው። “በሰራኸው መልካም ስራ ዘላለም ህያው ትሆናለህ፤ ዘላለም በክብር ታሪክህ ሲታወስ ይኖራል” ይባላል። ...አባባሎቹ የሆነ ደስ የሚል ነገር አላቸው። እኔም አባባሎቹን እወዳቸዋለሁ።
ነገር ግን፤ እንዲህ አይነት ሺህ እና ሺህ አባባሎች ተሰብስበው ቢደመሩ፤ ለሟች ነፍስ ሊዘሩና ህይወትን ሊመልሱ አይችሉም። በህይወት ያሉ ሰዎች፤ እነዚህን አባባሎች እንደመፅናኛ ሊጠቀሙባቸው ይችላሉ። ምናልባትም መንፈሳቸው ይነቃቃ ይሆናል - በህይወት ካሉና አባባሎቹን ከሰሙ። በህይወት ለሌሉና መስማት ለማይችሉ ግን፤ እነዚያ እልፍ አባባሎች በሙሉ ትርጉም የላቸውም። ከሞተ በኋላ፤ “ታሪኬ እንዴት ይወራ ይሆን?” ብሎ የሚያስብ ሰው የለም። አላሰበም ወይም አያስብም ማለቴ አይደለም። ለማሰብ፤ በቅድሚያ በህይወት መኖር አለበት። ከሞት በኋላ ግን፤ ... በቃ ...የለም።
ከመኖር ወደ አለመኖር መሻገር... ከዚያ በኋላ ምንም የለም። ባዶ ነው። ምን ያህል ሰው በስራዬ ያደንቀኝ ይሆን? ስንቱስ በሞቴ ያዝንልኛል? የቀብሬ አከባበር እንዴት ይሆን? የጀመርኩትና የገነባሁት ቢፈርስስ? ያቀድኩትና የተለምኩትስ ይሳካ ይሆን? ታሪኬ ዘላለም ይቆያል ወይስ እረሳ ይሆን?... ከሞት በኋላ እነዚህ ሁሉ ጥያቄዎች ፋይዳ የላቸውም። ለማን ሊፈይዱ! ለማን ሊጠቅሙ! ከሌለህ የለህም። ሁሉም ነገር አብቅቷል። ታዲያ የህይወት ፋይዳው ምንድነው? የመንግስቱ ለማ ግጥም አይመጣባችሁም? (ስንኞቹ ውስጥ “ት” ጠበቅ ተደርጋ ስትነበብ ነው ቤት የሚመታው)





ለምንድነው አልኩኝ
በምን ምክንያት
ህፃን መወለዱ
አርጅቶ ሊሞት...






በጨላለመ ሃሳብና ስሜት የጀመርኩት ፅሁፍ፤ ድንገት የመጣ እንዳልሆነ መገመታችሁ አይቀርም። ከጠ/ሚ መለስ ዜናዊ ዜና እረፍት ጋር ብዙ ሰዎች ብዙ ነገር አስበዋል። ስለ አገሪቱ የወደፊት እጣ ፈንታ አውጠንጥነዋል። ፖለቲካውና የስልጣን ሽግግሩ አሳስቧቸዋል። የኢኮኖሚና የኑሮ ሁኔታ እንዴት ይቀጥል ይሆን ብለው አሰላስለዋል ... በአመዛኙም ስጋትና ጥርጣሬ በተሞላበት መንፈስ። ለየት የሚል መንፈስ የሚጫጫናቸው ግን፤ ስለ ህይወትና ስለ ሞት ሲያስቡ ነው - “የህይወት ፋይዳ ምንድነው?” ከሚል ጥያቄ ጋር ተጭኖ የሚመጣ የጨላለመ መንፈስ።
በእርግጥ፤ ይሄ ጨለማ መንፈስ፤ ከሃዘን ስሜት ጋር ስለሚደባለቅና ስለሚቀየጥ፤ ሁለቱን በግልፅ ለይቶ ለማውጣትና ለማየት ያስቸግራል። ግን፤ ጨለማው መንፈስ ከሃዘን ስሜት ይለያል፤ ይብሳል። የሃዘን ስሜት፤ “አንዳች ነገር ማጣት”ን የሚያመለክት ነው - ተፈጥሯዊና ተገቢ የሆነ ስሜት። “የህይወት ፋይዳ ምንድነው? ምን ትርጉም አለው?” ከሚለው ጥያቄ ጋር አብሮ የሚከሰተው ጨለማ መንፈስ ግን፤ “ራስን ከማጣት” ስሜት ጋር የተያያዘ ነው - ከተሳሳተ አስተሳሰብ የሚመነጭና ተገቢ ያልሆነ ጨለማ መንፈስ።
ማጣትና ማዘን - ከትንሽ እስከ ትልቅ
አቤት የሃዘን አይነትና መጠን አበዛዙ! ለነገሩ የደስታ አይነትና መጠንም እጅግ ብዙ ነው። አይነታቸው ይብዛ እንጂ ከሁለት ምንጮች የሚፈልቁ ናቸው። ደስታ የሚመነጨው በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ፤ ከ”ስኬት” ነው። “ማጣት” ደግሞ ሃዘንን ያስከትላል። ደስታና ሃዘን የእለት ተእለት ህይወታችን ቢሆኑም፤ ከስኬትና ከእጦት የሚመነጩ መሆናቸው በግልፅ ይታየናል ማለት አይደለም። ባይታየን ደግሞ አይገርምም። የብዙዎቻችን ህይወት በአርቴፊሻል “ደስታ እና ሃዘን” ሲበረዝ ውሎ የሚያድር ነውና። እንዴት በሉ።

የውሸት “ደስታ”ን እያውለበለብን መፈንጠዝ ያምረናል - ያልደረስንበትን ስኬት እንዳገኘነው እየቆጠርን። ወይም አላስፈላጊ “ሃዘን” ተከናንበን ትካዜ ውስጥ እንነከራለን - አላግባብ በጥፋተኝነት ስሜት ራሳችንን እየወቀስን። በመጠጥ ሞቅታ የሚገኘው ደስታ ከየትም የሚመጣ አይደለም። ሰዎች ሞቅ ሲላቸው ሃብታም ወይም ጀግና፤ አዋቂ ወይም ትልቅ የሆኑ ሲመስላቸውኮ፡፡ “ስኬታማ ነኝ” ብለው አሰቡ ማለት ነው። “ስኬት” ደግሞ ደስታን ይፈጥራል - ጊዜያዊ አርቴፊሻል ደስታ። የአስመሳዮች ደስታም ተመሳሳይ ነው። ባልሰሩትና ባልፈጠሩት ስኬት፤ በአስመሳይነታቸው የሰው አድናቆትና ሙገሳ የሚጎርፍላቸው ሰዎች በደስታ የሚሆኑትን ሊያጡ ይችላሉ። በሙገሳ ሲሰክሩ፤ ስኬታማ የሆኑ ይመስላቸውና፤ ደስታ ይሰማቸዋል።
ችግሩ፤ ማታ ሰው ሁሉ ተኝቶ ሙገሳው ሲቋረጥ ወይም በማግስቱ ሞቅታው ሲበርድ፤ “ስኬታማ ነኝ” የሚለው የስካር ሃሳብም አብሮ ይጠፋል፤ “የውሸት ደስታውም” እንዲሁ። በእውነተኛ ስኬት ላይ የተመሰረተ እውነተኛ ደስታ ግን፤ በአንድ ሌሊት እንቅልፍና በአድናቂ እጦት በኖ አይጠፋም። የሆነ ሆኖ፤ ማንኛውም የደስታ አይነት፤ የውሸትም ይሁን የእውነት ደስታ፤ ዞሮ ዞሮ ከ”ስኬት” ጋር የተቆራኘ ነው (የእውነትና የውሸት ስኬት)።
የሃዘን ምንጭም፤ (ሃዘኑ ተገቢም ይሁን አላስፈላጊ)፤ ከ”ማጣት” ጋር የተያያዘ ነው - (የእውነትና የውሸት እጦት)። ያስቀመጥነውን ውድ እቃ ፈልገን ካላገኘነው፤ የጠፋና ያጣነው እየመሰለን እናዝናለን። ግን ጊዜያዊ ስለሆነ ብዙም አይጎዳም። መጥፎነቱ እጅግ ጎጂ የሆኑ አላስፈላጊ ሃዘኖችም አሉ። ከፍተኛ የፈተና ውጤት በማስመዝገቡ እየተደሰተ፤ ነገር ግን ከጓደኞቹ በመብለጡ የጥፋተኝነት ስሜት የሚፈጠርበት ተማሪ አለ - ጓደኝነታቸውን የሚያጣ እየመሰለው። በቢዝነስ ስራው ስኬታማ እየሆነ ደስታ ቢያገኝም፤ ገዳም የመግባት ፍላጎት በማጣቱ ራሱን እንደጥፋተኛ የሚቆጥርም ጥቂት አይደለም። እነዚህ አላስፈላጊ ሃዘኖች ናቸው።
ከ”ማጣት” (ከመጎዳት) የሚመነጩ እውነተኛ ሃዘኖችም ቢሆኑ አስፈላጊ ናቸው ማለቴ አይደለም። ግን ተፈጥሯዊ ናቸው። አንድን ነገር መውደድና ማክበር ማለት፤ ያስደስትሃል ማለት ነው፤ ስታጣው ደግሞ ያሳዝንሃል... የግድ ነው። ሁሉም ሃዘኖች ከማጣት የሚመነጩ ቢሆንም፤ ስፋትና ክብደታቸው ግን... የትና የት! የሚያኮማትር፣ እየቆየ የሚያስደነግጥና ግራ የሚያጋባ ሃዘን እንዳለ ሁሉ፤ ከአፍታ ብልጭታ የማያልፍ ሃዘንም ይኖራል።

ሃዘን የሚለውን ቃል በየጊዜው ምን ያህል እንደምንጠቀምበት አስቡት። ልብሷን ጭቃ ሲነካት አሳዘነችኝ ይላል። አዳልጦት ስለወደቀ አሳዘነኝ ትላለች። ካልተጎዳ ተመልሶ ይነሳል። ጭቃ የነካው ልብስም፤ ታጥቦ ይነፃል። ያጣነውን ነገር ቶሎ መልሰን የምናገኘው ከሆነ፤ ለሃዘን ፊት አንሰጠውም - ከወደቅንበት እንነሳለን፤ የጨቀየውን እናጥባለን። ግብዣ ጠርተውት ሳይመጣ በመቅረቱ፤ ብርጭቆው ስለተሰበረ፣ የልጅነቱ ፎቶ ስለተቃጠለ፣ የቤቱ ጣሪያ ስለተገነጠለ፣ በፈተና የማለፊያ ውጤት ስላጣ፣ የአሜሪካ ቪዛ ስለተከለከለ፣ ገንዘብ ከቦርሳው ስለተሰረቀ.... ያዝናል። ከፍቅረኛው ጋር ስለተጣላ፣ የሚወደው ሰው ስለደኸየ፣ የራሱ ንብረት በጎርፍ ስለተወሰደ፣ ጓደኛው በመኪና ስለተገጨ፣ የራሱ አካል በአደጋ ስለጎደለ፣ የሚያደንቀው ሰው ስለታመመ ... በጣም ያዝናል። የሚያከብረው ሰው ስለሞተ... እጅግ አዝኖ ያለቅሳል።
ደረጃቸው የሰማይና የምድር ያህል ቢራራቅም፤ ሁሉም አይነት ሃዘኖች፤ ኮምጣጣውም ሆነ መራራው ሃዘን ... ከ”ማጣት” የሚመነጩ ናቸው። አንዳንዶቹ ሃዘኖች እጅግ መራራ የማይሆኑት፤ ያጣነውን ነገር መልሰን ልናገኘው ስለምንችል ነው። ጊዜና ጥረት ያስፈልገው ይሆናል እንጂ፤ በተቃጠለብን ንብረት ምትክ ሌላ ንብረት የማፍራት እድል ይኖረናል። የለመድነው ወይም የምንወደው፤ የምናውቀው ወይም የምናከብረው ሰው ሲሞት ግን... መልሰን ልናገኘው አንችልም። ትዝታው ብቻ ነው የሚቀረን። የድሮውን ከማስታወስ በስተቀር፤ የድሮው ህይወት ተመልሶ እውን አይሆንም።
የሞት ሃዘን እጅግ መራራ ነው። በተለይ ከእለት ተእለት ህይወታችን ጋር የዘወትር ወይም የቅርብ ትስስር ያለው ሰው ሲሞት፤ ከሃዘኑ በተጨማሪ እየቆየ ድንግጥ ድንግጥ ያሰኛል። ቤት ስንገባና ስንወጣ፤ ድንገት እንድንገጣጠምና ድምፁን እንድንሰማ እንጠብቃለን። በየእለቱ የለመድነውና እንደ ቋሚ የተፈጥሮ ኡደት የምንቆጥረው ነገር ነዋ። ከብዙ ሃሳቦቻችንና ተግባራችን ጋር የተሳሰረ ነዋ። እናም፤ እንደለመድነው እንጠብቃለን።
ግን፤ ከእንግዲህ በአካል አናየውም፤ ድምፁንም አንሰማውም። ከእንግዲህ ጨርሶ የማይሆንና የማይቻል ነገር መሆኑ ብልጭ ሲልብን ድንግጥ እንላለን። ጭራሽ፤ በመጀመሪያዎቹ ቀናት ሃዘናችን እየበረታ ይሄዳል - በሞት ያጣነውን ሰው መልሰን ልናገኘው እንደማንችል በደንብ እየገባን ይመጣል። ከዘወትር የእለት ተእለት ልምዳችን ጋር የማይገጥም እውነታ ተፈጥሯል። ከዚህ እውነታ ጋር ስንፋጠጥ ድንግጥ እንላለን።
ጠ/ሚ መለስ ዜናዊ በቲቪ ሲናገሩ ማየት ምን ያህል ከህይወታችን ጋር እንደተሳሰረ አስቡት። አሁንም ድንገት ቲቪ ከፍተን ስንመለከት... የጠ/ሚ መለስ ንግግር ስናይ... የምናውቀውና የለመድነው ነገር ነው። ... ግን ወዲያው ድንግጥ እንላለን። ለካ፤ ከእንግዲህ በጭራሽ ፓርላማ ውስጥ ንግግር ሲያደርጉ በቲቪ መከታተል አንችልም፤ ጨርሶ ሊሆን የማይችል ነገር ነው። ... ለወትሮው እንደ ነባር ስንቆጥረው የነበረ ነገር፤ አሁን ፈፅሞ የማይቻልና የማይሆን ነገር ... ከእንደዚህ አይነት ነገር ጋር ስንፋጠጥ ነው ድንጋጤ የተቀላቀለው ሃዘን የሚሰማን - ከ”ማጣት” የመነጨ ሃዘን።

“የህይወት ትርጉም - ዘላለማዊነትን ማጣጣም”
ሰውን በሞት ከማጣት የሚመነጭ የሃዘን ስሜት፤ ከሌሎቹ የሃዘን ስሜቶች ለየት ይላል። ብዙውን ጊዜ ሌላ ተጨማሪ ስሜት ይጭንብናል። “የማይሞት ሰው የለም” ከሚለው ሃሳብ ጋር፤ “ታድያ የህይወት ፋይዳው ምንድነው?” የሚል ጥያቄና ጨለማ መንፈስ ይፈታተነናል። ህይወት ትርጉም የሚያገኘው፤ ሞት የሚባል ነገር ከሌለ ነው ብለን ስለምናስብ ይሆን? ህይወትን ስለማናጣጥማትም ሊሆን ይችላል። እናም፤ ከሞት ባሻገር ከሞት ወዲያ ማዶ እንቃኛለን - የህይወትን ትርጉም ለማግኘት።
አንዳንዴ፤ በሌላ የወዲያኛው አለም፤ ሌላ የወዲያኛው ህይወት እንዳለ በማመን፤ ከጨለማው መንፈስ ለመገላገል እንጥራለን። ሌላ ጊዜ ደግሞ፤ “የሞተው ሰው፤ በስራው ህያውና ዘላለማዊ ሆኗል” በማለት ራሳችንን እናፅናናለን - የህይወት ትርጉም ታሪካዊ ስራ አከናውኖ ማለፍ እንደሆነ በማመን። ከሞት በኋላ ሌላ የወዲያኛው ህይወት ባይኖር እንኳ፤ “የታሪክ ህይወት” የሚባል ምናባዊ የህልውና አለም እንፈጥራለን - “በታሪክ ሲታወስ የሚኖር ሰው” እንላለን።
እንግዲህ፤ መሞት ማለት ዘላለማዊ ፍፃሜ መሆኑን ላለማመን ነው መፍጨርጨራችን። በዚህም፤ ጨለማውን መንፈስ አሽቀንጥረን የምንጥል ይመስለናል። መሞት ግን፤ ዘላለማዊ ፍፃሜ ነው (ቢያንስ ቢያንስ በዚህ በምናውቀው ዓለም ውስጥ)። እንዲያም ሆኖ፤ ከጨለማ መንፈስ ለማምለጥ ዘዴ መፈለጋችን አይቀርም። ሟቹ፤ ሃዘናችንንና አክብሮታችንን በማየት እንደሚደሰት አድርገን እናስባለን - ከሞተ በኋላም ህያው እንደሚሆን እያስመሰልን።
“ያሰብከውን እናሳካለን፤ ራዕይህን እውን እናደርጋለን” በማለት ቃል እንገባለታለን። ነገር ግን፤ ቃላችንን መስማት አይችልም። ሲያስብ የነበረውን ብናሳካና ባናሳካ፤ ይዞት የነበረውን ራዕይ ብንፈፅምና ባንፈፅም ለኛ ለራሳችን ካልሆነ በቀር፤ ለሟቹ ትርጉም አይኖረውም። ሊያስደስተውም ሆነ ሊያሳዝነው አይችልም። በህይወት የለማ።
እናም፤ ሃሳብና እቅዳችን፤ ጥረትና ተግባራችን ሁሉ የታለመው፤ ሟቹን ለማስደሰት ከሆነ፤ በከንቱ ደከምን - ቅንጣት አናስደስተውም። ሃዘንና ድንጋጤያችንን፤ ክብርና አድናቆታችንን መግለፃችን ለሟቹ ይጠቅመዋል ብለን ካመንን፤ በከንቱ ባከንን - ቅንጣት አንጠቅመውም። “ዘላለማዊ ነህ፤ ህያው ነህ፤ መንፈስህ ከኛው ጋር ነው” የምንለው፤ ለሟቹ በማሰብ ከሆነ፤ በከንቱ ለፋን - ቅንጣት እድሜ አንጨምርለትም።
ሃዘኑም ሆነ አክብሮቱ፤ ድንጋጤውም ሆነ አድናቆቱ፤ ትርጉም የሚኖረው፤ በህይወት ላሉ ሰዎች ነው። መልካም ስራንና ሰሪዎችን ማክበር፤ ስኬትንና ስኬታማዎችን ማድነቅ፤ እነዚህ ጀግኖች በህልውና ሲገኙ መደሰትና በህልፈታቸው ሲታጡ ማዘን... ይሄው ነው ቁምነገሩ። መልካም ስራንና ስኬታማዎችን ማድነቅ ለራስ ነው - ለራስ የስብእና ጤንነት።
ሟቾቹማ፤ ከማንም ምንም አይፈልጉም። ለሟቾች፤ ምንም ቢሆን ምንም ትርጉም የለውም - በህልውና የሉምና። “ህያው ናችሁ፤ ዘላለማዊ ናችሁ” ብንል ለነሱ ዋጋ የለውም። እኛ ስለተናገርን ወይም ስላልተናገርን አይደለም። አለማወቃችን እንጂ፤ ጀግኖችና የስኬት ሰዎች ዘላለማዊ ህልውናን የሚያጣጥሙት፤ ከሞት በኋላ ሳይሆን፤ በህይወት ዘመናቸው ውስጥ ነው - በእያንዳንዷ መልካም ስራና ድንቅ ስኬት ውስጥ ነው ዘላለማዊ ህልውናን የሚያጣጥሙት።
ጀግኖች፤ በአስተዋይነት ያመነጩት ሃሳባቸው ትክክለኛ መሆኑን ሲያውቁ፤ ትክክለኛነቱ መቼም የማይሻር ዘላለማዊ እንደሆነ ያውቃሉ፤ በዚህም ዘላለማዊነትን ያጣጥማሉ። አርስቶትል የሎጂክ መርሆችን ሲቀምር፤ የሃሳቦቹ ትክክለኛነት ዘላለማዊ መሆናቸውን በማወቅ ነው። አንድ ነገር፤ በአንድ ጊዜ ድንጋይ መሆንና ድንጋይ አለመሆን አይችልም።
ኮፐርኒከስና ጋሊልዮ፤ መሬት በፀሃይ ዙሪያ ትሽከረከራለች ሲሉ፤ ሃሳባቸው ትክክለኛነት ዘላለማዊ እንደሆነ ያውቃሉ። ያኔ ነው፤ ዘላለማዊ ህልውናን የሚያጣጥሙት። በህይወት ዘመናቸው ስለሚያጣጥሙትም፤ ከሞት በኋላ አሻግረው ሌላ የህይወት ትርጉም ለማግኘት በከንቱ መድከም አያስፈልጋቸውም። በእውነታ ላይ የተመሰረተች እያንዳንዷ እውቀት፤ በመረጃ ላይ የተመሰረተች እያንዳንዷ ሃሳብ፤ የዘላለማዊ ህልውና መስኮት ነች። በጀግኖች አርአያነት መንፈሳችንን እያነቃቃን፤ እውነታ ታማኝ በመሆንና በቅንነት በማሰብ ነው፤ በህይወት ዘመናችን ዘላለማዊ ህልውናን የምናጣጥመው።
ጀግኖች፤ በችግርና በእንቅፋት ብዛት ሳይበገሩ፤ ለአላማቸውና ለሃሳባቸው በፅናት በመቆም በድንቅ ብቃት መልካም ተግባር ይፈፅማሉ። ብቃትና ተግባራቸውም፤ ድንቅና ጠቃሚ መሆኑን ብቻ ሳይሆን፤ መቼም ለዘላለም እንደማይሻር ይገባቸዋል፤ እናም ዘላለማዊነትን ያጣጥማሉ። ተፈጥሮን መመርመርና ለእውቀት መትጋት፤ መማርና ማስተማር፤ ምርጥ የእህል ዘር መፍጠርና ወንዝ መገደብ፤ ማሽንና ቴሌፎን፣ ክትባትና መድሃኒት ለመስራት ሙከራና ጥናት ማካሄድ... እነዚህ ብቃትና ተግባሮቻቸው እጅግ ድንቅና ጠቃሚ መሆናቸው፤ መቼም ቢሆን እስከዘላለሙም አይሻርም። የኛ ማወቅና አለማወቅ፤ የኛ ማጨብጨብና አለማጨብጨብ አይደለም። ብናውቅና ብናጨበጭብ ጥሩ ነው። ግን፤ ባናውቅና ባናጨበጭብም እንኳ፤ የጀግኖቹ ተግባር ጠቃሚ ሆኑን ልንሽረው አንችልም። እውነት ነውና። ዘላለማዊ ነው። ይህንን የሚያውቁ ጀግኖች፤ በህይወት ዘመናቸው ውስጥ በእያንዳንዱ ድንቅ ብቃትና መልካም ተግባር ዘላለማዊ የህይወት ደስታን ያጣጥማሉ።
ጀግኖች፤ ስኬታቸውና ራዕያቸው፤ እውነተኛና ብሩህ መሆኑን ሲያውቁ፤ እውነተኛነቱና ብሩህነቱ በየትኛውም ጊዜ እንደማይሰረዝ እንደማይደለዝ ይገነዘቡታል፤ እናም በዚያው ልክ ዘላለማዊ ህልውናንን ያጣጥማሉ። ከሊዊ ፓስተር ፔኒሲሊን፤ ከአርኪሜደስ የፈሳሽ ነገሮች ህግ፤ ከአንስታይን የኢነርጂ ቀመር ጀምሮ፤ እያንዳንዷ የእውቀት ግኝት፤ የቴክኖሎጂ ፈጠራና የምርት ውጤት፤ በብሩህ ራዕይ የታጀበች እውነተኛ ስኬት መሆኗ... ለዘላለም እውነት ነው።  መሞት ይህንን አይሰርዘውም።
የህይወት ትርጉምም ይሄው ነው - እንዲህ መቼም ዘላለምም ሊሰረዝና ሊሻር በማይችል፤ ከአስተዋይነት በመነጨ ትክክለኛ ሃሳብ፤ በድንቅ ብቃትና በመልካም ተግባር፤ በድንቅ ስኬትና በብሩህ ራዕይ ህይወትን ማጣጣም ነው የህይወት ትርጉም። ጨለማውን መንፈስ አሽቀንጥረን መጣል የምንችለው፤ ከሞት በኋላና ከሞት ወዲያ ማዶ አሻግረን ለመቃኘት በመፍጨርጨር አይደለም። ዘላለማዊ ህልውናና የህይወት ትርጉም ያለው፤ እዚሁ በህይወት ዘመን በምናሳልፋቸው ደቂቃዎችና ሰዓታት፤ ቀናትና አመታት ውስጥ ነው።
ህይወትና ሞት የግል ነው። መጋራት አይቻልም። ሁሉም ሰው በየግሉ ይሞታል፤ በዚህ በዚህ ሁላችንም እንመሳሰላለን። ነገር ግን፤ ሁሉም ሰው ህይወትን አያጣጥምም። የምናደንቃቸው ጀግና ሰዎች፤ ዘላለማዊ የህይወት ደስታን አጣጥመዋል። አድናቆታችን ትርጉም የሚኖረው፤ እኛም እንደየአቅማችን ያንን የህይወት ጣእም ለማጣጣም ስንነቃቃ ነው።
*****************************************************************************
 ምንጭ:--http://www.addisadmassnews.com

ረቡዕ, ኖቬምበር 21, 2012

“የፊደል ገበታ አባት”

የ”ሀለሐመ” ፊደል ገበታ ፈጣሪ ማነው?
ተስፋ ገብረስላሴ
**********
ከዛጉዬ ስርወ መንግስት በኋላ ግዕዝን ተክቶ ለንግግርና ለፅሁፍ ማገልገል የጀመረውና “የመንግስት የስራ ቋንቋ” የሆነው አማርኛ፤ ግዕዙን የፊደል ገበታ የቀረፀው ማንና መቼ እንደሆነ ለማወቅ ጉጉት እንደፈጠረው ሁሉ የአማርኛው “ሀለሐመ” የሚለውም እንዴት፣ መቼና በእነማን ተፈጠረ ብሎ መጠየቅ አጓጊ ነው፡፡“የፊደል ገበታ አባት” የሚል ቅፅል መጠሪያ ያገኙት ተስፋ ገብረስላሴን የህይወትና የስራ ታሪክ የሚያስቃኘው መፅሃፍ፤ ስለአማርኛ የፊደል ገበታ ፈጣሪዎች ማንነትና ዘመን ማብራሪያ ባይኖረውም፣ ባለታሪኩ በመጀመሪያ በብራና ላይ በእጃቸው እየፃፉ፣ በመቀጠልም በማተሚያ ቤት ማሽን እያባዙ ለህዝብ እንዲደርስ ያደረጉት “የአማርኛ የፊደል ቅርፅ በወቅቱ በእንጦጦ ማርያም፣ በባዓታ ለማርያምና በመካነየሱስ ስላሴ አጥቢያዎች እንዲሁም በገጠር አብያተ ክርስትያናትና በገዳማትና በዋሻዎች ብቻ ተወስኖ” እንደነበር መረጃ ይሰጣል፡፡
ይህ ፍንጭ አጥኚዎች የፊደል ገበታውን በእነዚህ ተቋማት ያኖረውስ ማነው ብለው እንዲጠይቁ የሚያግዝ ጥቆማ ነው፡፡
ለ100 ዓመት ሴተኛ አዳሪዎች ያልተለዩት መንደር
ተስፋ ገብረስላሴ በ1909 ዓ.ም የ15 ዓመት ልጅ ሆነው ከትውልድ መንደራቸው ወደ አዲስ አበባ ሲመጡ ያረፉበት መንደር አራት ኪሎ ነበር፡፡
በዚያ ዘመን ከአራት ኪሎ መንደሮች አንዱ በሆነው “እሪ በከንቱ ደንበኛ መጠጥ ቤቶችና ጥሩ ጥሩ ሴተኛ አዳሪዎች የሚገኙበት የከተማይቱ ደማቅ አካባቢ ፤አዝማሪና ሸላይ የማይታጣበት የቆንጆዎች መቀጣጠሪያ ነበር” ይላል በመፅሃፉ ገፅ 29 የሰፈረ መረጃ፡፡ የፓርላማ ማስፋፊያና የባሻ ወልዴ ችሎት መንደር ለዳግም ልማት ባይፈርስ ኖሮ ሴተኛ አዳሪነት ሁለተኛውን ምዕተ ዓመት ማስቆጠሩ አይቀርም ነበር ወይ ያሰኛል - መረጃው፡፡
ይፍረስ የተባለው የነጋድራስ አቡነከር ቤት
ተስፋ ገብረስላሴ አዲስ አበባ ከመጡ በኋላ ሰርተው ራሳቸውን ለመቻል በእንጨት ፈለጣ፣ ውሃ በመቅዳት፣ ጉድጓድ በመቆፈር፣ በጎዳና ንግድ እና መሰል ትናንሽ ስራዎች ላይ ተሳትፈዋል፡፡ ነጋድራስ አቡበከር ከጅቡቲ ከሚያስመጧቸው በተለይ ሽቶ እየተቀበሉ በየሆቴሉ ዞረው ሸጠዋል፡፡በዘመኑ በአራት ኪሎ መንደር በንግድ ስራቸው በጣም ታዋቂ የነበሩት ነጋድራስ አቡበከር የአፋር ብሄረሰብ ተወላጅ ነበሩ፡፡
ከፈረንሳይ አገር የሚያስመጡትን ሸቀጥ በጅቡቲ በኩል ወደ አዲስ አበባ በማስገባት አገልግሎት ሲሰጡ በዕድሉ ከተጠቀሙት አንዱ የነበሩት ተስፋ ገብረስላሴ፣ በኋለኛው ዘመን ላይ የነጋድራስ ግቢ ለሽያጭ ሲቀርብ ገዝተው ባለንብረት መሆኑ ቻሉ፡፡ ከህትመት ስራ ጋር የተያያዘ ከ100 ዓመት በላይ ታሪክ ያለው ግቢ ከባሻ ወልዴ ዳግም ልማት ስም ይፍረስ መባሉና ከዚህ ጋር የታዩ ክስተቶች ምን እንደሚመስሉ “ዘመን ተሻጋሪ ባለ-ውለታ” ታሪክን አስፍሮ መማሪያ እንዲሆን ማድረግ ችሏል፡፡
መንግስት በከተሞች ያገኘው ቤንዚን
በአሁኑ ወቅት በአገራችን ኢትዮጵያ እየተመዘገበ ያለው የኢኮኖሚ ዕድገት የነዳጅ ምርትን መሰረት ያደረገ አለመሆኑ ብዙዎችን እንዳስደመመ ይታወቃል፡፡ ካሁን በፊት በመንግስትና በህዝብ የተሰሩትን ሳይጨምር በአምስት ዓመት የትራንስፎርሜሽን እቅድ ተግባራዊ እንዲሆኑ የታቀዱ ሃሳቦችን ለመንደፍ መንግስትን የልብ ልብ የሰጠው ምንድነው ለሚለው ጥያቄ አንዱ መልስ “መንግስት በከተሞች ያገኘው ቤንዚን ነው” የሚል ነው፡፡
ዛሬ በከተማ የሚገኝ አንድ ሜትር ካሬ የመሬት ዋጋ ስንት እየተከፈለበት ነው ለሚለው ጥያቄ አንባቢ ከያለበት ሆኖ የሚያውቀውንና የሰማውን ለራሱ መልስ በመስጠት ያግዘኛል፡፡ የዛሬ 70 ዓመት በአዲስ አበባ ከተማ ያውም በአራት ኪሎ መንደር ለአንድ ሜትር ካሬ መሬት የተከፈለው ከፍተኛው ገንዘብ 2 ብር ከ35 ሳንቲም ነበር፡፡ የተስፋ ገብረስላሴ ማተሚያ ቤት የሚገኝበት ግቢ ከመጀመሪያው ባለይዞታ ወደ ሁለተኛው ባለሃብት የዞረው በዚህ ሽያጭ እንደነበር የ“ዘመን ተሻጋሪ ባለ-ውለታ” መረጃ ለአንባቢያን አቀብሏል፡፡ ለካንስ መንግስት ለታሪክና ለቅርስ ደንታ የሌለው መስሎ የሚታየው ለ “ነዳጁ” የተለየ ክብርና ዋጋ ስለሰጠ ነውም ያስብላል - መረጃው፡፡
የሚስተር ዴቪድ ውለታ
በ1990ዎቹ አጋማሽ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ በወጣ ዜና፤ “የመጀመሪያውን የአማርኛ መፅሃፍ ቅዱስ ተርጉሞ ለህዝብ የቀረበው በዓፄ ቴዎድሮስ ዘመነ መንግስት ከእንግሊዝ የመጣ ሚስዮናዊ ነው፡፡” የሚል ማንበቤን አስታውሳለሁ”” የተስፋ ገብረስላሴን የህይወትና የስራ ታሪክ በሚያስቃኘው መፅሃፍ ውስጥ በአፄ ቴዎድሮስ ዘመን ለወንጌል አገልግሎት ስለመጣ የካቶሊክ ሚሲዮናዊ ስለ ሚስተር ዴቪዲም ያነሳል፡፡
የኤደን ዜግነት የነበረው ሚስተር ዴቪድ፤ ከአፄ ቴዎድሮስ ህልፈት በኋላ በአፄ ምኒልክ ዘመን ወደ አዲስ አበባ በመምጣት “ፒያሳ በተባለው አካባቢ በአሁኑ ሲኒማ አምፒር መደዳ ካለ በአንደኛው ሰቀላ ቤት ላይ መፅሃፍ ቅዱስ እያሳተመ፣ አንዱን መፅሃፍ በአንድ ብር (ማርያትሬዛ) ማንበብና የመግዛት አቅም ላላቸው ሰዎች በየቤታቸው እያንኳኳ ይሸጥ እንደነበር ተገልጿል፡፡
የዚህ ሰው ተግባርና ውለታ ብቻውን በመፅሃፍ በቀረበለት የሚያሰኝ ነው፡፡ የክርስትና ሃይማኖት ለአገራችን የህትመት ዘርፍ፣ ለአማርኛ ቋንቋ ዕድገት፣ ለመፅሃፍ መሸጫ መደብሮች መከፈት፣መፅሃፍ አዙሮ የመሸጥ ስራ ለመጀመር… ቀላል የማይባል አስተዋጽኦ አበርክቷል፡፡
ክስ፣እስርና ውንጀላ ያልተለያቸው ባለታሪክ
የተስፋ ገብረስላሴን የስራና የህይወት ታሪክን ማዕከል አድርጎ የአገራችንን ማህበራዊ ፣ፖለቲካዊ፣ኢኮኖሚያዊና ባህላዊ ጉዳዮች በስፋት የሚያስ(ነኘው “ዘመን ተሻጋሪ ባለ-ውለታ” መፅሃፍ፤ ባለ ታሪኩ የህዝብና የአገር ባለውለታ መሆን የቻሉት በብዙ ውጣ ውረድ ውስጥ አልፈው እንደሆነ ይገልፃል፡፡
በንጉሱ ዘመን (ከኢጣሊያ ወረራ በፊትና በኋላ) ፣በጠላት ወረራ ወቅት፣ በደርግም አገዛዝ ለክስ፣ ለእስርና ውንጀላ ተዳርገዋል፡፡ በመጨረሻ ሁሉንም አሸንፈው በተደጋጋሚ ተሸላሚ ሆነዋል፡፡ ከአፄ ኃይለስላሴ መንግስት የቀኝአዝማች ማዕረግ ተሰጥቷቸዋል፡፡ የኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበር ደጋግሞ አመስግኗቸዋል፡፡
ሞትን መቅደም
ታላቅ ተግባርና ትልቅ ስም አርቆ መድረሻን ለማቀድ፣ከብዙ ጥረትና ልፋት የሚገኝ ነው፡፡ በአመታት ድካም የተገነባ መልካም ተግባርና ስም ሊጠፋ፣ ሊረሳና ሊዘነጋ የሚችልባቸው ብዙ ምክንያቶች አሉ፡፡ እኔ ከሞትኩ በኋላ ጥረትና ድካሜ ምን ይሆናል ብሎ ቀድሞ አለማሰብ ታላቅ ተግባርና ስም እንዲጠፋ ሰበብ ከሚሆኑት አንዱ ነው፡፡ ቤተሰቦቻቸውን ባለ አክሲዮን በማድረግ ኃ.የተ.የግ.አ/ማህበር በ1991ዓ.ም ያቋቋሙት ባለታሪኩ፤ ስራና መልካም ተግባራቸው እንዳይጠፋ ማድረግ ችለዋል፡፡
ለሟች መታሰቢያ ሐውልት ይሻላል ቤተ መፅሃፍት
ተስፋ ገብረስላሴ ግንቦት 26 ቀን 1992ዓ.ም ከዚህ ዓለም በሞት ሲለዩ፣ የ97 ዓመት የዕድሜ ባለፀጋ ነበሩ፡፡ ከመሞታቸው በፊት የቀብር ቦታቸውን በስላሴ ካቴድራል ለማዘጋጀት አስበው የነበረ ቢሆንም የአርበኞች ማህበር አርበኝነታቸውን አላውቅም ስላለ ቀብራቸው በእንጦጦ ኤልያስ ቤተክርስቲያን ተፈፅሟል፡፡ ባለ ሁለት ክፍል መቃብር ቤት ቤተ መፅሃፍት ሆኖ እንዲያገለግል ስለታሰበም በውስጡ ከ300 በላይ መፅሀፍት ይዟል፡፡
ይህ በአገራችን በስፋት ሊለመድ የሚገባ ጥሩ ጅማሮ ነው፡፡ “የፊደል ገበታ አባት” የሚል ቅዱስ መጠሪያ ያላቸው የቀኝ አዝማች ተስፋ ገብረስላሴን የህትመትና የስራ ታሪክ የሚያስቃኘውን መፅሃፍ የማስተዋወቅ ዳሰሳዬን የማጠቃልለው የዚህ ዓይነት መፅሃፍት ህትመት ቁጥር እየተበራከተ መምጣቱ ይበል የሚያሰኝ መሆኑን ገልጬ ነው፡፡
************************************************
ምንጭ:==http://www.addisadmassnews.com

ሰኞ, ኖቬምበር 12, 2012

ጋዜጠኛ ደምሴ ዳምጤ

"ዳኙ ገላግለን"

 1945-2005

‹‹ዳኙ ሊመታ ነው፤ ዳኙ ገላግለን . . . ወይኔ ዳኙ አ - ገ - ባ -፤ ደንሶ አገባ ዳኙ፣ ቀኝ አሳይቶ ግራ፣ ግራ አሳይቶ ቀኝ በጣም አስደናቂ ግብ ነው . . . ›› ትንፋሹ ቁርጥ ቁርጥ እያለ ደስታና ሲቃ፣ ስሜትም በተቀላቀለበት ድምፀት ታኅሣሥ 17 ቀን 1980 ዓ.ም. ያስተጋባው ታዋቂው የስፖርት ጋዜጠኛ ደምሴ ዳምጤ ነበረ፡፡
ኢትዮጵያ ያዘጋጀችውን 15ኛው የምሥራቅና መካከለኛው አፍሪካ ዋንጫ ከ25 ዓመት በፊት ያገኘችበትን ድል በራዲዮ ሞገድ አሳብሮ ድምፁን፣ እስትንፋሱን ያሰማው ጋዜጠኛ ደምሴ ትናንት ነበር፣ ዛሬ ግን የለም፣ ከአፀደ ሥጋ ተለየ፤ አረፈ፡፡

በኢትዮጵያ ስፖርት ጋዜጠኝነት ታሪክ ሁነኛ ሥፍራ ያለው ደምሴ፣ የስፖርት ዜናዊነቱን የጀመረው ምሥራቃዊቷ ድሬዳዋ ከተማ በአማተርነት እየዘገበ ወደ አዲስ አበባ መላክ በጀመረበት ጊዜ ነው፡፡ በተለይ በኢትዮጵያና ብሥራተ ወንጌል ሬዲዮ ጣቢያዎች፣ በኢትዮጵያ ቴሌቪዥንም ጋዜጠኛና ‹‹የስፖርት ፋና›› ጋዜጣ መሥራች ከነበረው ታላቁ ጋዜጠኛ ሰሎሞን ተሰማ ጋር ቅርበት ስለነበረው ከድሬዳዋ የሐረርጌን ስፖርታዊ እንቅስቃሴ እየዘገበ ይልክ ነበር፡፡

ኢትዮጵያ 10ኛውን የአፍሪካ ዋንጫ ካስተናገደችባቸው ከተሞች አንዷ ደምሴ ዳምጤ የነበረባት የኖረባት ድሬዳዋ የእግር ኳስ ዘገባ ትሩፋት ያቀረበባትም ነች፡፡ ለአገሪቱ ስፖርት ዕድገት በተለይም እግር ኳሱ እንዲያብብ በሙያው ያደረገው ጥረት ኢትዮጵያውያን ተጫዋቾች ክሂላቸው ከማንም እንደማያንስ በማንፀባረቅ ነበር፡፡ በ1970ዎቹ መጨረሻና በ80ዎቹ መጀመርያ ጎልተው ወጥተው የነበሩት እነሙሉጌታ ከበደ፣ ሙሉጌታ ወልደየስ፣ ገብረመድኅን ኃይሌን ሲያወድስ ገጣሚ ሆኖ በመገኘት ነበር፡፡

‹‹የምን ማራዶና የምን ፔሌ ፔሌ
እኛም አገር አለ ገብረመድኅን ኃይሌ›› ጎልታ የምትጠቀስለት መንቶ ግጥሙ ነበረች፡፡

በዘመኑ እየበረከቱ የመጡት ወጣት ጋዜጠኞች አርአያቸው እንደሆነ የሚናገሩለት ደምሴ፣ ሦስት ኦሊምፒኮች የዓለም ሻምፒዮናዎች፣ የአገር አቋራጭ ውድድሮችን እየተመለከተ ዜናውን አድርሷል፡፡

ጋዜጠኛ ደምሴ ተወልዶ ያደገው ድሬደዋ ሲሆን ከ33 ዓመት በፊት በኢትዮጵያ ሬድዮ ከመቀጠሩ በፊት የስፖርት ፊሪላንስ ጋዜጠኛ ሆኖ ከትውልድ ስፍራው ይሰራ ነበር፡፡

ጋዜጠኛ ደምሴ ለኢትዮጵያ ስፖርት እድገት ደከመኝ ሳይል የሰራና በዚህም በህዝብ ዘንድ ከፍተኛ ተወዳጅነትን ያተረፈ ባለሙያ ነበር፡፡

በሙያውም አትላንታ፣አቴንስና ቤጅንግ ኦሎምፒኮችን በስፍራው በመገኘት ለኢትዮጵያ ህዝብ አስተላልፏል፡፡


ከአባቱ አቶ ደምሴ ሳልለውና ከእናቱ ወይዘሮ ታየነው በሐረርጌ ጠቅላይ ግዛት ጋራ ሙለታ የተወለደው ጋዜጠኛ ደምሴ፣ ባደረበት ሕመም ምክንያት ሕክምናውን በአገር ውስጥና በውጭ ሲከታተል ቆይቶ ጥቅምት 26 ቀን 2005 ዓ.ም. አርፏል፡፡ ሥርዓተ ቀብሩም ትናንትና በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አፈ ጉባኤ አቶ አባዱላ ገመዳ፣ የመንግሥት ሹማምንትና የስፖርት ቤተሰቦች በተገኙበት ተፈጽሟል፡፡ ጋዜጠኛ ደምሴ ዳምጤ ባለትዳርና የሦስት ልጆች አባት ነበረ፡፡

ደምሴ ኢትዮጵያ በ1980 ለምሥራቅና መካከለኛው አፍሪካ አገሮች ሻምፒዮና(ሴካፋ) ከዚምባብዌ ጋር አዲስ አበባ ላይ ለፍጻሜ በፍጹም ቅጣት በደረሰችበት ወቅት ዳኛቸው ደምሴ በመጨረሻ ለሚመታት ምት ''ዳኙ ገላግለን''ብሎ በሬዲዮ ባስተላለፈው የቀጥታ ስርጭት ሳቢያ ብዙዎች ይህንኑ እንደ ቅጽል ስም አድርገውለት መቅረቱም ይታወቃል።

ከአንጋፋዎቹ ዝነኛና ታዋቂ የአገራችን የስፖርትጋዜጠኞች ሰለሞን ተሰማ ነጋ ወልደስላሴና ፍቅሩ ኪዳኔ ቀጥሎ በ1962 ዓ.ም. ከድሬ ደዋ በአማተር የስፖርት ዜና ዘጋቢነት ለ ሰባት አመታት በመቀጠልም በኢትዮጵያ ሬድዮ ድርጅት እስካሁን ለ33 ዓመታት ባጠቃላይ ከ40 ዓመት በላይ የስፖርት ጋዜጠኛ በመሆን ያገለገለ ታዋቂና ዝነኛው ጋዜጠኞ ደምሴ ዳምጤ -
- በሞስኮ ፤ በሎሳጀለስ ፤ በሴኦል ፤ በባርሴሎና ፤ በአትላንታ ፤ በሲድኒ ፤ በአቴንስና በቤጂንግ የኦሎምፕክ ጨዋታዎች ባቀረባቸው የስፖርት ዘገባዎች፤
- በዓለምና የአፍሪካ ዋንጫ ማጣሪያ የእግር ኳስ ጨዋታዎች ባስተላለፈው የእግር ኳስ ቀጥታ ስርጭት፤
- በዓለም አትሌትክስ ሻምፒዮንና በመላ አፍሪካ ጨዋታዎች፤
*******************************************************************************
 ምንጭ:--http://www.ethiopianreporter.com
             http://ethiopianobserver.wordpress.com/
             http://shegertribune.blogspot.com
            

እሑድ, ኦክቶበር 28, 2012

ተክሎ የሚጽፍ፤ ብርቱ ባለቅኔ

“የማይነጋ ህልም ሳልም
የማይድን በሽታ ሳክም
የማያድግ ችግኝ ሳርም
የሰው ህይወት ስከረክም
እኔ ለእኔ ኖሬ አላውቅም ::”

ብላቴን ጌታ ሎሬት ፀጋዬ ገብረ መድህን

                        (1928-1998 ዓ.ም.)
የዓለም ሎሪየት ታላቅ ባለቅኔ አንትሮፖሎጂስት እና ኢጂፕቶሎጂስት፣ የኮሜርስ ምሩቅ የህግ እውቀት ባለሙያ ጥዑመ ልሣን (ልዩ የትረካ ችሎታ ያለው) ተመራማሪ፣ ፀሐፌ ተውኔት ደራሲና ተርጓሚ ፀጋዬ ገብረ መድህን ቀዌሣ፤ ዛሬ በአፀደ ሥጋ ከእኛ ጋር ቢኖር ኖሮ በሥነ ጽሑፍከፍተኛውን ዓለም አቀፍ የሥነ ጽሑፍ ሽልማት (Nobel Prize) ለመሸለም የመጀመሪያው ኢትዮጵያዊ ባለቅኔ፣ የቋንቋ ጠቢብና የጽሑፍ ጥበብ ሊቅ ለመሆን በቻለ፡፡ በአማርኛና በኦሮምኛ፣ በእንግሊዝኛና በግዕዝ ቋንቋዎች ቅኔን የተቀኘ ብርቱ ባለቅኔ፤ በአማርኛ በኦሮምኛና በእንግሊዝኛ ቋንቋዎች ታላላቅ ሃሳቦችን የፃፈ ታላቅ ጠቢብ ነው - ፀጋዬ ገብረ መድህን፡፡ በሰው ልጆች ታሪክ ውስጥ በዓለማችን በተለያየ ሥፍራና ዘመን ከተፈጠሩ ታላላቅ ሊቃውንት አንዱ የሆነው ጋሼ ፀጋዬ በኢትዮጵያ ሥነ ጽሑፍ ውስጥ ከአንድ በላይ በሆነ ቋንቋ ከፃፉ ጥቂት ኢትዮጵያውያን ደራሲያን ጐራ ነው፡፡
ሣህለ ሥላሴ ብርሃነ ማርያም በጉራጊኛ በአማርኛና በእንግሊዝኛ ጽፈዋል፤ በሶስት ቋንቋዎች፡፡ ጋሼ ስብሃት ለአብ ገብረ እግዚአብሔር በተለይ በአማርኛና በእንግሊዝኛ፤ በተወሰነ መጠን ደግሞ በትግርኛና በፈረንሳይኛ ጽፏል፤ በአራት ቋንቋዎች፡፡ አቤ ጉበኛና ዳኛቸው ወርቁ በአማርኛና በእንግሊዝኛ ጽፈዋል፤ በሁለት ቋንቋዎች፡፡ እንዲሁም ሌሎች ኢትዮጵያውያን የጽሑፍ ጥበብ ባለሙያዎች በሁለትና በሶስት ቋንቋዎች የፃፉ አሉ፡፡ ጋሼ ፀጋዬ በሶስት ቋንቋዎች የፃፈ፤ በአራት ቋንቋዎች ቅኔን የተቀኘ ብርቱ ባለቅኔና ሊቀ ጽሑፍ (የፅሁፍ ጥበብ ሊቅ) ነው፡፡ የዋርካው ሥር ንግርት”፤ ኢትዮጵያን የላይኛው እውነት ከፍተኛው እውነት፤ የላይኛው ዙፋን …ያለበት ኤዞፕ የተሰኘውና ስለመጀመሪያው ጥቁር ፈላስፋ የሚቀኘው ያማረ ቅኔው፤ ቴዎድሮስ የተሰኘውና በእንግሊዝ አገር በሚገኙ ዩኒቨርሢቲዎች ውስጥ የታየ ቲያትሩ በእንግሊዝኛ ቋንቋ ከፃፋቸው ሥራዎቹ ሶስቱ ናቸው፡፡

እንዲሁም በአማርኛና በኦሮምኛ ቋንቋዎች የፃፋቸው በርካታ በከበረ ሃሳብ፣ በተዋበ ጥበብ የተመሉ ሥራዎች አሉት፡፡ ከእንግሊዝኛ ወደ አማርኛ የተረጐማቸውም እንደዚሁ በርካታ ናቸው፡፡
የሥመ ጥሩውን እንግሊዛዊ ባለቅኔና ፀሐፌ ተውኔት ዊሊያም ሼክስፒርን ሥራዎች ወደ ኢትዮጵያዊ ቋንቋዎች የተረጐሙ ኢትዮጵያውያን ጠበብት አሉ፡፡ ከነዚህ ውስጥ የክብር ዶክተር ደራሲ ከበደ ሚካኤልና መሥፍን ዓለማየሁ ይወሳሉ፡፡ ይሁንና በጋሼ ፀጋዬ መጠን የዊሊያም ሼክስፒርን ሥራዎች ለኢትዮጵያውያን ታዳሚዎች ያስተዋወቀ ማንም የለም፡፡ ጋሼ ፀጋዬ በኢትዮጵያ ቲያትር መድረክ በትርጉም ሥራዎቹም ሆነ በፈጠራ ተውኔቶቹ የራሱ የሆነ አዲስ የብርሃን ፈር የቀደደ (ከዘመን ዘመን ወደፊት ቀድሞ የራሱን ተደራሲ የፈጠረ) ታላቅ የተካነ የኪነጥበብ ባለሙያ ነው፡፡ ፀጋዬ ገብረ መድህን የጽሑፍ ጥበብ ባለሟል ብቻ ሳይሆን በኅብረተሰብ የምርምር ዘርፍ ከፍተኛ እውቀት ያለው፣ ከፍ ያለ ደረጃ የሚሰጠው ተመራማሪ ነው፡፡ ሁልጊዜ ወደ እውነት፤ ሁልጊዜ ከፍ ወዳለ እውቀት፤ ሁልጊዜ ወደተሳለ ጥበብ፤ ሁልጊዜ ወደ ሠፊ ምናብና ጥልቅ እውቀት የሚያድግ፣ ትጉህና የተባ ሊቀ ጽሑፍና ተመራማሪ ነው፡፡
ፀጋዬ ገብረ መድህን ቀዌሣ ከፍ ባለ ጥበብና በተኳለ ውበት፣ በእውነትና በፍቅር የተነካ የተሟሸ አንደበት ነው፡፡ የአፍሪቃና የህዝቦቿ አንደበት፤ የኢትዮጵያና የህዝቦቿ አንደበት፤ የኦሮሞ ህዝብ አንደበት፤ የተፈጥሮና የአምላክ አንደበት፤ የጥበብና የጥልቅ ምርምር አንደበት፤ የብርሃን ቃና ህያው አንደበት ነው፡፡
ዓመተምሕረቱን በትክክል ባላስታውስም፤ ከሠባ አምስት ዓመታት በፊት ግድም በአሥራ ዘጠኝ ሃያዎቹ መጨረሻና በአሥራ ዘጠኝ ሠላሳዎቹ መካተቻ ከአዲስ አበባ በስተምዕራብ አንድ መቶ ሠላሳ ስድስት ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ አምቦ አካባቢ ነው ጋሼ ፀጋዬ የተወለደው፡፡ ታላላቅ ሰብዕና ያላቸው ኢትዮጵያውያን ሠሎሞን ደሬሣ በወለጋ ጩታ፤ ሣህለ ሥላሴ ብርሃነ ማርያም በጉራጌ፤ ስብሀት ለአብ ገብረእግዚብሔር በአድዋ ርባገረድ፣ ተባባሪ ፕሮፌሰር ተስፋዬ ገሠሠ…የተወለዱት በዚሁ ዘመን በተለያየ ሥፍራ ነው፡፡ አፈወርቅ ወልደ ነጐድጓድ ከዚህ ዘመን ጥቂት ቀደም ይላል፡፡ የክብር ዶክተር ሀዲስ ዓለማየሁ ደግሞ ከሁሉም ቀደም ማለት ብቻ ሳይሆን፤ ከጐጃም ወደ አዲስ አበባ መጥተው ተፈሪ መኮንን እየተማሩ ፀረ ፋሺስት ቅስቀሳ ሲያደርጉ የነበረው በዚህ ዘመን ነው፡፡ ጋሼ ፀጋዬ የተወለደው ሀዲስ ዓለማየሁ በትግራይ ሠለክለካ የኢትዮጵያን አርበኞች ፀረ ፋሺስት ተጋድሎ ለመምራት እየተሰናዱ ነው፡፡
የታዋቂው አፍሪቃዊ ባለቅኔ፣ የትውልድ አገሩ የሴኔጋል ፕሬዚዳንት፣ በፈረንሣይና በፈረንሣይኛ ተናጋሪ አገሮች (Franco Phone) ተሠሚነት ያለው ትልቅ ምሁር፣ ሴዳር ሴንጐር የልብ ወዳጅ የሆነው ፀጋዬ ገብረመድህን ቀዌሣ፤ ከአምቦ ወደ አዲስ አበባ መጥቶ በወጣትነቱ መጀመሪያ የተማረው የንግድ ሥራ ኮሌጅ (ኮሜርስ) ገብቶ ነው፡፡ ከኮሜርስ በንግድ ሥራ ከተመረቀ በኋላ ነፃ የትምህርት ዕድል በማግኘት በአሜሪካን አገር በሚገኝ ዩኒቨርሲቲ የህግ ትምህርት አጥንቶ ከፍ ባለ ማዕረግ ተመርቋል፡፡
በቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዘመነ መንግሥት በአገሪቱ ከፍተኛውን የሥነ ጽሑፍ ሽልማት ከግርማዊ ጃንሆይ ከተቀበሉ ኢትዮጵያውያን የኪነጥበብ ባለሙያዎችና ሊቃውንት መሀከል አንዱ ጋሼ ፀጋዬ ገብረመድህን ነው፡፡
በጥቁር ግብጽ ጥናት ኢጂፕሎጂስትና በኅብረተሰብ የምርምር ዘርፍ አንትሮፖሎጂስት በመሆን ደማቅና ክቡር እውቅና ያለው ጋሽ ፀጋዬ፤ የታሪክ ምሁርና ከፍ ያለ ተመራማሪ ጭምር ነው፡፡
አንድ ኢትዮጵያዊ ምሁር ስለ ጋሽ ፀጋዬ በፃፈው መጽሐፍ፤ ይሄንን ታላቅና ብርቱ ኢትየጵያዊ ባለቅኔ “ምሥጢረኛው ባለቅኔ” እንዳለው አስታውሳለሁ፡፡
ከሃምሣ ዓመታት በላይ በትጋትና በትባት በጽንአት የተባ ብዕሩን ተክሎ ለመፃፍ የቻለ ሊቀ ጽሑፍ ነው ጋሽ ፀጋዬ፡፡
አብዛኞቹ ሥራዎቹ ግጥምና ቅኔዎች ተውኔቶችና የምርምር ሠነዶች ናቸው፡፡ ከተውኔቶቹ ከፊሎቹ ከእንግሊዝኛ ወደ አማርኛ የተተረጐሙ ሲሆኑ፤ ከነዚህ ውስጥ አብላጮቹ ከአምስት መቶ ዓመታት በፊት በአውሮጳ የኖረው ታዋቂው እንግሊዛዊ ፀሐፌ ተውኔት የዊሊያም ሼክስፒር ሥራዎች ናቸው፡፡ እርሱ በእንግሊዝኛ ከፃፋቸው ደግሞ በተለያዩ የአፍሪካ አገራት መድረኮች የታዩም አሉ፡፡ ከነዚህ ውስጥ አንዱ “ቴዎድሮስ” ነው፡፡
የጋሽ ፀጋዬ ሥራዎች በአገርና በህዝብ ፍቅር፤ በጥናትና በምርምር በአገሪቱና በህዝቦቿ ክቡር ቅርሶችና ዓይነታ (typical) ማንነት ላይ ያተኮሩ ብርሃንማ ቃና ያላቸው የተፈጥሮና የእግዚሃር ምሥክርና ህያው አንደበት ናቸው፡፡
በጥቁር አፍሪቃና በአረብ አፍሪቃ ከሃምሳ ሦስት በሚበልጡ አገራት ውስጥ ከሺህ በላይ ቋንቋዎች አሉ፡፡ በኢትዮጵያ ውስጥ ብቻ እንኳን ከሰማንያ የሚበልጡ ቋንቋዎችና ከሦስት መቶ በላይ ዲያሌክት አሉ፡፡ ከነዚህ ሺህ ቋንቋዎች የራሳቸው ፊደል ያላቸው ሁለት ብቻ ናቸው፡፡ አማርኛና አረብኛ፡፡ ይሁንና በሥነ ፅሁፍ የመጀመሪያውን ከፍተኛ ዓለም አቀፍ ሽልማት ለማግኘት የቻሉት አፍሪቃውያን ደራሲያን:- ወሌ ሱየንካ ከናይጄሪያ፤ እና ነጂብ ማህፉዝ ከግብፅ ናቸው፡፡ እንዲሁም ከደቡብ አፍሪቃ የሰላም ሰው (A man of peace) በመሰኘት ደግሞ ዴዚሞን ቱቱ እና ኔልሰን ማንዴላ፡፡ ወሌ ሱየንካ ከአፍሪቃ ከፍተኛውን ዓለም አቀፍ የሥነ ፅሁፍ ሽልማት (Nobel prize) በማግኘት ቀደምት አፍሪቃዊ ሊቀ ፅሁፍ ሲሆን፤ ከሶስት እና ከአራት ዓመታት በፊት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የክብር ዶክተሬት ዲግሪውን ተቀብሏል፡፡ ከነጂብ ማህፉዝ መፃህፍት ሁለቱ “ሌባውና ውሾቹ” የሚለውና “አሳረኛው” በአማርኛ ተተርጉመዋል፡፡ፊደል ያለው ብቸኛ አፍሪቃዊ ህዝብ ሆነን ለሺህ ዘመናት ፀንተን የኖርን ህዝቦች፤ ከፍተኛውን ዓለም አቀፍ የሥነ ፅሁፍ ሽልማት ለማግኘት ዘገየን፡፡ ከዚህ ሽልማት ጋር አንድ ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር፤ ወይም ከአሥራ ሰባት ማሊዮን ብር በላይ አብሮት አለ፡፡
ጋሼ ፀጋዬ ገብረመድህን ቀዌሳ እስካሁን በአካለ ሥጋ ቢኖርና ብዕሩ በህያውነት ቢዘልቅ ያንን ታላቅ የሥነ ፅሁፍ ሽልማት ለማግኘት፤ የመጀመሪያው ኢትዮጵያዊ የሥነ ፅሁፍ ባለሙያ ሊሆን በቻለ ነበር፡፡ ይሄ ፅሁፍ ለብርቱው ኢትዮጵያዊ ባለቅኔ የዓለም ሎሪየት ፀጋዬ ገብረመድህን ቀዌሳ ታላቅ ነፍስ ክብር ይገባዋል፡፡
************************************************************************************
ምንጭ:--http://www.addisadmassnews.com

ማክሰኞ, ኦክቶበር 09, 2012

«...ኢትዮጵያ ልዩና ታሪካዊ አገሬ ናት...»

ፕሮፌሰር ሪቻርድ ፓንክረትስ
*********************
የለንደኑ ትንታግ ወጣት ለኢትዮጵያ በመወገን እንደ አርበኛዋ እናታቸው ፀረ- ፋሽስት ጽሑፎችን በጋዜጣ በማውጣት ትግል የጀመሩት ገና የዩኒቨርሲቲ ተማሪ እያሉ ነበር። ይህም በመሆኑ የሥነ ጽሑፍ ክህሎታቸውን በንድፈ ሐሳብ እውቀትና በምርምር አዳብረው ለህትመት ካበቋቸው ከሃያ በላይ መጻሕፍት የተወሰኑት ለአገራችን ዩኒቨርሲቲዎች የመማሪያና የምርምር ሰነዶች ለመሆን በቅተዋል።
በልጅነት ዕድሜያቸው የኢትዮጵያን ጉዳይ በደማቸው ያሰረፁትና በሃያ ዘጠኝ ዓመታቸው የዶክትሬት (PHD) ዲግሪያቸውን በከፍተኛ ማዕረግ አግኝተዋል። የለንደኑ ዩኒቨርቲቲ የዕውቀት ቀንዲል ለአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ከሃምሳ ዓመት በላይ የሰጡት ምሁራዊ ተልዕኮ ተቋሙ ዛሬ ለደረሰበት የዕድገት ምዕራፍ የታሪክ ባለድርሻ አድርጓቸዋል።
በወጣትነት ዕድሜያቸው ከጀመሩት ክቡር የመምህርነት ሙያ ባለፈ በኢትዮጵያ ላይ የላቀ ምርምርና ጥናት ለማካሄድ ያስቻለ፣ ታሪካዊ ቅርሶችን አሰባስቦ ለመያዝ ያገዘ እና አገራችንን ለዓለም አቀፉ ህብረተሰብ ያስተዋወቀ፣ የኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ኢንስቲትዩትን በመመስረት እንደእናታቸው የዘመን ተሻጋሪ ታሪክ ባለቤት ለመሆን ችለዋል።
በቅኝ ገዥዎችና በፋሽስት ኢጣሊያ የተዘረፉ ታሪካዊ ቅርሶችን ለማስመለስ ከኢትዮጵያውያን ባልንጀሮቻቸው ጋር በመሆን በአደረጉት ዓለም አቀፋዊ ትግል የአክሱም ሐውልትን፣ የአፄ ቴዎድሮስ ክታብንና ሌሎችንም ቅርሶችን በአገራቸው ከወገናቸው ጋር ደምቀው እንዲታዩ በማድረግ ሕዝባችን ለዘመናት ከነበረበት ፀፀትና ቁጭት እንዲላቀቅ አድርገዋል።
የእናታቸውን የአርበኝነት የተጋድሎ ገድል የሕይወት ዘመን ስንቅና መመሪያ አድርገው በተለይም ከአዲስ አበባ ዩንቨርሲቲ ኮሌጅ ጀምረው ተቋሙ ዩኒቨርሲቲ ከሆነም በኋላ ለአበረከቱት ምሁራዊ አስተዋፅኦ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የመርጌታነትና የተመራማሪነት ብቃታቸውን በማረጋገጥ የፕሮፌሰርነትና የክብር ዶክትሬት (PHD) ዲግሪ ማዕረግ አጐናፅፏቸዋል።
በብሔራዊም ሆነ በዓለም አቀፍ ደረጃ አንቱታን ያተረፉት እኒሁ ምሁር በኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ ባደረጉት ጥልቅ ጥናትና ምርምር ከአፄ ኃይለሥላሴ ሽልማት ድርጅትና ከእንግሊዝ መንግሥት የወርቅ ሚዳሊያና ኒሻን ለመሸለምም በቅተዋል።
የኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ኢንስቲትዩትን ከመመስረት ባለፈ በሰጡት ያልተቆጠበ አመራርና ድጋፍ ለእኒሁ የአገር ባለውለታ ምሁር የሃምሳ ዓመት ወርቃማ አገልግሎት ለመዘከር በተዘጋጀ ልዩ ሥነ ሥርዓት ላይ በብር የተሰራ የአክሱም ሐውልት ምስል ተሸላሚ ሆነዋል።
የእነዚህና የሌሎችም እውነታዎች ባለቤት የምጣኔ ሀብት ታሪክ ምሁሩ ፕሮፌሰር ሪቻርድ ኬር ፔቲክ ፓንክረስት ይባላሉ። እኒህ የዛሬው እውቅ ዓለም አቀፍ ምሁርና የዚያን ጊዜው እምቦቀቅላ ሕፃን የተወለዱት እ.አ.አ በወርሐ ታህሣሥ 1927 በአገረ እንግሊዝ ለንደን ከተማ በሚገኘው ሐምስቴድ ሆስፒታል ነው። የዚያን ጊዜው ብላቴና የዛሬው አዛውንት እናት የኢትዮጵያ ሕዝብ የቁርጥ ቀን የልብ ወዳጅ፣ የሴቶች መብት ተሟጋች ፣ አርቲስት፣የሶሻሊስት ርዕዮተ ዓለም አቀንቃኝ፣ የፀረ - ፋሽዝም ንቅናቄ ፈር ቀዳጅ፣ ጋዜጠኛና ደራሲ የሆኑት ሚስስ ሲልቪያ ፓንክረስት ይባላሉ። አባታቸው ሚስተር ሲልቪዮ ኮርዮም ሰዓሊና ጋዜጠኛ፣ እንዲሁም ፀረ ፋሽስት አቋም የነበራቸው እንግሊዝ አገር የሚኖሩ ኢጣሊያዊ ስደተኛ ነበሩ።
የዚያን ጊዜው የለንደኑ ቡቃያና የዛሬው ፕሮፌሰር የተወለዱት አንደኛው እና ሁለተኛው የዓለም ጦርነት በተጠናቀቀበት ማግሥትና ዋዜማ በመሆኑ ጦርነቶቹ የፈጠሩአቸው ፖለቲካዊ፣ ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ መመሰቃቀሎች በዕድገታቸው ላይ አንፃራዊ ተፅዕኖ መፍጠሩ ባይቀርም ወላጆቻቸው ዕቅፍ ድግፍ አርገው በማሳደጋቸው እነሆ ከዚያ ዘመን የከፋ ሰብዓዊ ቀውስ ተርፈው ዛሬ የሰማንያ አምስት ዓመት ዕድሜ ባለፀጋ ለመሆን በቅተዋል።
በጦርነቶች መካከል የለመለመች ሕይወት
ምንም እንኳን የያኔው ሕፃን ሪቻርድ ከልደት እስከ ልጅነት የነበራቸው የሕይወት ጉዞ ጦርነት ባስከተለውና በፈጠረው ሰብዓዊ ቀውስ የታጀበ ቢሆንም አንድ ለእናቱ የሆኑት የሚስስ ሲልቪያ የስስት ልጅ በሰባት ዓመታቸው ከእናታቸው ጉያ ወጥተው ችክዌል በሚባለው ትምህርት ቤት ይገባሉ። ሆኖም ግን የገቡበት ትምህርት ቤቱ የሚመላለሰው የባቡር ሀዲድ በመጐዳቱ ሕፃኑ ተማሪ በእግራቸው ተመላልሰው መማር እንደማይችሉ ታመነበት። እናም አፋጣኝ እርምጃ በመውሰድ መኖሪያቸው አካባቢ በነበረው ወደ ባንክራፍት ትምህርት ቤት ይዛወራሉ።
የዚያን ጊዜው ሕፃንና ተማሪ ሪቻርድ ፓንክረስት ትምህርት ቤታቸውን የዕውቀት ማዕከል በማድረግ ከክፍል ወደ ክፍል ከፍተኛ ውጤት እያገኙ መዘዋወረ ሲጀምሩ የብሩህ አዕምሮ ባለፀጋ መሆናቸውን ያመላክታሉ። ይሁን እንጂ 'በጥባጭ ካለ ማን ጥሩ ውሃ ይጠጣል' እንዲሉ ገና የሰባተኛ ክፍል ተማሪ እያሉ ሁለተኛው የዓለም ጦርነት ይጀመራል። ወቅቱ እንኳንስ ለመማር ቀርቶ በህልውና ለመትረፍም አስፈሪ ቢሆንም ትምህርት ቤቶች ባለመዘጋታቸው ተማሪ ሪቻርድ ፓንክረስት እንደሌሎቹ አቻዎቻቸው የመማር ማስተማሩን ሂደት በሚገባ መከታተላቸውን ይቀጥላሉ። ምንም እንኳን ጦርነቱ የፈጠረው ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ቀውስ በሁሉም እንግሊዛዊ ላይ የሚታይ ነበር። የአርበኛዋ የወይዘሮ ሲልቪያ ልጅ በትምህርት አቀባበላቸውና ዘወትር ከማይለያቸው ትጋታቸው ላይ ተፅዕኖ እንዳልፈጠረባቸው ዛሬ ላይ ሆነው ያስታውሳሉ።
ይህም በመሆኑ ወጣቱ ፓንክረስት ለመማር የነበራቸው ሩጫ ባይጠናቀቅም ሁለተኛው የዓለም ጦርነት ከመጠናቀቁ በፊት ማለትም እ.አ.አ 1944 በአስራ ስምንት ዓመታቸው የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን በከፍተኛ ውጤት በማጠናቀቅ ዩኒቨርሲቲ ለመግባት መንፈሳዊ ዝግጅት ያደርጋሉ። ግን ደግሞ የእንግሊዝ መንግሥት ዩኒቨርሲቲዎች አገራዊ ግዳጃቸውን ተወጥተው ከግንባር ለሚመለሱ ወጣቶች ቅድሚያ የትምህርት ዕድል እንዲሰጣቸው የሚል አዲስ መመሪያ በማውጣቱ ዩኒቨርሲቲ ለመግባት ቀን ይቆጥሩ የነበሩት ወጣቱ ሪቻርድ በሚፈልጉት ከፍተኛ ትምህርት ተቋም ለመግባት እንቅፋት ይገጥማቸዋል።
ይሁን እንጂ የልጃቸውን ጭንቀት በሚገባ የተረዱት እናታቸው ወይዘሮ ሲልቪያ ጓደኛቸው የሆኑትንና የፖለቲካል ሳይንቲስት የነበሩትን ፕሮፌሰር ላስኬን ያማክሯቸዋል። ምሁሩም የተለያዩ በጐ ምክንያቶችን በመደርደር ወጣቱ ሪቻርድ ለንደን ዩኒቨርሲቲ እንዲገቡ ይደረጋሉ። የሚስስ ሲልቪያ ብቸኛ ልጅ ሩቅ አስበው ቅርብ አዳሪ አልሆኑም። እናም ለንደን ዩንቨርሲቲ ኢኮኖሚክስ ትምህርት ቤት በመግባት ትምህርታቸውን በትጋት መከታተሉን ይቀጥላሉ። ገና ከልጅነታቸው ጀምሮ አስተውሎ መራመድንና ጊዜን በዋዛ ፈዛዛ ማሳለፍን የማይወዱት የዚያን ጊዜው የለንደን ዩኒቨርስቲ ተማሪና የዛሬው እውቅ የታሪክ ምሁር የሦስት ዓመት የዩኒቨ ርሲቲ ቆይታቸውን አጠናቀው በሃያ አንድ ዓመታቸው በምጣኔ ሀብት (Economics) የመጀመሪያ ዲግሪያቸውን በማዕረግ ያገኛሉ።
የምጣኔ ሀብት ባለሙያ የሆኑት ወጣቱ ፓንክረስት በተቀዳጁት ውጤት ቢደሰቱም ወደ ሥራ ዓለም ከመግባት ይልቅ ጊዜ ሳያጠፉ ትምህርታቸውን መቀጠል እንዳለባቸው ይወስናሉ ። የትና ምን መማር እንዳለ ባቸው ማሰላሰል በያዙበት ወቅት ታላቅ የምስራች ይደርሳቸዋል። በመጀመሪያ ዲግሪያቸው ያስመዘገቡት ውጤት በቀጥታ ለዶክትሬት (PHD) ዲግሪ የሚያበቃቸውን ትምህርት እንዲማሩ ለንደን ዩኒቨርሲቲ የነፃ ትምሀርት ዕድል ይሰጣቸዋል።
አንብበው የማይሰለቹት፣ ፅፈው የማይደክሙት የዚያን ጊዜው ሪቻርድ ፓንክረስት ጀንበር ወጥታ እስከምትጠልቅ ብቻ ሳይሆን የእንቅልፍ ጊዜያቸውን ሳይቀር ለጥናታቸውና ለትምህርታቸው በመስጠታቸው በአስተማሪዎቻቸው ሳይቀር አንቱታን ያተርፋሉ። እናም በሃያ ዘጠኝ ዓመታቸው በምጣኔ ሀብት ታሪክ (Economic History) የዶክተሬት (PHD) ዲግሪያቸውን እ.አ.አ በ1954 በከፍተኛ ውጤት በመመ ረቅ እነሆ ዛሬ ድረስ ያች በሁለት ዓለም አቀፍ ጦርነቶች መካከል የተፈጠረች ነፍስ በዕውቀትና በክህሎት ገዝፋ ዓለም ዕውቅና የቸራት ለመሆን ችላለች።
በዘር የተላለፈ አርበኝነት
አርበኝነት ፈርጀ ብዙ ነው። አርበኝነት በአውደ ግንባር ይፈጠራል። አርበኝነትን ጠላትን በማንኛውም መገናኛ ብዙኃን በመፋለምም ድል ማግኘት ይቻላል። አገራችን በፋሽስት ኢጣሊያ በተወረረችበት ጊዜ ህዝባችን በዱር በገደሉ መሽጐ ጠላትን ድል እንደነሳ ሁሉ አንዳንድ ዜጐቻችንም በውጭ አገር ሆነው በዲፕሎማሲው መስክ በመሰማራት አርበኝነታቸውን አረጋግጠዋል። በሌላም በኩል አንዳንድ የውጭ አገር ዜጐች ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን በመወገን ዘመን ተሻጋሪ የአርበኝነት ታሪክ አስመዝግበዋል። ለዚህ እውነታ ሁነኛ ማሳያ የሚሆኑት ደግሞ የኢትዮጵያ ህዝብ የቁርጥ ቀን ወዳጅና የፀረ- ፋሽዝም ንቅናቄ ፈር ቀዳጅ ሚስስ ሲልቪያ ፓንክረስት ናቸው፡፡ ይህም ብቻም አይደለም « ዘር ከልጓም» ይስባል እንዲሉ ለኢትዮጵያና ለህዝቦቿ ያላቸውን ፍቅርና ከበሬታ በብቸኛው ልጃቸው አዕምሮ ውስጥ እንዲሰርፅ በማድረጋቸው የዛሬው ፕሮፌሰሩ ልጃቸው ከልጅነት እስከ ዕውቀት በኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ ትኩረት ሰጥተው ያስገኙት ውጤትና የሰጡት አገልግሎት ከዘር የተላለፈ አርበኝነት ሆኖ የሚፈረጅ ነው፡፡
በዚህ ረገድ የዚያን ጊዜው ወጣትና የዛሬው አዛውንት ፕሮፌሰር ከኢትዮጵያና ከህዝቧ ጋር መቼ እና እንዴት እንደተዋወቁ ሲናገሩ « ... በእርግጥ የኢትዮጵያ ተምሳሌቴ እናቴ ናት። በተለይም በዕድሜና በትምህርት እየደረጀሁ ስመጣ እናቴ ስለኢትዮጵያ ታሪክ ትነግረኝ ነበር። ኢትዮጵያ የታሪክ ባለፀጋ መሆኗን ሁሌም ታጫውተኝ ነበር። ኢትዮጵያ በነፃነት የኖረችና ሕዝቧም ለነፃነቱ ተጋዳይ እንደሆነ ትተርክልኝ ነበር። በተለይም ፋሽስት ኢጣሊያ በነፃይቱ አገር ገብቶ እያደረሰ ያለውን ጭፍጨፋም ሀዘን በተሞላበት ሁኔታ ትገልፅልኝ ነበር። ከዚህም ሌላ እናቴ ታዘጋጀው በነበረው 'ኒው ታይም' (አዲስ ዘመን) ጋዜጣ ላይ ኢትዮጵያን የተመለከቱ ጽሑፎችን በማንበብ ኢትዮጵያን ለማወቅ አስተዋፅኦ አድርጐልኛል። ይህ ብቻም አይደለም ዩኒቨርሲቲ ስገባ ኢትዮጵያን የበለጠ የማውቅበት ተጨማሪ መድረክ አገኘሁ። ለንደን ከሚኖሩት ከሐኪም ወርቅነህ ልጆች በተጨማሪ ከነፃነት በኋላ ለንደን ከመጡት ፣ ከመንግሥቱ ለማ፣ ከአፈወርቅ ተክሌ፣ ከሐብተዓብ በአይሩ፣ ከሚካኤል እምሩ ... ወዘተ ጋር ጓደኝነት ፈጠፍኩ። እነዚህ ጓደኞቼ ስለኢትዮጵያ የሰጡኝ ዝርዝር መግለጫ ደግሞ ኢትዮጵያን አቅርበው አሳዩኝ።
« ... እናም የእናቴን ጋዜጣ ከማንበብ ባሻገር የኢጣሊያን ፋሽስታዊ ድርጊት በመቃወም ጋዜጣው ላይ መፃፍ ጀመርኩ። ኢትዮጵያውያን ተማሪዎች በፋሽስት ኢጣሊያን ላይ የሚያወጡትን መግለጫ፣ ስብሰባዎችንና ሰላማዊ ሰልፎችን እየተከታተልኩ ለእናቴ ጋዜጣ መዘገብ ጀመርኩ። ከሁሉም በላይ ደግሞ በአስራ ሰባተኛው ክፍለ ዘመን ጀርመናዊው የታሪክ ሊቅ ሉደልፍ ስለኢትዮጵያ የፃፈውን በማንበብና ለጋዜጣ በሚሆን መልኩ አዘጋጅ ስለነበር ስለ ኢትዮጵያ ያለኝን ዕውቀት የበለጠ አሰፋልኝ። ይህም በመሆኑ ከእናቴ ጋዜጣ በተጨማሪ በምድር ባቡር ሠራተኞች ጋዜጣ ላይም መፃፍ ጀመርኩ። እናም ገና በልጅነት ዕድሜ የቀሰምኩት እውነታ ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያውያንን እንድወድ አድርጐኛል። ከሁሉም በላይ ግን እ አ አ 1951 ከእናቴ ጋር አብሬ በመምጣት ኢትዮጵያን ማየት መቻሌ በሁለንተናዊ መልኩ 'ማየት ማመን ነው' የሚለውን አባባል አረጋገጠልኝ...» በማለት የትናንቱን የሕይወት ጉዞአቸውን ያስታውሳሉ።
ፕሮፌሰር ሪቻርድ ፓንክረስት ትናንት የጀመሩትን የአርበኝነት ፍልሚያ በቀጣይም የህይወታቸው አካል በማድረግ እናታቸው ሚስስ ሲልቪያ ፓንክረስት ኢትዮጵያን ለመኖሪያቸውም ሆነ ለመቀበሪያቸው መርጠው ወደ ኢትዮጵያ ሲመጡ ኢትዮጵያን እንደ እናታቸው በማፍቀር ' አንለያይም' በማለት እ.አ.አ በ1956 አዲስ አበባ ይገባሉ።
ሙሽራው ምሁር
ወጣቱ ዶክተር ሪቻርድ ፓንክረስት እናታቸውን ተከትለው አዲስ አበባ ሲመጡ በቅፅበታዊ ትውውቅ ቢቢሲ ዋና መስሪያ ቤት ፊት ለፊት በሚገኝ አደባባይ ቀጥረው ያናገሯቸው እና በስፔን ሬስቶራንት ራት ጋብዘው ከማፍቀር ባለፈ ለትዳር ከጠየቋት ፍቅረኛቸው ጋር በመለያየታቸው ከአካላቸው ክፍል አንዱን ትተው የመጡ ያህል ሆኖ ይሰማቸዋል። ደግሞም ፍቅር ሩቅ ለሩቅ ሲሆን እንከን እንደማያጣው ያምናሉ። እናም ፍቅረኛቸውን አዲስ አበባ እንዲመጡ ያግባቧቸዋል።
ወጣቷም ጥሪው «ሲሻኝ ጢስ ወጋኝ» ሆነባቸውና ለንደንንተሰናብተው አዲስ አበባ ይገባሉ። ቀንም ሆነ ሌሊት ወደ ለንደን ይጓዝ የነበረው የምሁሩ ዕዝነ ልቦናም መንጐዱን አቆመ። «ሳይደግስ አይጣላም» እንዲሉ ወጣቷ ሪታ አልደን ደግሞ ውለው ሳያድሩ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ የቤተ መጽሐፍት ኃላፊ ይሆናሉ።
ወጣቶቹ የለንደን ልጆች ' የአራዳ ልጆች' ከመሆን ባለፈ ፍቅራቸውን በትዳር ለማጥበቅ ይወሰናሉ። የሠርግ ሥነ ሥርዓታቸውን በእንግሊዝ ኦምባሲ ውስጥ ለመፈፀም ይስማማሉ። ይሁን እንጂ የዚያን ጊዜው ወጣት የምጣኔ ሀብት ታሪክ ምሁር ስለኬንያ ነፃነት፣ ጆሞ ኪንያታ ከእስር እንዲፈቱ፣ አፍሪካውያን የትግል መሳሪያ የሚሆናቸውን የአፍሪካ አንድነት ድርጅት መመስረት እንዳለባቸው የሚያስገነዝቡ ጽሑፎችን ለንደን ይታተም በነበረው ' ዌስት አፍሪካ በሚባል መጽሔትና በአቶ አሀዱ ሳቡሬ ዋና አዘጋጅነት በሚታተመው ፈረንሳይኛና አማርኛ ጋዜጣ ላይ አውጥተው ስለነበር የጥንዶቹ የሠርግ ግብዥ በኤምባሲው ግቢ ውስጥ እንዳይካሄድ በኢትዮጵያ የእንግሊዝ አምባሳደር ይከለከላሉ። እናም የሠርጋቸው ሥነ ሥርዓት በኤምባሲው ቅጥር ግቢ ከተፈፀመ በኋላ የራት ግብዣቸውን በገነት ሆቴል ለማካሄድ ይገደዳሉ።
ሙሽሮቹ ለጊዜውም ቢሆን ገነት ሆቴልን የጫጉላ ቤት ያደርጉታል። ይሁንና በዕድሜ የገፉ እናታቸውን በቅርብ ሆነው ለመደገፍ በማሰብ ኑሮአቸውን በእናታቸው መኖሪያ ቤት ያደርጋሉ። ከእናታቸው ጋር በሰላምና በፍቅር በመኖር ላይ እያሉ ሚስስ ሲልቪያ በፀና ታምመው እ.አ.አ በ1960 ከዚህ ዓለም በሞት ይለያሉ። ዶክተር ሪቻርድ በእናታቸው ሞት ምክንያት መራራ ሀዘን ውስጥ ይገባሉ። በሌላም በኩል የእናታቸው ቀብር ኢትዮጵያውያን ከልብ በመነጨ ሀዘንና በተለይም አፄ ኃይለስላሴ በተገኙበት በታላቅ ሥነ ሥርዓት መፈፀሙን ሲመለከቱ ወገን መሀል መሆናቸውን ያረጋግጣሉ። እናም በጊዜ ሂደት ለእናታቸው ተዘጋጅቶ የነበረውንና ጦር ኃይሎች አካባቢ የሚገኘውን ቤት በመግዛት ወልደው ለመሳም ይበቃሉ።
ተመራማሪው - መሪጌታ
ወጣቱ ሪቻርድ ፓንክረስት የዶክትሬት ዲግሪያቸውን እንዳገኙ እዚያው ለንደን ከተማ በአንድ ታዋቂ ኢንስቲትዩት እና ለንደን ዩኒቨርስቲ በተመራማሪነትና በመምህርነት አገልግለዋል። ይሁን እንጂ እ.አ.አ በ1956 ከእናታቸው ጋር ወደ ኢትዮጵያ ከመጡ በኋላም ለንደን ጀምረውት ከነበረው የሥራ መስክ አልተለያዩም። እናም የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ መምህር ሆነው ሥራቸውን ሲጀምሩ ጊዜ አልፈጀ ባቸውም።
በወቅቱ ስለአዲስ አበባም ሆነ ስለኮሌጁ ስለነበራቸው ስሜት ሲናገሩ « ... ለአጭር ጊዜም ቢሆን አዲስ አበባን የአየኋት በመሆኑ ብዙም ግርምት አልፈጠረችብኝም። በእርግጥ ከአውሮፓ ለመጣ ሰው እንግዳ መሆን የማይቀር ነው። ግን ደግሞ እናቴም ስላለችና ቀደም ሲልም ለንደን ያፈራኋቸው ኢትዮጵያውያን ጓደኞች ስለነበሩኝ ባይተዋርነት አስተሰማኝም። በእርግጥ ገና ባልተደራጀ ኮሌጅ ውስጥ መስራት ችግሩ ውስብስብ ነው። አዲስ አበባ ዩኒቨርሲስቲ ኮሌጅ አደረጃጀቱ ያልተጠናከረ በመሆኑ ክፍተቱን ለመሙላት ተደራራቢ ሥራዎችን መሥራት ግድ ነበር። ይህም በመሆኑ የተለያዩ የትምህርት አይነቶችን ማስተማር ነበረብኝ። በዚህም መሠረት ኢኮኖሚክስ ፣ የዓለም፣ የአፍሪካና የኢትዮጵያ እንዲሁም የግብዕ ታሪክ ሳይቀር አስተምር ነበር። ይህ ሲሆን ግን ያልተማርኩትንና የማላውቀውን የትምህርት አይነት አንብቤ አስተምር ነበር። በወቅቱ የነበረው የሥራ ጫና ደግሞ በሰብዕና ላይ ተጨማሪ ዕውቀት እንዳገኝ አድርጐኛል። ከማስተማሩም ባለፈ ወደ ምርምርና ጥናት እንዳተኩርም አድርጐኛል» በማለት ሃምሳ ስድስት ዓመት ወደ ኋላ ተጐዘው ያስታውሳሉ።
ያም ሆነ ይህ በአፍላ ጉልበታቸው በመምህርነት ከሰጡት የላቀ አስተዋፅኦ ባለፈ ኮሌጁን ወደ ዩኒቨርሲቲ ደረጃ ለማሸጋገር በተደረገው እንቅስቃሴ ሙያዊ ኃላፊነታቸውን ማበርከታቸውን ይናገራሉ። በተለይም እ.አ.አ ከ1956 እሰከ 1976 የሰጡት ወሰን የለሽ ሙያ ተልዕኮ ዛሬ ላይ ሆነው የሚኮሩበት መሆኑን ይናገራሉ። ዶክተር ሪቻርድ ፓንክረስት በመምህርነት ብቃታቸው፣ በጥናትና ምርምር ውጤታቸው የረካው የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ደግሞ የፕሮፌሰርነት ማዕረግ በማጐናፀፍ ማንነታቸውን አዲስ ምዕራፍ ላይ ያስቀምጠዋል።
ፕሮፌሰር ሪቻርድ ፓንክረስት በአብዮቱ ማግስት እ.አ.አ በ1976 ወደ ለንደን በማምራት አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የጀመሩትን ጥናትና ምርምር በኦርየንታልና በአፍሪካን ጥናት ትምህርት ቤት እና በለንደን ዩንሸርስቲ ይቀጥላሉ። እንዲሁም' ሮያል ኤዥያቲክ ሶሳይቲ' ለተባለው ተቋም የቤተመጽሐፍት ኃላፊም በመሆን አገልግለዋል ። ይሁን እንጂ እ.አ.አ በ1986 አዲስ አበባ በመመለስ የመምህርነትና የተመራማሪነቱን ተግባር አጣምረው በማራመድ ለአገራችንም ሆነ ለዓለም አቀፍ ህብረተሰብ የሚጠቅም የጥናትና ምርምር ውጤቶች በመጽሐፍ እያሳተሙ ይፋ አድርገዋል።
ዘመን ተሻጋሪ ስጦታዎች
« ... ምንም እንኳን የእንግሊዝ ፓስፖርት ቢኖረኝም እኔ ግን የዓለም ልጅ ነኝ። ... እናም ዓለም ደግሞ የእኔ አገር ነች» የሚሉት አዛውንቱ ፕሮፊሰር « ...ኢትዮጵያ ደግሞ ለእኔ ልዩና ታሪካዊ አገሬ ናት...» በማለት በልበ ሙሉነት ይናገራሉ። እናም ከልጅነት እስከ ዕውቀት ባለው የሕይወት ዘመናቸው እርሳቸውና ኢትዮጵያ በአካልም በመንፈስም ባለመለያየታቸው ጥናትና ምርምራቸው ሳይቀር ኢትዮጵያን ማዕከል ያደረገ መሆኑን በአፅንኦት ይናገራሉ።
ገና በወጣትነት ዕድሜያቸው በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ በመምህርነት በማገለገል ላይ እያሉ ኢትዮጵያ እልቆ መሳፍርት የሆነውን ታሪኳን የሚፈትሽ አትዮጵያዊ የሆነ የጥናትና ምርምር ተቋም እንደሚያስፈልግ ይወስናሉ። እናም እ.አ.አ በ1963 የኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ኢንስቲትዩትን በማቋቋም ለኢትዮጵያ ህዝብ ታላቅ የማንነት ማረጋገጫ ማዕከል ያበረክታሉ።
«... ኢትዮጵያ ጥንታዊ ታሪክ ያላት መሆኗን የተገነዘብኩት በ17ኛው ክፍለ ዘመን ሉዳልፍ የተባለው ጀርመናዊ የታሪክ ሊቅ ስለ ኢትዮጵያ የፃፈውን ለእናቴ ጋዜጣ በሚሆን መልኩ ሳዘጋጅ ነው። ይሁን እንጂ የኢትዮጵያን የታሪክ ባለፀጋነት የበለጠ ለማወቅ ደግሞ በኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ ብቻ ያነጣጠረ የምርምር ማዕከል አስፈላጊ ነበርና ተግባራዊ አደረኩት። እነሆ ኢንስቲትዩቱም የታለመለትን ዓላማ ዕውን አድርጓል። ኢትዮጵያው ያን ብቻ ሳይሆኑ ዓለም አቀፍ ተመራማሪዎች ሳይቀሩ የኢንስቲትዩቱ ተጠቃሚ ሆነዋል። በሌላም መልኩ በኢንስቲትዩቱ የተቋቋመው ሙዚየም በአገር ገፅታ ግንባታ የማይናቅ አስተዋፅኦ እያበረከተ ነው። ቤተ መጽሐፍቱም ኢትዮጵያን ለማጥናትና ለመመራመር ሁነኛ መሳሪያ ሆኖ እያገለገለ ነው። ያም ሆነ ይህ ኢንስቲ ትዮቱ በውስጤ የነበረውን ምኞትና ፍላጐቴን በሕይወት ዘመኔ ተግባራዊ ሲያደርግ በማየቴ ኩራት ይሰማኛል።» በማለት የኢንስቲትዩቱ መስራችና ለአስራ ሁለት ዓመት በዳይሬክተርነት ስለመሩት ዘመን ተሻጋሪ ስጦታ ይናገራሉ።
ፕሮፌሰሩ ሪቻርድ ፓንክረስት ለኢትዮጵያ ሕዝብ ያበረከቱት ገጸ በረከት ኢንስቲትዩቱ ብቻ ሳይሆን ለአገራችን ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የመማሪያና እና ለዓለም አቀፍ ተመራማሪዎች ደግሞ ማጣቀሻ የሚሆኑ ከሃያ ሁለት በላይ መጽሐፍትን ለሕትመት አብቅተው ለትውልድ ሁሉ የሚተላለፉ ህያው ቅርስ አበርክተዋል። ይህ ብቻም አይደለም ከ400 በላይ የተለያዩ የምርምር ጽሑፎችን በመፃፍ ለዓለም አቀፉ ህብረተሰብ ለንባብ አብቅተዋል። እ.አ.አ ከ1956 ዓ.ም ጀምረው በመምህርነት፣ በጥናት ምርምር ውጤታቸውና ክህሎታቸው በፕሮፌሰርነት ማዕረግ ያበቃቸው የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መጠነ ሰፊ ለሆነው ምሁራዊ አስተዋፅኦአቸው የክብር ዶክትሬት (PHD) ዲግሪ አበርክቶላቸዋል።
በኢትዮጵያ ጉዳይ ላይ ጥናትም ምርምር በማድረጋቸውም ከአፄ ኃይለሥላሴ የሽልማት ድርጅትና ከእንግሊዝ መንግሥት የወርቅ ሜዳሊያና ኒሻን ተሸላሚ የሆኑት እኒህ የአገር መከታ በቅኝ ገዥዎችና በፋሽስት ኢጣሊያ የተዘረፈ ታሪካዊ ቅርሶችን በማስመለሱ ረገድም በፊታውራሪነት ተሰልፈው ውጤት አስመዝግበዋል። ለዚህም የተዘረፉ ቅርሶችን ለማስመለሰ ከሌሎች ኢትዮጵያውያን ጋር በመሆንና በፊታውራሪነት በመሰለፍ የአክሱም ሐውልትን ፣ የአፄ ቴዎድሮስ ክታብን ፣ ታቦትና ታሪካዊ የብራና ፅሑፎችን፣ ጋሻና ጦርን ... ወዘተ የመሳሰሉት ታሪካዊ ቅርሶች ለአገራቸው እንዲበቁ በማድረግ ሕዝባችንን ከዘመናት ፀፀትና ቁጭት እንዲላቀቅ አድርገዋል፡፡ ይህን በማድረጋቸው እንደ አርበኛዋ እናታቸው ከኢትዮጵያና ከህብረተሰቡ ከበሬታን ከመጐናፀ ፋቸው ባለፈ እርሳቸውም በልጅነት የጀመሩትን አርበኝነት ዛሬም ገናና ሆኖ እንዲታይ አድርገዋል።
አዛውንቱ ፕሮፌሰር
ፋሽስት ኢጣሊያን ገና በልጅነት ዕድሜያቸው በጽሑፋቸው የተፋለሙት ትንታጉ የለንደኑ ቡቃያ ዛሬ የሰማኒያ አምስት ዓመት የዕድሜ ባለፀጋ ሆነዋል። ከዚሁ የህይወት ዘመናቸው ከሃምሳ አምስት ዓመት በላይ የሆነውን የዕድሜያቸውን ክፍል ደከመኝና ሰለቸኝ ሳይሉ ዕውቀታቸውንም ሥነ ጉልበታቸውን ለኢትዮጵያ እና ለሕዝቦቿ ዕድገት አበርክተዋል።
እነሆ የተፈጥሮ ሕግ ሆነና እኒህ የአገር ባለውለታ ዛሬ እርጅና ተጫጭኖአቸዋል። ይሁን እንጂ የእርሳቸው ውጤት የሆኑት የኢትዮጵያ ጥናትና ምርምር ኢንስቲትዩት፣ እንዲሁም መማሪያና ማጣቀሻ የሆኑት መጽሐፍ ቶቻቸው የዛሬው አዛውንት ዘላለማዊ ወጣት አድርገው ያሳዩአቸዋል።
ፕሮፌሰር ፓክረስት እንደ እናታቸው ሁሉ ከኢትዮጵያ ጋር ያላቸው ቁርኝት ወሰን የለሽ ነው። ቤተሰ ቦቻቸውም እርሳቸው ከሚጓዙበት ፈር አላፈገፈጉም።
******************************
http://www.ethpress.gov.et
ሪፖርተር ዋካ ይርሳው
ቀን 2012

ማሞ ካቻ (አቶ ማሞ ይንበርብሩ)

  አቶ ማሞ ይንበርብሩ (ማሞ ካቻ) እስቲ እናስታውሳቸው፣ ተቀብሮ እንዳይቀር አኩሪ ታሪካቸው  (ደረጀ መላኩ)   አቶቢሲ ማሞ ካቻ የት ትሄዳለህ? ገብረ ጉራቻ… ታዳጊው ማሞ ይንበርበሩ ገና በጨቅላ እድሜው አባቱ አቶ...