ዓርብ, ማርች 18, 2016

ከመጻሃፍት ዓምባ

እንዳለጌታ ያቆመው የበዓሉ ግርማ ሀውልት _ደረጀ በላይነህ

*********************************************************************
 በዓለም ታሪክ፣በትውልድ ሰማይ ላይ የፈኩ፣ የማይረሱ ኮከቦች አሉ፣በሰው ልብ የሚነበቡ በጠመኔ ተጽፈው የሚነድዱ፡፡ ዘውድ-አልባ ነገስታትም እንደዚሁ! … ታላላቅ ፖለቲከኞች፣ ደራሲያንና ሳይንቲስቶች ዘመን ዘልቀው፣ አድማስ ርቀው ይታያሉ፡፡ ታዲያ እነዚህ ብርቅዬዎች  እንደሚቆረጠም እንባ፣እንደሚፈለጥ ደም እንቆቅልሽ ሆነው፣ አሊያም በታሪካቸው ድምቀት እንደ ገነት አበባ በጽድቅ አረፋ ተሞሽረው ከወረቀት ወደ ልባችን ሊመጡ ይችላሉ-እንደየዕጣቸው፡፡
እኛ ሀገር የጥበብ ብርሃን ከፈነጠቁት፣ ዕውቀትና ውበት እንደ ሽቶ ካርከፈከፉት፣ግን ደግሞ በእንባ ሸለቆ ውስጥ በሰቀቀን ዐመድ ለብሰው ከቀሩት መሀል ደራሲ በዓሉ ግርማ አንዱና ደማቁ ነው፡፡ በዓሉ በመጽሐፍቱ በነፍሳችን ጎጆ የቀለሰ፣ በልባችን በፍቅር የታተመ ታላቅና ተወዳጅ ደራሲ ነው፡፡ ምናልባትም አንዳንዶቻችን ውስጥ በጥበብ እርሻ የዘራና የወለደ አባት ነው፡፡
ታዲያ መቃብሩን ያላየነው፣በነፍሳችን እየባዘንን በትካዜ ፉጨት የፈለግነውን ይህን ደራሲ ወጣቱ ፀሐፊ እንዳለጌታ ከበደ አራት ዓመታት ያህል ከሕይወቱ ቆርሶ ሮጦና ላቡን ጠብ አድርጎ፣ ካገር አገር ተንከራትቶ አዲስ ዱካ፣ በ440 ገጾች ጠርዞ “በዓሉ ግርማ ሕይወቱና ሥራዎቹ” በሚል ርዕስ ይዞልን መጥቷል፡፡
ይህ መጽሐፍ በዓሉ ግርማ ለህፃንነቱ የተሰጠውን የተፀውዖ ስም መነሻና ትርጉም በማነፍነፍ ያልገመትነውን መልስ ሁሉ የሚሰጥ ነው፡፡ “በዓሉ” ማለት ምንድነው? … በምን ቋንቋ ወዘተ … ብሎ የሚነግረን ከግምታችን ራቅ የሚል ነው፡፡ የበዓሉ አባት ማናቸው? … ግርማስ ማነው? … የሚለው ጥያቄ መልስ ከዚህ ቀደም በመገናኛ ብዙኃን ከተወሩት ፈቀቅ ይላል! …
ሱጴ ቦሮ የተወለደው በዓሉ ግርማ በበርካታ መጽሐፍቱ በውበት የሚጋልባቸው የአማርኛ ቃላትና ዐረፍተ ነገሮች አንደበቱ ሳይገቡ በፊት የስነ ትምህርት ምሁራን “የአንደኛ ደረጃ ት/ቤት ዕድሜ” በሚሉትና የሥነ ልቡና ምሁራን “gang age” የቡድን ዕድሜ በሚሉት መሟጠጫ ከኦሮሚፋ በስተቀር አንዳች መናገር ሳይችል ነበር አዲስ አበባ የመጣው-በ14 ዓመቱ፡፡ አዲስ አበባ ከመጣ በኋላ ሕንዳዊው አባቱ ያቀጨመበት ፊት፣ የሕንዳዊው ሰራተኛ የሆነው ተቀጣሪ በዓሉን በፍቅር ለማሳደግ ሲወስደው፣ ከገጠር /ከሱጴ ቦሮ/ የመጡት ሰዎች ጥለውት ሲሄዱ፣  … ለከተማው ባይተዋር የሆነ ልጅ በማያውቀው ከተማና አውድ፣ በማያውቀው ማህበረሰብ ውስጥ ለብቻው ሲቀር ምሽቱን እንዴት ያድር ይሆን? … ለኔ ከባድ የሕይወት ፈተና ይህ ነው፡፡  በዓሉ ግርማ ይህንን ፅዋ ቀምሷል፡፡ልጅነቱ ምስቅልቅል፣ ስነ-ልቡናው ዝንጉርጉር ነው፡፡  የበዓሉ ግርማ የሕይወት ታሪክ መጽሐፍ በሰለጠነውና በተሻለው የአፃፃፍ መንገድ የተፃፈ ነው፡፡ የህይወት ታሪክ አፃፃፍ፣ በአርስጣጣሊስ ዘመን ተጀምሮ በአፍላጦን እየዳበረ ሺህ ዓመታት  ይግፋ እንጂ በእንግሊዝኛ “Biography” የሚለውን ቃል አብሮ የተጠቀመው እንግሊዛዊ ገጣሚ ጆን ድራይደን ነው፡- በ1683 ዓ.ም፡፡ ታዲያ ይዘቱም የተለየ ስራ የሰሩ ሰዎችን ታሪክ የሚተርክ ነበር፡፡ “The History of practical men’s lives” ይህም ማለት አንደኛ ስራ የሰሩ፣ የጎላ ታሪክ፣ የዳጎሰ ትዝታ ያላቸውን ማለት ነው፡፡
እንዳለጌታ ከበደ ከዚህኛው ወደዘመነው ከሃያኛው ክፍለ ዘመን፣ ወዲህ በተጀመረው የህይወት አፃፃፍ ይትበሃል በመጠቀም የባለታሪኩን አካላዊ ብቻ ሳይሆን ስነ ልቡናዊና ማህበራዊ፣መልክዐ-ምድራዊ ዐውድ ሳይቀር ፈልፍሎ በማውጣት፣ ሰውየውን እንደ ስጋ ለባሽ እንጂ እንደ መለኮት በማይታይበት ሁኔታ ጽፎታል፡፡
ለመርማሪ አንባቢ ገና የሚዘረዘሩና የሚላጡ ትንተናዎችን የሰጠ ይመስለኛል፡፡ በርግጥም ከአንደኛው የዓለም ጦርነት በኋላ የሕይወት ታሪክና የግለ ታሪክ አፃፃፍ መልክ በዚህ ተቀይሯል፡፡ ግን ደግሞ በሃገራችንስ የጻፉ ሁሉ መች ተጠቀሙበት!...እንዳለጌታ ግን የእንስትዋ ፀሐፊ ዶክተር ካትሪኒ ሀንተርን መርህ ተግባራዊ አድርጓል፡፡ የልጅነት ሕይወትን መዳሰስ ግድ እንደሚል ያሰመሩበትን ደመቅ አድርጎ ተጠቅሞበታል፡፡
 መረጃ ፍለጋ ጓዳ ጎድጓዳውን ባክኗል፣ የበርካታ ቢሮዎችን ደጃፍ ረግጧል፡፡ አያሌ ሰዎችን ደጅ ጠንቷል፡፡ … የህይወት ታሪክን የሚፅፍ ሰው ችግሮች ከሚቸገርባቸው ነገሮች አንዱ ታሪኩ የሚፃፈው ሰው በህይወት ያለመኖር ነው፡፡ ለምሳሌ በዓሉ ግርማ በሕይወት ቢኖር እንዳለጌታ ከበደ ብዙ ቦታ የሮጠባቸውን ሀሳቦች በቀላሉ ያገኝ ነበር፡፡ ሌላው ቀርቶ የዕለት ማስታወሻዎች፣ ሰዎች ጋር የቀሩ ጽሑፎች፣ የግል ገጠመኞች፣ ውስጣዊ ሕልሞችና ሌላ ሰው ያልሰማቸው ፈተናዎች ሊኖሩ ይችላሉ፡፡
ይሁንና እነዚህን ሁሉ ዋጋ ከፍሎ ሰርቷቸዋል፡፡ ለምሳሌ በመጽሐፉ ውስጥ የተካተተው የተወዳጅዋ ድምፃዊት ብዙነሽ በቀለና የበዓሉ ግርማ አስደማሚ የፍቅር ታሪክ ትልቅ ቦታ የሚሰጠው ነው፡፡ ትልቅ ቦታ የሚሰጠው ነው፡፡ በእጅጉ የሚደንቅና የሚያጓጓ የታላላቅ ሰዎችን ተሰጥዖና ክህሎት ያለፈ ማንነት ጉልህ አድርጎ የሚያሳይ፣ ልብን በፈገግታ ሻማ የሚለኩስ ነው፡፡ ምናልባትም መጽሀፉ ውስጥ ያሉትን አሳዛኝ ድባቦች ወደ ፍልቅልቅ የፍቅር አውድ የሚቀይር ነው፡፡ ለኔ ልዩና ድንቅ ነው፡፡
ለምሳሌ ስለዚህ ዕጹብ-ድንቅ ፍቅር እንዳለጌታ ኢየሱስ ወርቅ ዛፉን አነጋግሯቸው እንዲህ ብለውታል፡-‹‹ሁለቱ እጅ ለእጅ ተያይዘው፣እንደ ጣሊያኖቹ …በየመንገዱ ሲላፉ፣ ሲሳሳቁ…  በሚያስቀና ስሜት ሆነው በርጋታ ወክ ያደርጉ እንደነበር ሁልጊዜ ትዝ ይለኛል-የእሷን ዘፈን በሰማሁ ፣የእሱን መጽሃፎች ባነበብኩ ቁጥር›› (ገጽ 121)
እንደ ባለ ህልም እንዳለጌታ ከጊዜ ጋር ባይሽቀዳደምና ዛሬ እማኝነት የሰጡ ሰዎች ቢያልፉ ኖሮ ይህ ድንቅ እውነታ ከእግራችን ሥር ሾልኮ - ነበር፡፡ ኪሮስ ወልደሚካኤልን አስሶ ማግኘቱ የሚያስመሰግነውና የሚያስደንቀው ነው፡፡ ሊመሰገንና ሊደነቅ ይገባል! ከላይ እንደጠቀስኩት የተሻሻለው የሕይወት ታሪክ አፃፃፍ የግለሰቦችን ታሪክና አካባቢ ብቻ ሳይሆን እግረመንገዱን የዘመኑን ማህበረ-ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ መልክ፣ የማህበረሰብና የህብረተሰቡን እምነትና ሥነ ልቡና ስለሚያሳይ ከበዓሉ ህይወት ጋር አጣምረን የኢትዮጵያን ውስጣዊና ውጫዊ ሥዕል ቃኝተናል። ለታሪኩ ምስክር ይሆኑ ዘንድ የተመረጡትን ጎምቱ የሀገር ልጆች አስተሳሰብና ስነ - ልቡናም ገምግመናል፡፡
በመጽሐፉ ውስጥ በዓሉ ግርማ ሰው ነው፤ በዓሉ ደራሲ፣ ጋዜጠኛ፣ ባለስልጣን ነው፡፡ በዓሉ ዝነኛ ነው፣ በዓሉ ምስኪንም ነው፡፡ ለምሳሌ ከብዙነሽ በቀለ የፍቅር ጉዞ በኋላ የልጆቹን እናት ወ/ሮ አልማዝ አበራን ሲያገባ ገንዘብ አጥሮት ከመስሪያ ቤቱ ብር ተበድሮ ደግሷል፡፡ ይህንን ደግሞ ያደረገው ለባለቤቱ ካለው ታላቅ ፍቅር የተነሳ ነበር፡፡ ባለቤቱ ከቀደመው ባለቤቷ ልጆች ያሏት ቢሆንም ያገባት ግን በልጃገረድ ወግ ነበር፡፡ … በዓሉ ድንቅ ሰው ነው፡፡ ገጽ 129 ላይ እንዲህ ይላል። ‹‹ያኔ የጋብቻ ስነ-ስርዐታቸው የተፈጸመውና አልማዝ የተሞሸረችው ‹በልጃገረድ ደንብ ነው› በልጃገረድ ደንብ መሆኑ በዘመኑ የነበሩትን ያስገረመና በዓሉ ለአልማዝ ያለውን ፍቅር በገቢር የገለጠበት ነበርም ይባላል፡፡…” እንዳለጌታ ከበደ የበዓሉን የህይወት ታሪክ ሲፅፉ በዘመን አንጓ ሸንሽኖ ነው፡፡ ለምሳሌ ከልጅነቱ እስከ ጉብዝናው ያለውን “ማለዳ” ብሎታል፡፡ ከማህበራዊ ህይወቱ እስከሙያዊ አበርክቶቱ ያለውን ቀትር “የሚል ስያሜ ሰጥቶታል፡፡ “ምሽት” (ሩቅ አልሞ ቅርብ ያደረው ቀዩ ኮከብ) ወዘተ እያለ ተርኮታል፡፡
እንደደራሲ በዓሉ የፃፋቸውን ስድስት ያህል መፃህፍት ለመተንተን ሞክሯል፡፡ በተለይ “የሕሊና ደውል” እና “ሀዲስ” የሚመሳሰሉበትንና የሚለያዩበትን መንገድ ጥናታዊ ጽሑፎችን ዋቢ አድርጎ አሳይቷል። በህይወቱ ላይ ጣጣ ያመጣውን “ኦሮማይ”ን፣ የደራሲነትን ህይወት ፍንትው አድርጎ የሚያሳየውን “ደራሲው”ን ከ “አድማስ ባሻገር”ንና በመስሪያ ቤት ባላንጣዎቹ ዳግም እንዳይታተም ዕድል የተነፈገውን “የቀይ ኮከብ ጥሪ”ን በሚገባ ቃኝቷቸዋል፡፡
ሌላው እንዳለጌታ አንባቢዎቹን የሞገተበት ጉዳይ በዓሉ ግርማ በውኑ አለም ያሉትን ሰዎች ቀድቶ ይጠቀምባቸዋል  የሚለውን ሀሳብ ነው። ለዚህም በዓሉ ግርማ ብቻ ሳይሆን በሀገራችን ሀዲስ አለማየሁ፣ ጳውሎስ ኞኞና ብርሃኑ ዘርይሁን መሰል ልምምድ እንደነበራቸው ማስረጃ ጠቅሷል፡፡ ያ ብቻ ሳይሆን በዓሉ አንድን ሰው በቀጥታ መውሰድ ሳይሆን፣ ከአንድ ሰው አንድ ነገር ቢወስድም፣ ታሪኩ ውስጥ በሚኖረው ቦታና ሚና ግን የዚያን ሰው ህይወት ወርሶ እንደማይኖር አስረድቷል፡፡ እኔም በዚህ ቦታ እንዳለጌታን እደግፈዋለሁ፡፡ ትልቁ ሌዎ ቶልስቶይስ ቢሆን ዙሪያውን ያሉ ሰዎችና ቤተሰቦች አይደል ገፀ ባህሪ አድርጎ የሳለ! … ምርጡ አሜሪካዊ ደራሲ ኧርነስት ሄሚንግዌይ! … ኖቤል የተሸለመው‘ኮ ኩባ ባህር ዳርቻ ያለውን ዓሳ አጥማጅ ሕይወት ሥሎ ነው። ኧረ ብዙ አሉ! … እንዳለጌታ ግን በድፍኑ ሳይሆን፣ በተለይ “ኦሮማይ” ላይ ያሉትን ገፀ ባህሪያት ተንትኖ ያሳያል፡፡ ለምሳሌ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የሥነ ፅሑፍ መምህር የነበሩት አቶ ብርሃኑ ገበየሁ ያቀረቡትን በገፅ 191 እንዲህ ጠቅሷል፡-
…በህይወት ከሚገኙ ሰዎች ባህሪዎቻቸውን የሚቀዱ ደራሲያን ብዙ ናቸው፡፡ እነዚህ ሰዎች ያንን ሰው ወደ ስነ ጽሑፍ እንዳለ ሊያመጡት ግን አይቻልም፡፡ ግን ከዚያስ ነው? ደመቅ ያለው ክፍል ጎልቶ ስለሚታየው ለማንፀሪያነት ይወስዳሉ፡፡ አንዳንዴ የሰውየውን የሕይወት ታሪክ መታገጊያና ዳራ አድርገው ይነሳሉ ግን ያን ሰውዬ እነሱ እንዳዩት ነውን’ጂ፣ ያ ሰውዬ እንደሆነ ነው አይደለም፡፡…” እያሉ ይቀጥላሉ ብርሃኑ ገበየሁ፡፡
“በዓሉ ግርማ ህይወቱና ሥራዎቹ” በሚለው መጽሐፉ ውስጥ ቁልፉ ምዕራፍና ክፍል “ውድቅት፤ ተወንጃዮቹና እንደሙሴ መቃብሬ አይታወቅ” የሚሉት ናቸው፡፡ ውድቅት እንደስሙ ነው፡፡ ሌሎቹ ሁለቱም ፅሁፎች በዓሉ ግርማ ብቻ ሳይሆን ራሱ ፀሐፊው መረጃ ለማግኘት የዳከረበት፣ ግራ የተጋቡ የተሳከሩ መረጃዎች አንጎል የሚንጡበት ነው፡፡ በተለይ በተለያዩ ጊዜያት በተለያዩ ሰዎች የተሰጡን መረጃዎችን እነ ጓድ መንግስቱ ኃይለማርያምም ሸምጥጠው የካዱትን ነገር ፍጥጥ አድርጎ የሚያጋልጠው፣ የበዓሉ ግርማ በማዕከላዊና “ቤርሙዳ” ውስጥ መታሰሩንና መንገላታቱን የሚያሳዩ መረጃዎች መገኘታቸው ጉድ የሚያሰኝ ነው፡፡ ተረፈ ዘመድአገኘሁ የተባለው ሾፌር በገጽ 380 ላይ ምስክርነቱን ሲሰጥ፤ ፡-‹‹በዓሉ ግርማን ከማዕከላዊ ወደ ቤርሙዳ ሶስት ጊዜ አመላልሼዋለሁ፤ከዚያ በኋላ ደግሜ አላገኘሁትም፤››ብሏል፡፡
ይህ ደግሞ ቀደም ሲል የተያዘ ቀን ተገድሏል የሚለውን ግምት ለውጧል፡፡ አዲስ ጥሬ መረጃ ይሏል እንዲህ ነው፡፡
በተለይ “እንደሙሴ መቃብሬ አይታወቅ” የሚለው ክፍል እንዳለጌታ ሰነድ የፈተሸበትና በኢትዮጵያ ምሁራን ላይ በግፍ የተፈፀመውን ግፍና መከራ ቁልጭ አድርጎ ያሳየበት ነው፡፡ በተለይ የተረፈ ዘመድ አገኘሁና የኪሮስ ወልደማርያም ምስክርነት፣ የበዓሉን በማዕከላዊ እሥር ቤት እንዲሁም በቤርሙዳ መጉላላት - እስከነፍፃሜው ቁልጭ ያለ ማስረጃ ይሰጣል፡፡
ፀሐፊው በዚህ ምዕራፍ እነ ደራሲ አበራ ለማ የሰጡትን እማኝነት ፉርሽ የሚያደርግ ሀሳብ ማግኘቱ በይፋ ካሳየ በኋላ መረር ብሎ ይሞግታል፡፡ እዚህ ምዕራፍ ላይ ብቻ ሳይሆን በመላው መጽሐፉ ውስጥ በርካታ ጥርጣሬዎችንና መረጃዎችን በድፍረትና በምክንያት ያስጎነብሳል፡፡
በዚህ መጽሐፍ ጠንከር ያለ በራስ መተማመን በማየቴ ተደንቄያለሁ፡፡ … በዕውቀት ማደግ መበልፀግ ማለትም ይህ ነው፡፡ የመጽሐፉ ደራሲ እንዳለጌታ ከበደ ከመጀመሪያዋ ገፅ ጀምሮ እስከ መጨረሻዋ ገፅ ድረስ ላቡን ጠብ አድርጎ፣ አምጦና ደክሞ፣ ወጥቶ ወርዶ ነው የሰራው፡፡ ከታች ካለው የማህበረሰብ ክፍል እስከ ቀድሞ የሀገሪቱ ምክትል ፕሬዚዳንት ፍስሀ ደስታ ድረስ መሰላሉን እየረገጠ ተጉዟል፡፡ (በታሪኩ መሟጠጫ ጊዜ ፍስሀ ደስታ ከመንግስቱ ኃይለማርያም ቀጥለው የሀገሪቱ ከፍተኛ ባለስልጣን ነበሩ፡፡)
በአጠቃላይ የእንዳለጌታ አዲሱ መጽሐፍ የልቦለድን ያህል ልብ የሚሰቅል፣ ጣዕም ያለው፣ ቀልብን የሚስብ፣ እንብርት የሚቆነጥጥ ስሜት ያለው፣ ጥልቅ ምርምር የተደረገበትና ግሩም ነው፡፡
እንደ ብርቱ የህይወት ታሪክ ፀሐፊም ፎቶግራፎችን፣ የተለያዩ ደብዳቤዎችን፣ ጋዜጦችንና መጽሔቶችን፣ መጽሐፍትንና ቃለ -ምልልሶችን ወዘተ ለግብዓትነት ተጠቅሟል፡፡ በአካባቢ ገለፃዎችም ሳይቀር ሥነ ልቡናዊ ምስሎችን ፈልፍሏል፡፡ በጥቅሉ በኢትዮጵያ የስነ ጽሑፍ ታሪክ ውስጥ ታላቅ የባለውለታነት አሻራውን አትሟል፡፡
ጥቂት ቢስተካከሉ የሚባሉ መጠነኛ የሃሳብ ድግግሞሽ፣ የቃላትና የገለፃ ምርጫ፣ ባይካተቱ ጥሩ ነበር የምንላቸው እጅግ ጥቂት ነገሮች አሉ፡፡ በተለይ ደግሞ ማንነታቸው ሳይጠቀስ የቀረቡት ሰዎች ጉዳይ አንባቢን ግራ ያጋባል፡፡ ለምሳሌ ገጽ 389 ላይ ‹‹ወሰን ሰገድ ገብረ ኪዳን››ይላል፡፡ ወሰን ሰገድ የቱ!...ጋዜጠኛ ቢባል፣ ቢቻል ከሰራቸው ስራዎች ጋር ቢጠቀስ! ይሁንና ይህን ትልቅ ስራ ላየ ሰው፣ እንከኖቹ ከቁብ የሚገቡ አይደሉም፡፡ በጥቅሉ እጅግ የምንወደውንና እንደ እግር እሳት የሚያንገበግበን ውድ ደራሲ አባታችንን ታሪክ ለዚህ ወግ ማዕረግ በማብቃቱ ለእንዳለጌታ ያለኝ ፍቅርና አክብሮት በእጅጉ ጨምሯል! ነፍስህን በሀሴት የሚያጠግብ ሲሳይ ይስጥህ! … እላለሁ፡፡ በድንጋይ ሳይሆን በልባችን ውስጥ በደም ስለቆመው ጀግና ደራሲ ሀውልት እንዳለጌታ ባለውለታ ነህ! … እ - ሰ -ይ! 
*******************************************************************************
http://www.addisadmassnews.com/

ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ

ማሞ ካቻ (አቶ ማሞ ይንበርብሩ)

  አቶ ማሞ ይንበርብሩ (ማሞ ካቻ) እስቲ እናስታውሳቸው፣ ተቀብሮ እንዳይቀር አኩሪ ታሪካቸው  (ደረጀ መላኩ)   አቶቢሲ ማሞ ካቻ የት ትሄዳለህ? ገብረ ጉራቻ… ታዳጊው ማሞ ይንበርበሩ ገና በጨቅላ እድሜው አባቱ አቶ...