ዓርብ, ማርች 18, 2016

የአምባሳደር ዘውዴ ረታ "የኤርትራ ጉዳይ በቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዘመነ መንግስት"


"የኤርትራ ጉዳይ በቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዘመነ መንግስት" የተሰኘው መፅሃፋቸው ይዘት ፣ መፅሃፉን ለመፃፍ የተከተሉት አካሄድና ስለመፅሃፉ የምሁራን አስተያየት።
*****************************************************
"ስለ ኤርትራ ጉዳይ አዘጋጅቼ የማቀርበው ይህ መፅሃፍ በቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዘመን የነበረውን ታሪክ የሚገልፅ ስለሆነ፣ ከጥቂት አመታት በፊት ከኢትዮጵያዊ ቤተሰብነት ወደ ጎረቢትነት የተለወጡትን የዛሬዎቹን ኤርራዊያኖችንና ዛሬ ያሉበትን ሁኔታ አይመለከትም። ኤርትራዊያኖች እናታቸው ከነበረችው ከኢትዮጵያ ለመለየት ስለደረጉት ረዥም ጉዞና በመጨረሻም ነፃነትን ለመቀዳጀት እንዴት እንደበቁ ታሪካቸውን ፅፈው እስኪያቀርቡልን እንጠብቃለን። ከዚያ በፊት ግን የኢትዮጵያና የኤርትራ ህዝቦች እውነተኛውን ጉዳይ በትክክል ሊያውቁት የሚገባ የሀያ አመታት የታሪክ ሂደት አለ። ይህወም፤

  1. [በኃይለሥላሴ ዘመነ መንግስትበኤርትራ ውስጥ እጅግ አብዣኛው ሕዝብ፣ ከባዕድ አገዛዝ ለመላቀቅና ኢትዮጵያዊነቱን ለማስመለስ፤ "ኢትዮጵያ ወይ ሞትብሎ መከራና ፈተና እየተቀበለ ምን ያህል እንደታገለ፤
  2. የቀዳማዊ ኃይለሥላሴ መንግስት ኤርትራን ከኢትዮጵያ ጋር ለማዋሃድ፤ በኃያላን መንግስታቶች ዳኝነት እና በተለይ በተባበሩት መንግስታት ድርጅት ለብዙ አመታት ያደረገው ፋታ የሌለው ሙግት እስከ ምን ድረስ እንደነበረ፤
  3.  በአለም ማህበር ሸንጎ ላይ ኤርትራ በፌደሬሽን ከኢትዮጵያ ጋር እንድትቀላቀል ፍርዱ እንዴት እንደተወሰነና፤ ከዚያም ለአስር አመታት የተካሄደው የፌደሬሽን አስተዳደር በምን መልክ ይሰራበት እንደነበር፣ ሁዋላም በምን አኩዋሁዋን እንደፈረሰ፤
እውነተኛውን ታሪክ የኢትዮጵያ እና የኤርትራ ህዝቦች አውቀውት የየራሳቸውን አቁዋም መያዝ ይገባቸዋል ብዬ ስለመንኩ፣ ባለኝ አቅም እውቀት የየራሳቸውን አቁዋም መያዝ ይገባቸዋል ብዬ ስለመንኩ፣ ባለኝ አቅም ለዚህ ጉዳይ ምርምርና ጥናት ብቻ የሰባት አመታት ጥረት አድርጌአለሁ።

የአፄ ዮሐንሥ ዘመነ መንግስት ካበቃ ከስልሣ አመታት በሁዋላ፣ በኢትዮጵያ እጅ የነበረው የኤርትራ ጉዳይ፣ ትክክለኛውና እውነተኛው ስዕል፣ ለዛሬውና ለመጭው ትውልድ በሀቅ ካልቀረበ፣ የመገንጠሉና ለነፃነት የተደረገው ውጊያ ብቻውን ብዙ ሺህ ጊዜ ተራብቶ ቢፃፍ፣ ታሪኩን የተሟላ አያደርገውም።

እኔም የኤርትራን ታሪክ አንድ ቀን መፃፍ አለብኝ የሚል ሀሳብ ያሳደረብኝ በህይወቴ ዘመን ምን ጊዜም ያልረሳው አንድ ትዝታ አለኝ።

እንደ ኤውሮፓ አቆጣጠር በመስከረም 1953 አም በጋዜጣና ማስታወቂያ መስሪያ ቤት የአዲስ አበባ ራዲዮ ወሬ አንባቢና ሪፖርተር ሆኘ ስቀጠር እድሜየ አስራ ስምንት አመት ነበር። ስለ ዜናዎች አስባሰብና አቀራረብ በዚያን ጊዜ ለራዲዮ የአማርኛ ዜና አዛጋጅ ከሆኑት ከአቶ አስፋ ይርጉ ዘንድ በመለማመድ ለስድስት ወራት ከቆየሁ በሁዋላ፣ በክቡር አቶ መኮንን ሀብተወልድ ትእዛዝ የቤተመንግስት ዜና ሪፖርተር እንድሆን ተመደብኩ። በዚሁ በአዲሱ መደቤ ያጋጠመኝ የመጀመሪያው የሪፖርተርነት ስራ፣ ንጉሠ ነገሥቱ የኤርትራን ቺፍ ኤግዚኩቲፍ ደጃዝባች ተድላ ባይሩን አስጠርተው ማነጋገራቸውን የሚገልፅ ዜና ማዘጋጀት ነበር። በተሠጠኝ መምሪያ መሰረት ገነተ ልዑል ቤተ መንግስት በመገኘት ያየሁበትን ፅፌ [መጠነኛ በሻሻል ተደርጎበትአቀረብኩ።

... በፌደረሽኑ ጊዜ የኤርትራ ቺፍ እግዚኩቲፍ አዲስ አበባ በመጡ ቁጥር፣ ከአውሮፕላን ጣቢያ ጀምሮ እስከ ቤተ መንግስቱ የሚደረገውን የፕሮቶኮል ጀብ ጀብ በምን ምክንያት እንደሆነ ለማወቅ [ፍላጎት] ከዚያን ዘመን ጀምሮ በአእምሮዬ ላይ ተቀርፆ ቀረ።

በፓሪስ የጋዜጠኝነት ሞያ አጥንቼ ከተመለስኩ በሁዋላ ለአስር አመታት በማስታወቂያ ሚንስቴር፣ ለአምስት አመታት በውጭ ጉዳይ ዲፕሎማሲ ስራ ባገለገልኩበት ዘመን፣ የኤርራን ጉዳይ በሰፊው ተከታትያለሁ። እንደ አውሮፓ ዘመን አቆጣጠር 1962 አም የኤርራ ፌደሬሽን ሲፈርስ በጋዤጠኝነት አስመራ ተልኬ ሁሉንም አይቻለሁ። ከክዚያም በሁዋላ በኤርትራ ጉዳይ ከፍተኛ ሚና የተጫወቱትን የኢትዮጵያንና የኤርትራን ታላላቅ ሰዎች እያናገርኩ የታሪኩን አካሄድ በየመልኩ በዝርዝር ለማጥናት ጥሩ እድል አጋጥሞኛል።
  1. ኤርትራን ወደ ኢትዮጵያ ለመመለስ በአለም ሸንጎ ላይ ለሰባት አመታት ተሟግተው ድሉን ያገኙት ጸሀፊ ትእዛዝ አክሊሉ ሀብተወልድ
  2. ኤርትራን ከፌደሬሽን አስተዳደር ወደ ፍፁም አንድነት ለማዋሀድ ያበቁዋት ቢትወደድ አስፍሐ ወልደሚካኤል
በሠጡኝ ሰነዶች በሰፊው ተጠቅሜያለሁ። ከነዚህ ሌላ በአዲስ አበባና በሮም በዋሽንግተንና በኒውዮርክ፣ በሎንዶንና በፓሪስ እየተዘዋወርኩ ብዙ ምርምና ትናጦች አድርጌአለሁ።

ማንም ሰው እንደሚያውቀው የኤርትራ ጉዳይ በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ ምንጊዜም የሚኖር ነው። ሰው የሚያውቀውን ፅፎ ማስጣወሻ ቢተው፣ በተለይ እኛን ለሚተካው ትውልድ የጠለቀ ምርምር ለማድረግ እንደሚረዳይ አይጠረጠርም። ይህ እጅግ የተወሳሰበ የታሪክ አካሄድ ያለው ጉዳይ፣ በጣት በሚቆጠሩ ሰዎች ብዕር ብቻ ተፅፎ አይቆምም። እንኩዋንስ በቅርቡ የተፈፀመው ቀርቶ የጥንቱም ቢሆን በየጊዜው በሚደረገው ምርምር፣ አዳዲስ ሰነዶች ስለሚፈልቁ ፅሁፉ እንደቀጠለ ነው። ለምሳሌ የዛሬ ሁለት መቶ አመት የተፈጠረው የፈረንሳዩ የቀዳማዊ ናፖሊዮን ታሪክ እስካሁን ተፅፎ አላለቀም። በዚህ አይነት ሲታይየኛ የኢትዮጵያችን ጉዳይ ገና አልተጀመረም ማለት ይቻላል።

በቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዘመን የተከናወነውን የኤርትራን ጉዳይ በበኩሌ አሟልቸ ለማቅረብ ብዙ ጥረት ስለአደረኩ፣ አንባቢዎች ጠቃሚ ነገሮች እንደሚያገኙበትተስፋ አደርጋለሁ"  ብለዋል።

ሊሎች ምሁራን ስለዚሁ መፅሃፍ የሚከተለውን አስተያየታቸውን ፅፈዋል።
 

  1. ፕሮፌሰር ታደሰ ታምራት:- "...ይህ የአምባሳደር ዘውዴ ረታ ያሳተሙት 'የኤርትራ ጉዳይየተባለው መፅሃፍ፣ በኛ በታሪክ ተማሪዎችና መምህራን በኩል እስካሁን ሙሉ በሙሉ ያላየናቸውና ያልደረስንባቸውን ቀጥተኛ መረጃዎች ለብዙ አመታት ብክብር ጠብቀው በማጥናትና በማመሳከር፤ አዲስ የተጣራ ዘገባ ስለአቀረቡልን ደራሲውን በሕዝብ ፊት እናመሰግናለን ..."
  2. ፕሮፌሰር መርዕድ ወልደአረጋይ "ይህ ዘውዴ ረታ አዘጋጅቶ ያቀረበልን መፅሀፍ አንደኛ ለኢትዮጵያውያን የመስሪያ ቁዋንቁዋ በሆነው በአማርኛ በመፃፉ  ሁለተኛ ኢትዮጵያዊና ሃገራዊ በሆኑ ምንጮች ተመስርቶ በመፃፉ፤ ለዚህ ውስብስብ መስሎ ለሚያየው የኤርትራ ጉዳይ አስተማማኝ የሆነ ግንዛቤ ይሰጣል ብዬ እገምታለሁ"
  3. ፕሮፌሰር ባህሩ ዘውዴ:-  "የዛሬ ሠላሳ አመት ግድም አምባሳደር ሐዲስ ዓለማየሁ በሎንዶን ቦሮዋቸው የቀመሙትን ፍቅር እስከ መቃብር የተሰኘውን የዘመናችን ምርጥ ልብወለድ ድርሰት ለአንባቢያን አቀረቡ፣
  4.   ዛሬ ደግሞ አምባሳደር ዘውዴ ረታ ሌላ ፍቅር እስከመቃብር ይዞልን ብቅ ብሏል።...ደራሲው ለአፄ ኃይለሥላሴ መንግስት በነበረው ቀረቤታና በተለይም ለኤርትራ ጉዳይ የታሪኩን ሁለት አበይት ተዋንያን፣ ማለትም የአክሊሉ ሀብተወልድ እና የአስፍሐ ወልደሚካኤልን አመኔታ በማግኘቱ፣ አያሌ ብርቅ ይሆኑ ሰነዶች ለጥናቱ ድምቀትና ጥልቀት ሊሰጡት ችለዋል። በዚህም አማካይነት በትውልዶች መካከል ተፈጥሮ የቆየውን የእውቀትና የልምድ ክፍተት ለመድፈን አንድ ትልቅ አስተዋፅኦ ያደርጋል። አምባሳደር ዘውዴረታ ከፍተኛ የታሪክ ስልጠና ሳያገኝ የተካነበትን የጋዜጠኝነት ሞያ በመመርኮዝ ታሪካዊ ሁኔታዎችን ተረድቶ በሚጥም ቁዋንቁዋ ትልቅ ገፀ-በረከት ስለአቀረበልን እናመሰግነዋለን"
  5. ************************************************************************** 

ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ

ማሞ ካቻ (አቶ ማሞ ይንበርብሩ)

  አቶ ማሞ ይንበርብሩ (ማሞ ካቻ) እስቲ እናስታውሳቸው፣ ተቀብሮ እንዳይቀር አኩሪ ታሪካቸው  (ደረጀ መላኩ)   አቶቢሲ ማሞ ካቻ የት ትሄዳለህ? ገብረ ጉራቻ… ታዳጊው ማሞ ይንበርበሩ ገና በጨቅላ እድሜው አባቱ አቶ...