ያዕቆብ ወልደማርያም
ጎምቱ ጋዜጠኛ!__ያዕቆብ ወልደማርያም ************************* ስለ ኢትዮጵያ የጋዜጠኝነት ታሪክ ሲወሳ ስማቸው አብሮ ከሚጠቀሰው ውስጥ ይመደባሉ። የመንግሥታዊው «ዘ ኢትዮጵያን ሄራልድ» ጋዜጣ የመጀመሪያው ኢትዮጽያዊ ዋና አዘጋጅም ሆነው ሰርተዋል - አቶ ያዕቆብ ወልደማርያም። ዛሬም በ86 ዓመታቸው ከሙያው አልራቁም። ያነባሉ፣ ይጽፋሉ፣ በሌላ ሰው የተጻፉትንም ያርማሉ። ይህን ተግባራቸውን የነፍሳቸው ምግብ ያህል የሚቆጥሩት አቶ ያዕቆብ፤ በሚዲያ ራሳቸውን ለማስተዋወቅ ፈቃደኛ አይሆኑም። ስለ ሥራቸውና ማንነታቸውም መናገርን አይሹም። «ታዋቂነትና ዝነኝነት በሥራ እንጂ በቲፎዞ ወይንም በሌሎች ፍላጎትና ግፊት መሆን የለበትም» ብለው ያምናሉ። ይህን እያሰብኩ ከአንድ ወዳጃቸው ስልካቸውን ወስጄ ደወልኩ፤ ስልካቸውን አነሱ። ማንነቴን ገልጬ ለቃለ ምልልስ ቀጠሮ እንዲይዙልኝ ጠየቅሁ። በቀላሉ ፈቃዳቸው ይሆናል ብዬ ባልገምትም በስልክ ንግግራችን ብዙም የማሳመን ጥረቴን ሳልገፋ «የእኔ ታሪክ ለሌሎች የሚጠቅምና የሚያስተምር ከሆነ መልካም፤ ይሁን!» የሚል ምላሻቸውን አገኘሁ። በሦስተኛው ቀን በተቀጣጠርንበት ሰዓት ሽሮ ሜዳ ወደሚገኘው መኖሪያ ቤታቸው ያቀናሁት እኚህን ጎምቱ (በሳልና አንጋፋ) ጋዜጠኛ፣ በአገሪቱ ወሳኝ የታሪክ ምዕራፎች ሁሉ ሃሳባቸውን በብዕራቸው ሲያነጥቡ፤ የሌሎችንም ጽሑፎች ሲያረቱ የነበሩትን አረጋዊ እንዴት ባለ አቅም ቃለ መጠይቅ ማድረግ እንደሚገባ እያሰብኩና እያሰላሰልኩም ነበር። የእርሳቸው አቀራረብ ግን ነገሮችን ሁሉ ቀላል የሚያደርግ ሆነ። ለማንበቢያና ለመጻፊያ ምቹ ሆኖ በተዘጋጀና በመስታወት በተከለለ በረንዳቸው ከሁለት ሰዓት በላይ ባደረግነው ቆይታ የበርካታ ዘመናት ጋዜጠኝነት ሙያዊ አስተዋጿቸውንና የሕይወት ልምዳቸውን እንዲህ አወጉኝ...